Wednesday, March 22, 2017

አዲስ አበባ በውሃ፣ በመብራት እና በነዳጅ እጥረት እየተሰቃየች ነው




(ዘ-ሐበሻ) በአፍሪካ መዲና አዲስ አበባ የውሃ፣ የመብራት እና የነዳጅ እጥረት ነዋሪዎቿን እያጎሳቆለ እንደሚገኝ ከሃገር ቤት የመጡ መረጃዎች አስታወቁ:: በአዲስ አበባ የውሃ እጥረት ችግር ተባብሶ የቀጠለው ለከተማዋ የውሃ አቅርቦት የሚያገለግሉ ጉድጓዶች በመድረቃቸው ምክንያት መሆኑን የህውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን ማስታወቁ ይታወሳል::
file photo

መስሪያ ቤቱ ይህ ችግር ተቀርፏል በሚል በመንግስት ሚዲያዎች ቢናገሩም የውሃ እጥረቱ ተባብሶ መቀጠሉ ተዘግቧል:: በተለይም በአሁኑ ወቅት ጐተራ፣ ሳሪስ አቦ፣ ቂርቆስ፣ ስታዲየም፣ ቦሌ፣ ሃያ ሁለት፣ ቤተ-መንግሥት አካባቢ፣ የካ ጣፎ ኮንዶሙኒየም፣ የካ ሃያት፣ ወሰን ግሮሰሪ፣ ካራ ስላሴ፣ ሽሮ ሜዳ፣ ፈረንሣይ ለጋሲዬን፣ ቤላ፣ ካዛንቺስና ላንበረት መናኸሪያ አካባቢዎች የውሃና የመብራት እጥረት ነዋሪውን እየፈተነው ነጋዴዎችም የንግድ እንቅስቃሴያቸውን በተቀላጠፈ መንገድ ማካሄድ እንዳልቻሉ ተገልጿል::
በሌላም በኩል አዲስ አበባ ከውሃና ከመብራት እጥረቱ በተጨማሪ የነዳጅ እጥረት ነዋሪውን እያማረረው መሆኑ ተሰማ:: ላለፉት ሁለት ሳምንታት በአዲስ አበባ ነዳጅ ለመቅዳት ረዥም ሰልፍ እና ጋዝ ማደያዎች በራፍ ላይ እንደሚያድሩ የሚገልጹት ምንጮች የኢትዮጵያ ነዳጅ አቅራቢ ድርጅት በነዳጅ አቅርቦት ላይ የተፈጠረ ምንም ችግር የለም ቢልም ነዋሪው ግን የ ዕለት ተ ዕለት ተግባሩን እንዳያከናውን ችግር ፈጥሮበታል::
መንግስት ማንን እንደሚዋሽ አይገባንም የሚሉት አስተያየት ሰጪ አሽከርካሪዎች እነርሱ በሚድያ እጥረት የለም እያሉ ሕዝቡ ግን ጋዝ ማደያዎች ላይ ተኮልኩሎ ይውላል ሲሉ ተናግረዋል::

No comments:

Post a Comment