Monday, October 31, 2016

በቀይ ሽብር ዘመን የኢሕአፓ የመረጃ ሰው ወይዘሮ መታሰቢያ ስዩም ሰሙንጉስ ኣረፉ።


በቀይ ሽብር ዘመን የኢሕአፓ የመረጃ ሰው ወይዘሮ መታሰቢያ ስዩም ሰሙንጉስ  ኣረፉ። የወይዘሮ መታሰቢያ ስዩም ሰሙንጉስ ኣጭር የሕይወት ታሪክ እንደሚከተለው ነው።
ወይዘሮ መታሰቢያ ስዩም ሰሞንጉስ ከ አባታቸው ከኣቶ ስዩም ሰሙንጉስ ተጫኔ እና ከእናታቸው ከወይዘሮ ኣቦነሽ በቀለ በኣዲስ ኣበባ ተረት ሰፈር በሃምሌ 23 ቀን 1949 ኣመተ ምህረት ተወለዱ፤ ወይዘሮ መታሰቢያ ስዩም ሰሙንጉስ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸውን በሲቢስቴ ነጋሲ ትምህርት ቤት ሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን በሽመልስ ሃብቴ ትምህርት ቤት ኣጠናቀዋል።
ወይዘሮ መታሰቢያ ስዩም ሰሙንጉስ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ካጠናቀቁ በኋላ ፒያሳ ከሚገኘው የኣተሻገመ የጽሕፈት ስራ ትምህርት ቤት የጽሕፈት ስራዎች ስልጠና በመውሰድ በሰርተፍኬት የተመረቁ ሲሆን እንዲሁም በኣዲስ ኣበባ የንግድ ስራ ኮሌጅ በጸሃፊነት ሙያ የሚሰጠውን ትምህርት በመከታተር በዲፕሎማ ተመርቀዋል በተጨማሪም በፍት ህ ሚኒስቴር ስር የተለያዩ የሕግ ትምህርቶችን በመከታተል እስከለተ ሞታቸው ድረስ በሕግ የማማከር እና በሕግ ኣገልግሎት ስራ ላይ ተሰማርተው ከ30 ኣመት በላይ ቆይተዋል።
ወይዘሮ መታሰቢያ ስዩም ሰሙንጉስ በትግል ስማቸው በለጥሻቸው አምሐ በቀይ ሽብር ዘመን በተንቀሳቀሱበት ሁሉ የደርግ ገዳዮችን ኮቴ በመከተል ለኢሕኣፓ የመረጃ ስራ ሲሰሩ እንደነበር እና የበርካታ የሕዋስ ኣባላትን ሕይወት እንዳተረፉ የሕይወት ታሪካቸው ያስረዳል ። ወይዘሮ መታሰቢያ ስዩም ለተቸገሩ የነጻ የሕግ ኣገልግሎት በመስጠት እንዲሁም በማህበራዊ መስክ ሕዝብን በነጻ በማገልገል ኖረዋል።
ወይዘሮ መታሰቢያ ስዩም ሰሞንጉስ በደረሰባቸው ድንገተኛ ሕመም ያረፉ ሲሆን የቀብር ስነስርዓታቸው ቦሌ ሩዋንዳ በሚገኘው የቅዱስ ሚካዔል ቤተክርስቲያን ተፈጽሟል። ወይዘሮ መታሰቢያ ስዩም ሰሙንጉስ ባለትዳርና የኣምስት ልጆች እናት ነበሩ። ፈጣሪ ነብሳቸውን በገነት ያኑርልን።

No comments:

Post a Comment