Friday, October 21, 2016

ኢትዮጵያ የኢንተርኔት አገልግሎት እንዲቋረጥ በማድረጓ ወደ 9 ሚሊዮን ዶላር (180 ሚሊዮን ብር) አካባቢ ማጣቷ ተገለጸ


ኢሳት (ጥቅምት 10 ፥ 2008)
በኢትዮጵያ የተከሰተውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ ሃገሪቱ የኢንተርኔት አገልግሎት እንዲቋረጥ በማድረጓ ምክንያት ወደ 9 ሚሊዮን ዶላር (180 ሚሊዮን ብር) አካባቢ ማጣቷን አንድ አለም አቀፍ የቴክኖሎጂ ተቋም ይፋ አደረገ።
ሃገሪቱ ለስድስት ወር የሚይቆየውን አዋጅ ተግባራዊ ካደረገች በኋላ የሞባይል ኔትወርክና ኢንተርኔት መዘጋት የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ክፉኛ እየጎዳ እንደሚገኝ ካርትዝ አፍሪካ (Quartz Africa) የተሰኘ መጽሄት ዘግቧል።
ገዢው የኢህአዴግ መንግስት ተግባራዊ በተደረገው በዚሁ አዋጅ ኢትዮጵያ ከፍተኛ ገቢን ከሚያጡ የአፍሪካ ሃገራት መካከል ግንባር ቀደም ሆና ተፈረጃለች።
መቀመጫቸውን በአዲስ አበባ ያደረጉ የተለያዩ ሃገራት መንግስት የኢንተርኔት አገልግሎትን ዝግ በማድረጉ ምክንያት ስራቸው እየተስተጓጎለ መሆኑን ባለፈው ሳምንት ቅሬታ ማቅረባቸው ይታወሳል።
ኢትዮጵያ እጅግ ዝቅተኛ የተባለ የኢንተርኔት እና የሞባይል ስልክ ግንኙነት ተጠቃሚ ሃገር ናት።
በህወሃት/ኢህአዴግ የሚመራው መንግስት በኦሮሚያ ክልል በዚህ አመት ብቻ 4 ጊዜ የማህበራዊ ሚዲያ ማቋረጡን ዘገባው አመልክቷል።
በቅርቡ ደግሞ አዲስ አበባን ጨምሮ በአማራና ኦሮሚያ ክልሎች የሞባይል ኔትዎርክ በመቋረጡ ሃገሪቱ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዶላሮች እያጣች ነው።
አክሰስ ናው (Acces Now) በተሰኘ የቴክኖሎጂ ኩባንያ የሰብ-ሰሃራ አፍሪካ ፖሊሲ ተንታኝ የሆኑት ኤፕሬም ፔርሲ ኬንያቶ መንግስት በኢንተርኔት የሚደረጉ የመረጃ ልውውጦችን ዝግ ቢያደርግም ህዝባዊ ተቃውሞው ግን ከቁጥጥር ውጭ ሆኗል ሲሉ ተናግረዋል።
የአፍሪካ የሰብዓዊ መብት ኮሚሽንን ጨምሮ የተለያዩ አለም አቀፍ ተቋማት የኢትዮጵያ መንግስት የወሰደውን ዕርምጃ እንዲያጤነው በመጠየቅ ላይ ናቸው።

No comments:

Post a Comment