Tuesday, November 29, 2016

ወዳጄ አቶ ደምስ በለጠ ሰላምታዬ ይድረስህ። (ፈቃደ ሸዋቀና )


ወዳጄ አቶ ደምስ በለጠ ሰላምታዬ ይድረስህ። (ፈቃደ ሸዋቀና )
ወዳጄ አቶ ደምስ በለጠ ሰላምታዬ ይድረስህ። ፊስ ቡክ ላይ አስተያየት ስሰጥ አስተያየት ከሰጠሁበት ጉዳይ ጋር ተያይዞ ስምህን ጠቅሼ ፓል ቶክ ላይ ስትናገር ስምቼ ያነሳሁትን ነገር አስመልክቶ የሰጠኸውን ምላሽ አንብቤያለሁ። በመጀመሪያ ነገር ወዳጅነታችንንና አብረን ያሳለፍነውን ጊዜ አንስተህ የተናገርከው እውነት ነው። ዛሬ በኑሮ ምክኛት ተራራቅን እንጂ በጣም የቅርብ ሰዎች ነን። አሜሪካ ተሰደን የገባነውም አንድ ሰሞን እንደነበረ አሳታውሳለሁ። በጊዜው ውሏችንም እንድ ላይ እንደነበረ የተናገርከው እውነት ነው። እውነቱን ለመናገር እኔ ሀሳብ በሰጠሁበት ጉዳይ ላይ ያለህ አመለካከትና የያዝከው ፖለቲካ ላይ ያለኝ አሉታዊ አስተያየት እንደሰው ብቻ ሳይሆን እንደወዳጅ ከማይህ ሰው ጋር አይገናኝም። ክፉ ነገር እንዲያገኝህ ቀርቶ ሰው ክፉ እንዲመኝብህ አለመፈለግ ብቻ ሳይሆን አልፈቅድም። ስብዕናህና የምትከተለው ፖለቲካም ለኔ የተለያየ ነገር ነው። ፖለቲካህን መተቸትም መጥላትም ከሌላው ላንተ እንደወዳጅ ካለኝ አመለካከት ጋር የተለየ ነው። አለመታደል ሆኖ እኛ ፖለቲካ ውስጥ ይህንን መለየት እንችልም። ፖለቲካቸው አላግባባ ያላቸው ሰዎች ደም እንደተቃባ ባላንጣ ሲሆኑ ያሳዝነኛል። ከዚህ አይነት መንጋ ጋር እንዳትዳበል ምኞቴም ጸሎቴም ነው።
ወደ ዋናው ነገር ልመለስ። እንግዲህ አንተ ላይ ሳይሆን ስህተት ነው የምለው ሀሳብህ ላይ ልመጣ ነውና መቻል ሊኖርብህ ነው። በመጀመሪያ ለጽሁፍህ የስጠኸው “ካብ አይገባ ድንጋይ” የሚለው ርዕስ መሳይ ነገርና የምኒልክንና የጎበናን ተረት የጨመርከው ነገር ጥንቸል ወዲያ ምዝግዝግ ወዲህ ነው። እንደምታውቀው እኔ መንዝና ይፋት ነው ተወልጄ ያደኩት። ያማራን ወግ በማወቅም ሆነ የቋንቋውን አሰላለጥ ካንተ አዲስ አበባ አደኩ ከምትለው በተሻለ አውቀዋለሁ። በሽሙጥ መሳደብህ መሆኑ ገብቶኛል። ከጠቀመህ ልትጨምርበት ትችላለህ። የተቸሁትን የተሳሳተ አስተሳሰብህን ግን የከዘራ ያህል እንኳን ቀና አያደርገውም። በተለይ የሚኒልክና ጎበና ተረትህ የየጁ ደብተራ ቅኔው ቢያልቅበት ቀረርቶ ጨመረበት እንደሚባለው ነው። ያነሳሁትን ነገር ባግባቡ መመለስ አለመቻልን ለመሸፈን የተፈጠረ ዘዴ መሆኑ ገብቶኛል።
የፓልቶኩን ውይይት ባጋጣሚ ሰማሁ ያልኩት ውሸት ነው በማለት ውሸታም ልታስመስለኝ ያደረከው ሙከራም ፍሬ ከርስኪ ነው። በእለቱ አንድነት የጋበዘኝ መሆኑ ልክ ነው። የናንተን ውይይት እንድሰማ አልጋበዘኝም። ጠይቀው። ሁል ጊዜ እንደሚያደርገው ስልኬ ላይ ደውሎ ሀሳብ በስልክ እንድሰጥ ነው የሚጋብዘኝ። እደውላለሁ ብሎ ሳይደውልልኝ ስለዘገየ ምን እንደተፈጠረ ለማወቅ ብዬ ነው ፓልቶክ ክፍሉ ውስጥ የገባሁት። ይህን ፕላን ሳላደርግ ገብቼ መስማቴን ነው ባጋጣሚ ያልኩት። ይችችን ነገር ብትተዋት ላንተም አይጎዳህም። እኔ ፐርሰናሊቲ ላይ እንከን መፈለግ እንዳልኩህ ያንተን ጎባጣ አስተያየት አያቀናውም። ያንድ ግለሰብ ስም ጠርተህ ከሱ ጋር ፌስ ቡክ ላይ ስትነጋገሩ “የአማራው ትግል የምትሉት ወንዝ የማያሻግር ሀሳብ ነው ብለህ ነበር” ብለህ የጻፍከውም ከሰማይ ላይ ቧጠህ መሆን አለበት። እንዲህ አይነት ነገር አልተናገርኩም። ተመልሰህ ሄደህ እንበው። ደረቅ ዉሸት ነው። ጽሁፉን ብዙ ሰው ስላነበበው ይታዘቡሃል። ከግለሰቡ ጋር የተመላለስንበት ጉዳይም ይህ አልነበረም። እንድ የማውቀው ሰው በስም ተጠቅሶ ዘሩ ባባቱ ኤርትራዊ በናቱ ጎጃሜ ስለሆነ በክፉ እንድንጠረጥረው የሚያስገነዝብ ፖለቲካ እይቼ ነበረ አስተያየት የሰጠሁት እንጂ ስለ አማራ መደራጀት አለመደራጀት አልነበረም።እኔ በመርህ ደረጃ ባማራ መደራጀት ላይ ችግር የለብኝም። አላማው ራዕዩ ገቡና ስትራቴጂው ብቻ ነው ጥያቄዬና ጭንቀቴ።
እንዳነበብከው እኔ ካንተም ሆነ እንተ ትንታግ ኣማራ ከምትላቸው ሰዎች ጋር ያላስማማኝ ግፋ በለው የምትሉትን ጎንደር ውስጥ የሚጋደለውን የገበሬ ተዋጊ ሀይል ማፈግፈጊያም ሆነ ስንቅና ትጥቅ ማቀበያ ሊጠቅመው ከሚችል የኤርትራ መንግስት ላይ ማቅራራት ማብዛታችሁ ስትራቴጂክ ሂሳብ ማድረግ የተሳናችሁ መሆኑን መተቼቴ ነው። ይህን ትችት ሳቀርብ ተሳስቼ ከሆነና ተገቢ ምላሽ ካገኘሁ ሀሳቤን ለመለወጥ ክፍት ህሊና ይዤ ነው። ሁለትና ሶስት ወር የማይዘልቅ ትጥቅና ስንቅ የያዘን ተዋጊ ካለው በቂ ጠላት ሌላ ለምን ትጨምሩለታላችሁ ነው ያልኩት። እንዲሁም ኤርትራ ሆነው ሚታገሉት ወገኖቹ ላይ የምታካሂዱት አድፋፊ ፖለቲካ ከጉራና ከደመነፍሳዊ አርበኝነት የበለጠ ስትራቴጂያዊ ስሌትና ማውጠንጠን የሌለበት ግልብና የገልቱ ስራ ሆኖ ማግኘቴን ነው የተናገርኩት። እሁን ደግሞ መልስ ስትሰጠኝ የትግል ስልት ሞዴልህ የጣሊያን ጊዜው የነአበበ አረጋይ መሆኑን ነግረህናል። ይህ መቼም ለወገን ትንሽ መጨነቅ የማይታይበት አሌሜንታሪ ስሌት የሌለበት ጉራ ከመሆን የማይዘል የህጻን ጨዋታ የሚተካከል ነገር ነው። ለነገሩ በጣሊያን ጊዜም ቢሆን መሳሪያ ለማስገባት አባቶቻችን ሱዳንን የመሰለ ጎረቤት ሀገር ተጠቅመዋል። ጃንሆይም ካገር የወጡት በጂቡቲ በኩል ነበር። ይህ ፈጽሞ የማይረባ ስትራቴጂክ አስተሳሰብ መሆኑን ለማውቀ ወታደራዊ ሳይንስ እውቀት አይጠይቅም። ከጣሊያኖች ጋር የተደረገው ትግል ባይነቱም በይዘቱም ዛሬ ከብዙ አሰርት አመታት በሁዋላ ከተለወጠው አለምና ከምንዋጋው መንግስት ጋር የሰማይና የመሬት ያህል ልዩነት አለው። አማራ ሲተርት ቀን አስኪያልፍ ያባትህ ባሪያ ይግዛህ ይላል። ምን ቸገራችሁ ቀን እስኪያልፍ አጎንብሶ እየሄደም ለአለማው የሚጠቅመውን ነገር ቢያደርግ? ለመሆኑ ባፍ ሲወራ የምሰማው ርዳትችሁ በየት አርጎ ነው የሚደርሰው? እሁን ይህን መገንዘብ ወታደራዊ ሳይንስ መማር የሚጠይቅ ነገር ነው? የኔ አገር ሰው እንዲህ አይነቱን በባዶ ቤት የሚካሄድ መመጻደቅና ጉራ ቂጥ ገልቦ ክንብንብ ይለዋል።
አሳቀኝ ያልኩህን ኢሳያስ አማርኛ የማይናገረው አማራ ስለሚጠላ ነው የሚለውን መላ ምትህን ትክክለኝነት መመከትም አልቻልክም። የጠንቁዋይ ፖለቲካ የሚለው ቃል የኔው ቃል ነው። ትንሽ መላ ምትን እንደ እውነት የሚያወሩ ሰዎችን የምገልጽበት ቃል ነው። እኔ ለምሳሌ ከኢትዮጵያ ጋር የለውን የእንድ ሀገርነት ስሜት ለማስወገድ ሲል የሚያደርገው ይመስለኛል። ወይም ብዙ ኤትዮጵያዊ ደም ስላለው ከዚያ ጋር እንዳይያዝበት አስቦ ይሆናል ማለት እችላለሁ። አንተ እንደውነት የወሰድከውን መላ ምት የሚወዳደሩ መላ ምቶች ላሳይህ ብዬ ነው ይህን የምጠቅስልህ። ለወደፊቱም ከደመነፍስህ ይልቅ እመክኖአዊነት ላይ ብትበረታ ጥሩ ነው። ከተሳሳተ መደምደሚያ ላይ የተነሳ ሰው ትንታኔው ሁሉ ከንቱና ስህተት ከመሆን አያልፍም።
“አስተማሪ ነህ እንጂ ወታደራዊ ሳይንስ አታውቅም” የምትለው ክርክርህ ውሀ አታነሳም። የክርክራችን ጉዳይ ወታደራዊ ሳይንስ አይደለም common sense ነው። ትጥቅና ስንቅ ሰራዊት እንደሚያስፈልገው ለማወቅ ወታደራዊ ሳይንስ መማር አለብህ እያልከኝ ነው። ውሽልሽል ክርከር ነው። እጅም እግርም የለውም። በነገራችን ላይ ብዙ ነገር አነባለሁ። አዋቂዎች እጠይቃለሁ። በማላውቀው ነገር ላይ በድፍረትና በደመነፍስ ዘው የምል ሰው አይደለሁም። ወይም የተማርኩትን ሞያ አንተ እዚያ ፓልቶክ ላይ ስትናገር እንደሰማሁት ሚስጥረ ስላሴ ማስመሰል አልፈልግም። እዚያው ፓል ቶክ ላይ በጆርናሊዝም ከራሺያ የማስተርስ ዲግሪ ስላለኝ ብዙ ኤርትራ ውስጥ ያሉ ነገሮችን የማወቂያ መንገድ አለኝ እያልክ ስትናገር ሰምቼ የልታዘብኩህ መስሎሀል። በነገራችን ላይ ኤርትራ በአካል ብዙ ጊዜ መመላስለስክን ካልሄድነው ሰዎች የተሻለ መረጃ እንዳለህ ለማስመሰል የሞከርከው ብዙ አያስኬድም። በዚህ የኢንፎርሜሽን ዘመን መረጃ ለማግኘት ቦታው ድረስ በአካል መሄድ የለብህም። ብታምንም ባታምንም ስለዚያ አካባቢ ካንተ የተሻለ ወቅታዊም ታሪካዊም መረጃ አለኝ። እንዳንተ ደጋግመው ኤርትራ የሚመላለሱ ነገር ግን ካንተ በጅጉ የተለየ መረጃ የነገሩኝ ሰዎችም አሉ። ያንተ ልክ ሆኖ የነሱ ስህተት የሚሆንበት ምክኛት የለም። እዚህ ለማውራት ተራ ወሬ ይሆናል እንጂ እንተንም አብሮህ ይጉዋዝ የነበረውን ጉዋደኛህን ሰለሞን ተካልኝንም አስመረረን ስለምትሉት ነገር የሚወራውን ሰምቻለሁ።
በመጨረሻም ይህቺን ወንድማዊ ማሳሰቢያ ላጋራህና ላብቃ። እውነቱን ለመናገር ይህ ያማራ ብሄርተኛ ነን ማለትን እንደፋሽን የተያያዙት ሁሉ ፖለቲካቸውን ባግባቡ ካልያዙ ላማራ ህዝብ አደገኛና አጥፊ ( liability) ሲሆን ይታየኛል። የፖለቲካ ትግል ወታደራዊም ቢሆን ከግማሽ የማይተናነሰው ስራው የማሰብ ስራ ነው። ብሄርትተኝነት አደገኛ ነገር መሆኑን ከታሪክ ንባብ ትረዳለሁ ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ። ናዚዝምም የጎሳ ብሔርተኝነት ነው። ትግሬ ሁሉ ካማራ መሬት ተጠርርጎ መውጣት አለበት የሚሉ ያማራ ብሄርተኛ ነን ባዮች እዚህ ፌስ ቡክ ላይ አያለሁ። ይህ ያማራ ህዝብ ፍላጎትም ጥያቄም አይደለም። የናዚዎቹና የሩዋንዳዎቹ ሁቱዎች ጋር የሚቀራረብ ሀሳብ ነው። ኦሮሞ ህዝብና ትግሉ ላይ አፋቸውን የሚከፍቱ ያማራ ተቆርቁዋሪ ነን ባዮችም ልጉዋም ያስፈልጋቸዋል። እንዳንዶቹ ለምሳሌ የኦሮሞዎችን እንቅስቃሴና መሪዎቻቸውን ሁሉ በጅምላ ያጥላላሉ። ክ 3 ሚሊዮን የሚበልጥ ያማራ ህዝብ በኦሮሞ ክልል ውስጥ እንደሚኖር የሚያውቁም አይመስሉም። እነዚህ ሚሊዮኖች አማሮች ከኦሮሞ ህዝብ ጋር በሰላም ይኖራሉ። ኦሮሞዎች ላይ ባማራ ስም የሚደረገው አፍ ከፈታ በስላም ተስማምተው በሚኖሩት እማሮች ላይ አደጋ መጋበዝ መሆኑ የማይገባቸው ሰዎች አይቻልሁ። እነዚህን ሀይ በሉውቸው። እኔ በኢትዮጵያ ምድር እንዲህ አይነት አማራ አይቼ አላውቅም። ያማራ ህዝብ ትልቅና አስተዋይ የሆነ ህዝብ ነው። የሰከኑ እሴቶች አሉት። ያማራን ህዝብ መብት ለዘላቂው ማስከበር የሚቻለው ከሌሎች ብሔረሰቦች በተለይ ከኦሮሞ ሕዝብ ጋር ድልድይ በማበጀት መሆኑ ሊገባችሁ ይገባል። ከዚህ በተጨማሪ እንታገለዋለን የምትሉትን መንግስት ትታችሁ ከሱ ጋር የሚታገሉ ሀይሎች ጋር የያዛችሁት የአግድሞሽ ትግል ቢቆም ጥሩ ነው። ለምሳሌ ኢሳትና አርበኞች ግንቦት 7 ላይ የምታካሂዱትን ዘመቻ ብታቆሙት ጥሩ ነው። የምትጎዱት ባይኖርም እንታገለዋለን ለምትሉት መንግስት የፕሮፓጋንዳ ድጋፍ እየሰጣችሁ መሆኑ ሊገባችሁ ይገባል።
በመጨረሻም ባማራ ስም የምታካሂዱትን መስመር የለቀቀ ስራ “NOT IN MY NAME” የምንል ብዙ አማሮች መኖራችንንም እያሰባችሁ።

No comments:

Post a Comment