Friday, March 31, 2017

አንድ ኦራል ተሽከርካሪ ከ30 በላይ ወታደሮችን አሳፍሮ ከመተማ ወደ ቋራ ወረዳ በመጓዝ ላይ እያለ በመገልበጡ ሁሉም ወታደሮች አልቀዋል።

   
አንድ ኦራል ተሽከርካሪ ከ30 በላይ ወታደሮችን አሳፍሮ ከመተማ ወደ ቋራ ወረዳ በመጓዝ ላይ እያለ  በመገልበጡ ሁሉም ወታደሮች አልቀዋል።
መጋቢት ፳፪ (ሃያ ሁለት)ቀን ፪፲፻፱ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- የኢሳት ወታደራዊ ምንጮች እንደገለጹት ከሳምንት በፊት አንድ ኦራል ተሽከርካሪ ከ30 በላይ ወታደሮችን አሳፍሮ ከመተማ ወደ ቋራ ወረዳ በመጓዝ ላይ እያለ ለምለም ተራራ ላይ ሲደርስ በመገልበጡ ሁሉም ወታደሮች አልቀዋል። ምንጮች አሰቃቂ ሲሉ በጠሩት በዚህ አደጋ የአንድም ወታደር ህይወት ሊትርፍ አለመቻሉን ተናግረው፤ በከፍተኛ ሁኔታ የተቃጠሉና አካላቸው የተለያዩ ወታደሮች አስከሬን እየተለቀመ ተወስዷል። አደጋው በምን ምክንያት እንደተከሰተ እስካሁን ለማወቅ አልተቻለም። ወታደሮቹ በአካባቢው የሚንቀሳቀሱ ታጋዮችን እንዲያድኑ ተልእኮ ተሰጥቷቸው ነበር። ከዚሁ አካባቢ ዜና ሳንወጣ ከሁለት ሳምንት በፊት በአካባቢው የሚንቀሳቀሱ ታጋዮች በቋራ ወረዳ አስተዳደር ላይ የፈጸሙትን ጥቃት ተከትሎ በተነሳ የእሳት አደጋ በአቅራቢያው የነበሩት ፍ/ቤት፣ የግብርና ጽ/ቤትና ሌሎችም መስሪያ ቤቶች ከወደሙ በሁዋላ ፣ አብዛኞቹ የወረዳው ባለስልጣናት ተይዘው ታስረዋል። ባለስልጣናቱ ከታጋዮች ጋር ግንኙነት ፈጥረው ጉዳት እንዲደርስ አድርገዋል በሚል ጥርጣሬ በቁጥጥር ስር ቢውልም ይህን የሚያሳይ መረጃ እስካሁን አልቀረበባቸውም። ይህ በእንዲህ እንዳለ ትንናት የአርበኞች ግንቦት 7 ታጋዮች የ3 ሚሊሺዎችን የጦር መሳሪያ ነጥቀው መውሰዳቸውን ተከትሎ፣ ታጋዮችን ለማደን የወጣ አንድ ሻምበል ጦር ይህን ዜና እስካጠናከርንበት በኢትዮጵያ ሰአት አቆጣጠር እስከ ቀኑ 11 ሰአት አለመመለሱ ታውቋል። ወታደሮች በተያዘላቸው ሰአት አለመመለሳቸውን ተከትሎ የተለያዩ አስተያየቶች እየተሰጡ ቢሆንም፣ ወታደሮቹ ለምን እንዳልተመለሱ ኢሳት እስካሁን ተጨባጭ መረጃ ለማግኘት አልቻለም። ከዚሁ ጋር በተያያዘ በጭልጋ ወረዳ ሻርዳ ቀበሌ፣ 17 አርሶአደሮች አንድ የነጻነት ታጋይን ካላስገባችሁ እርምጃ ይወሰድባችሁዋል በመባላቸው ጫካ ለመሰደድ ተገደዋል። ነፍሰጡሮች ሳይቀሩ ጫካ ለማደር መገደዳቸውን ታጋዩ ይናገራሉ።

No comments:

Post a Comment