Friday, November 25, 2016

20 አውሮፕላኖች ተገደው ጋምቤላ ማረፋቸውን የኢትዮጵያ መንግስት አስታወቀ BBN


20 የሚሆኑ የሲቪል አውሮፕላኖች ተገደው ጋምቤላ ክልል እንዲያርፉ መደረጉን የኢትዮጵያ መንግስት አስታወቀ፡፡ የኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለስልጣን በዛሬው ዕለት ለሀገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን በሰጠው መግለጫ፣ አውሮፕላኖቹ በአሁን ሰዓትም በጋምቤላ አየር ማረፊያ እንደሚገኙ ባለስልጣኑ አስታውቋል፡፡
የባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ዋና ዳይሬክተር ኮሎኔል ወሰንየለህ ሁነኛው በመግለጫቸው ላይ ‹‹በአሁኑ ወቅት እነዚህ ተልዕኳቸው ያልታወቀና ቀድመው ወደ ኢትዮጵያ የአየር ክልል ለመግባት ፈቃድ ያልጠየቁ ቀላል አውሮፕላኖች ማንነትና የኢትዮጵያን አየር ክልል የመጣሳቸው ምክንያት እየተጣራ ነው›› ማለታቸው ተዘግቧል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ቀለል ባሉ አውሮፕላኖች በሚደረግ ውድድር ላይ ተሳታፊ የነበረ አንድ የብሪታኒያ ፓይለት ወደ ኢትዮጵያ ግዛት ከገባ በኋላ የት እንደገባ አለመታወቁን የውድድሩ አዘጋጆች ገልጸዋል፡፡ ሞሪስ ኪርክ የተባለው የ72 ዓመት ሰው አፍሪካን በሚያካልለው የጉዞ ውድድሩ ከሱዳን ተነስቶ ወደ ኢትዮጵያ ጋምቤላ ክልል በመጓዝ ላይ እያለ ግንኙነቱ መቋረጡን መረጃዎች ጠቁመዋል፡፡ ዴይሊ ሜል የተባለው ጋዜጣም ለጉዳዩ ሽፋን ሰጥቶ ዘግቧል፡፡
በኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን በኩል ዛሬ በተሰጠው መግለጫ ላይ ግን ወደ ኢትዮጵያ ጋምቤላ ክልል የገቡት አውሮፕላኖች 20 መሆናቸው ተጠቅሷል፡፡ ባለስልጣኑ፣ አውሮፕላኖቹ የኢትዮጵያን አየር ክልል ጥሰው የገቡበት ምክንያት እየተጣራ ነው ቢልም፣ ሌሎች ዘገባዎች እንደጠቆሙት ከሆነ ግን፣ አውሮፕላኖቹ ወደ ጋምቤላ ክልል ሊገቡ የቻሉት በውድድር ምክንያት ነው ተብሏል፡፡ ቀለል ባሉ አውሮፕላኖች የሚደረገው እና አስር የአፍሪካ ሃገራትን የሚሸፍነው ይኸው የአየር ውድድር በዚህ ዓመት ፕሮግራሙ፣ ዩኒሴፍ ለተባለው የተባበሩት መንግስታት የህጻናት መርጃ ድርጅት ገቢ ለማሰባሰብ የተዘጋጀ መሆኑ ተነግሯል፡፡

No comments:

Post a Comment