Sunday, May 7, 2017

«ፍልስፍና የሚጀምረው ከመደነቅ ነው» (ሞረሽ ወገኔ የዐማራ ድርጅት )




በምዕራባውያን የክርስትና እምነትና አስተሳሰብ ውስጥ ከፍተኛ ተጽዕኖ እንዳሳደረ የሚነገርለት ፕሌቶ፣ philosophy begin in wondres ይላል። ይህ ወደ አማርኛ በጥሬው ሲተረጎም « ፍልስፍና የሚጀምረው ከመደነቅ ነው» እንደማለት ይሆናል። አዎ! የምርምር መነሻው መደነቅ፣ መገረም፣ ለምን? እንዴት? የሚሉት ጥያቄዎች በአንድ ሰው አዕምሮ ውስጥ ሁነኛ ቦታ  ሲይዙ ነው። እነዚህን ጥያቄዎች እንዲያነሳ፣ የመደነቅ ስሜት በአዕምሮው ያደረበት ያ! ሰው፣ ወደ ምርምር እንዲገባ ይገፋፋል። ምርምሩም ንድፈሀሳቦችን ማፍለቅና የፍልስፍና ቀመሮችንና አስተሳሰቦችን በፈርጅ በፈርጃቸው ወደ ማስቀመጥና እነዚያን ወደ ማስፋፋት ያመራል።  መደነቅ፣ መገረም፣ መጠየቅ፣ ለአዲስ አስተሳሰብ በር ከፋች ነው። ለችግሮች መፍቻ ቁልፍ የመፍትሔ ሀሳብ ማፍለቂ መነሻ ነው። መደነቅ፣ መገረም፣ መጠየቅ፣ ለምን ?እንዴት? ካልተባለ አዲስ አስተሳሰብ፣ አመለካከት፣ እምነት፣ አሠራር አይፈልቅም።
በዛሬዪቱ ኢትዮጵያ ዘረኛው የትግሬ ወያኔ ቡድን ለ፳፮ ዓመታት ለዘመናት በቅብብሎሽ የዳበሩ ኢትዮጵያዊ ዕሴቶችን፣ እምነቶችን፣ አሠራሮችን፣ ግንኙነቶችን፣ አብሮነቶችን ወዘተ እያጠፋ፣ የአገሪቱን የብዙ ሺ ዓመታት ታሪክ በመቶ ዓመት ገድቦ ታሪኳን ሲያጠፋና ሲያጎድፍ፣ የተፈጥሮ የባሕር በሯን ወዶ አሳልፎ ሰጥቶ መተናፈሻ የሌላት ዝግ መሬት ሲያደርጋት፣ ሕዝቡን በነገድ ከፋፍሎ ዓይንና ናጫ ሲያደርገው፣ የአገሪቱንና የሕዝቡን አንጡራ ሀብት የአንድ ሽፍታ ቡድን ሲያደርግ፣ ኢትዮጵያውያን አለመደነቃችን፣ እንዴት? ለምን? አለማለታችን አገሪቱ እንደአገር፣ ሕዝቡ እንደ አንድ ሕዝብ ሊቀጥል ከማይችልበት ደረጃ ላይ እንዲደርስ የራሱን አፍራሽ ሚና ተጫውቷል።
ከሁሉም በላይ የዐማራው ቀለም ቀመስ ትውልድ፣ የመጠየቅ፣ ለምን፣ እንዴት የማለት ሁለንተናዊ አቅም ያለው ምሑር ክፍል፦
  • ወያኔ ዐማራው የትግራይ ሕዝብ ደመኛ ጠላት ነው፤ ዐማራ ካልጠፋ የትግራይ ሕዝብ ማኅበራዊ ሰላም አያገኝም ብሎ ፕሮግራም ነድፎ ዓላማውን ለማሳካት ከደደቢት እስከ ምኒልክ ቤተመንግሥት ሲንቀሳቀስ፣
  • ዐማራውን በነፍጠኝነት፣ በገዥ መደብነት፣ በጨቋኝ ብሔርነት፣ በኢትዮጵያ አንድነት ጠበቃነት ፈርጆ የዘር ማጥፋትና የዘር ማጽዳት ወንጀል ሲፈጽምበት፣
  • ዐማራው ዘሩን እንዳይተካ ተፈጥሮአዊ መብቱን ከልክሎ መካንና ታማሚ ሲያደርገው፣
  • ዐማራውንና ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖትን ዳግም እንዳያንሰራሩ አከርካሪውን መተነዋል ብለው በአደባባይ ሲፎክሩ፣
  • ዐማራን ገድለን ቀብረነዋል ሲሉ፣
  • በየእስር ቤቱ ዐማራ በመሆናቸው ብቻ አስረው የቁም ስቅል የሚያሳዩዋቸውን ወገኖች ነገዳቸውን እየጠሩ ሽንታም፣ ሱሪአችሁን አስወልቀናችኋል ሲባሉ፤
  • በራሱ በወያኔው ፓርላማ ተብየ ሁለት ነጥብ አራት(፪.፬) ሚሊዮን ዐማራ ስልታዊ በሆነ መንገድ እንደጠፋ ሲነግሩን፣
  • ከሐረርጌ፣ ከአርሲ፣ ከወለጋ፣ ከኢሉባቡር፣ ከሸዋ፣ ከጎንደር፣ ከጎጃም ፣ከከፋ ክፍለሀገሮች ዐማራ በመሆናቸው ብቻ፣ ለዘመናት ከኖሩበት አካባቢ ንብረታቸውን ተነጥቀው በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሲባረሩና የዘር ማጽዳት ወንጀል ሲፈጸምባው፣
  • የወልቃይት፣ ጠገዴ ፣ ጠለምትና አርምጭሆ ሕዝዝ ማንነቱን ተነጥቆ ትግሬ ነህ ሲባል፣ እርስቱን ተነጥቆ ለትግሬ ሲሰጥ፣ ወንዱ ሲገደል፣ ሲታሰር፣ ሲሰደድ፣
  • በአሰቦት ገዳም ክርስቲያኖችና ዐማሮች ከነሕይዎታቸው ገደል ሲጣሉ፣
  • በምሥራቅና ምዕራብ ሐረርጌ ዐማሮች በዘር ተለይተው የዘር ፍጅት ሲፈጸምባቸው፣ ነፍሰጡሮች ሆዳቸው በሳንጃ ሲተለተል፣ እንደ በግ ሲታረዱ፣
  • በአርባ ጉጉ፣ በጉራ ፈርዳ፣ በቤንቺ ማጅ፣ በወንበራ፣ ወዘተ ዐማሮች ሲታረዱ፣ በጅምላ ሲጨፈጨፉ፣
የዐማራው ቀለም ቀመስ ትውልድ አልተደነቀም። አልተገረመም፤ አልተቆጨም። ለምን? እንዴት? አላለም። ይህን  ባለማለቱም፣ አጥፊዎቹ ወያኔዎች ያሰቡትን እንዲያደርጉ ጊዜ እንዲያገኙ ረዳቸው። ዐማራውም ችግሩን የሚረዳለት አጥቶ፣መፍትሔ  ሳያገኝ ፳፮ ዓመታት በመቆየቱ ከአምስት ሚሊዮን በላይ ዐማራ ከምድረ-ገጽ እንዲጠፋ ሆኗል። ይኸም ሁላ ሆኖ የዐማራው ቀለም ቀመስ ትውልድ በወገኖቹ ላይ የወያኔ ዘረኛ አገዛዝ የሚያደርሰው ግፍና መከራ ገና አላስደነቀውም። ቢደነቅ ኖሮ መፍትሔውን ለማግኘት ፳፮ ዓመት አይፈጅበትም ነበር። በዛሬዪቷ ኢትዮጵያ የዐማራው ዓይነተኛ ችግር ፣የዐማራው ሊሂቃን በወገናቸው ላይ የሚፈጸመው የዘር ጥቃት አላስደንቀው፣ አላስገርመው፣ አላስቆጣውና አላስቆጨው ማለቱ ነው።
ዘረኛው የወያኔ ቡድን በዐማራው ነገድና በኢትዮጵያዊነት ላይ የሚፈጽመው ግፍና በደል አስደንቋቸው፣ አስገርሟቸው፣ ለምን እንዴት? ያሉ ግለሰቦችና ቡድኖች መኖራቸው ባይካድም፣ ብዙኃኑ ባለመደነቁ፣ ባለመገረሙ፣ ለምን እንዴት ብሎ ባለመጠየቁ፣ የተወሰነው ደግሞ ሆድ አደር በመሆኑ፣ ጥቂቱ ከአራጆቹ ጋር አፋሽ አጎንባሽ በመሆን፣ በድርጊቱ ተደንቀው፣ ተገርመውና ለምን እንዴት? ብለው ለችግሩ መፍትሔ ለማስገኘት አዲስ አስተሳሰብ፣ አዲስ አደራጃጀት፣ አዲስ አመለካከት ወዘተ ባፈለቁ ግለሰቦችና ድርጅቶች ላይ የሚወርደው፣ ከስም ማጥፋት እስከ ሕይዎት የማጥፋት ዛቻ የቱን ያህል በስፋት እየተሰራጨ እንደሆን ስናስተውል፣ አሁንም ገና የዐማራው ልጅ በወገኖቹ ላይ የሚፈጸመው የዘር ፍጅት ገና ያላስደነቀው ወይም ያላስገረመውና እንዴት ብሎ ለመጠየቅ ከተኛበት ያልባነነ መሆኑን ያሳያል።
ከዚህ ላይ መነሳት ያለበት ጥያቄ፣ የዐማራው ቀለም ቀመስ ትውልድ በወገኖቹ ላይ የሚደርሰው በደል እና እልቂት እንዲያስደንቀው፣ እንዲያስገርመው እና ለምን፣ እንዴት ብሎ እንዲጠይቅ፣ እስካሁን በዐማራው ላይ ያልተሞከሩ የማሰቃያ መንገዶች ምን ናቸው? ቀለም ቀመሱ ትውልድ በወገኖቹ ላይ የሚፈጸመው ግፍ እንዲደንቀው ስንትስ ዐማራ ከምድረ ገጽ  መጥፋት አለበት?  ስንትስ ዐማራ ከኢትዮጵያ ምድር መፈናቀል አለበት?የሚሉት ናቸው።
በግልጽ እንደሚታወቀው፣ ምንጊዜም አዲስ ሀሳብ፣ አዲስ አሠራር፣ አዲስ አመለካከት የሚያቀርቡ ሰዎች የሚደርስባቸው ውግዘት፣ እስራትና መከራ የት እየሌሌ እንደሆነ ይታወቃል። ዐማራው ተጠቃ ብለው፣ዐማራውን ከፈጽሞ ጥፋት ለመታደግ አዲስ የአደረጃጀት ስልት ይዘው የተነሱት ፕሮፌሰር አሥራት ወልደየስ የደረሰባቸውን ግፍ ሁላችንም እናውቃለን። በእርሳቸው ተከታዮች በነበሩት አቶ አሊ እድሪስ፣ ወንዳየን ካሣ፣ ሻለቃ  ጌታቸው መንግሥቴ፣ አሰገደች ሸዋንግዛው፣ቆምጨ ወዘተ ምን እንደተፈጸመባቸው የምናውቅ እናውቃለን።
ዛሬም ዐማራውን ከፈጽሞ ጥፋት ለመታደግ፣ ዐማራው የችግሩን ስፋትና ጥልቀት ተገንዝቦ ራሱን ከታቀደለት ጥፋት መከላከል እንዲችል ድምፅ ለመሆን በተደራጁት እውነተኛ የዐማራ ድርጅቶችና ግለሰቦች ላይ እየተራመደ ያለው እስትንፋስ የመዝጋት ፣ «ይቺ ባቄላ ካደረች አትቆረጠምም» በሚል ስሌት ድምፃቸውን ለማፈን፣ስብዕናቸውን ለማጉደፍ፣ ማንነታቸውን ለማቆሸሽ የሚደረገው ዘመቻ፣ ከወያኔና ከተባባሪዎቹ ብቻ የተከፈተ አይደለም። ይልቁንም አብዛኞቹ በዐማራው ላይ ላለፉት 26 ዓመታት የተፈጸመበት ዘር ማጥፋትና ዘር ማጽዳት ወንጀል ያላስደነቃቸው፣ ያላስገረማቸው፣ ለምን እና እንዴት ብለው ለመጠየቅ አቅሙም፣ ፍላጎቱም፣ችሎታውም በሌላቸው የዐማራው ልጆች መሆን ስንረዳ፣ «ጌታ ሆይ! የሚሠሩትን አያውቁትምና ይቅር በላቸው» ከማለት በላይ ምን ማለት ይቻላል?
አዲስ ሀሳብ፣ አዲስ አመለካከት፣ አዲስ ግኚት ያፈለቁ ሰዎች፣ግኚታቸውን ወደ ማኅበረሰቡ ለማስረጽ የሚያደርጉት ጥረት ካለውድ ዋጋ የሚሳካ አይደለም። ዋጋው ሕይዎትን፣ ደምን፣ ንብረትን፣ ማንነትን ያስከፍላል። ውግዘትን፣ ርግማንን፣መገለልን፣ ወዘተ ያስከትላል። ሆኖም ግኚቱ በሂደት ለሰው ልጆች ማኅበራዊ፣ኢኮኖሚያዊ፣ ባህላዊ፣ ፖለቲካዊና ሃይማኖታዊ ፍላጎቶች መሟላት የሚያስገኘው ፋይዳ እየጎላ ሲሄድ የተወገዘው ተመስግኖ፣ የተጠላው ተወዶ፣ የተረገመው፣ ተመርቆ፣ አንየው የተባለው ለመታየት ብርቅ ሆኖ፣የተናቀው ተከብሮ፣ማየታችን ኅብረተሰብ የደረሰበት ሁለንተናዊ የዕድገት ደረጃ፣ ያነሳቸውና የጣላቸው ፍልስፍናዎች ወይም አዳዲስ ሀሳቦች ሕያው ነቃሾች ናቸው።
ዛሬም የዐማራውን ኅልውናና ማንነት ጥያቄ አንስተው በሚንቀሳቀሱ ድርጅቶችና ግለሰቦች ላይ የሚነዛው ስም ማጥፋት ዘመቻ የተጠመዱ ድርጅቶችና ግለሰቦች፣ ለዘመቻው ያነሳሳቸው ምክንያቶች ከሚከተሉት ባንዱ፣ በሁለቱ ወይም በሁሉም ሊሆኑ ይችላሉ።
አንደኛ፦ ዐማራው መጥፋት አለበት ብለው ያመኑ፣ የዐማራው ደመኛ ጠላቶች የሆኑ፣
ሁለተኛ፦ አዳዲስ አስተሳሰብ ለመቀበል የተቸገሩ፣ በነበረ መልኩ መቀጠል አለበት ብለው የሚያምኑ፣
ሦስተኛ፦ በዐማራው ላይ የሚፈጸመው በደል እንደበደል የማይመለከቱ፣ በደሉ በሁሉም ኢትዮጵያውያን ላይ የሚፈጸም ነው ብለው ራሳቸውን የሚያታልሉ፤
አራት፦ እንደ ሰው ግፍ ሲፈጸም እያዩ ግፍን ማውገዝ የማይፈልጉ፣ በአንፃሩ በዐማራው ላይ እየተፈጸመ ያለው የዘር ማጥፋትና የዘር ማጽዳት ወንጀል ያላስደነቃቸውና ለምን ብለው ለመጠየቅ ያልፈለጉ፣
አምስተኛ፦ ዐማራው ተደራጅቶ ራሱን ከጥፋት ከተከላከለና ማንነቱን ካስጠበቀ፣ የማይነቀነቅ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ኃይል ሆኖ ስለሚወጣ፣ ይህ እንዳይሆን በእንጭጩ እንቅጨው ብለው የሚያስቡና የሚያምኑ፣
ስድተኛ፦ ዐማራውን በነፍጠኝነት፣ በገዥነት፣ በትምክህተኝነት፣ በጨቋኝ ብሔርነት ፈርጀው፣ ከኢትዮጵያ ፖለቲካዊ ሕይዎት ውስጥ ሊወገድ ይገባል ብለው የሚያምኑ፣ ወዘተ እንደሆኑ ለዐማራው ኅልውና መጠበቅ በሚጮኹ ድርጅቶችና ግለሰቦች ላይ የሚነዙት በዶለዶመ እርሳስ እየጻፉ የሚያሰራጩት የስም ማጥፋት ድርጊት ያስረዳል።
እነዚህ ወገኖች ሊረዱትና ሊረዱትም የማይፈልጉት ሐቅ አለ። በዛሬዪቱ ኢትዮጵያ የፖለቲካ፣የኢኮኖሚና የማኅበራዊ አስተሳሰብ  አሽከርካሪ ሞተር ነገድ ነው። ባለፉት 26 ዓመታት ከሕዝባችን ቁጥር ፷፭ %የሚሆነው ተግቶ ያደገው ብሔርተኝነትን እንጂ፣ ኢትዮጵያዊነትን አይደለም። ከሁሉም በላይ የሁሉም ነገዶች ቀለም ቀመስ ትውልድ ሊባል በሚችልበት መልኩ፣ የሚያቀነቅኑት ፖለቲካ በፀረ-ዐማራና በፀረ-ኢትዮጵያዊነት ላይ የተቃኘ ነው። በመሆኑም ሁሉ ዐማራውን በጠላትነት ፈርጀው እንዲጠፋ ዘመቻ ከከፈቱ ሩብ ምዕተዓመት ተቆጥሯል። ማንም ሊገነዘበው እንደሚችል፣ በዐማራውና በኢትዮጵያዊነት መካከል ምንም ዓይነት ግጭት የለም። ዐማራነት ኢትዮጵያዊነት፣ ኢትዮጵያዊነት ዐማራነት ነው። ይህ ሲባል ሌሎች ማንነቶች የሉም ማለት አይደለም። አሉ። ሁሉም ግን መገለጫቸው ኢትዮጵያዊነት ነው። ወያኔ ጠንክሮ እየሠራ ያለው ይህ ነገዳዊ ማንነቶች ከኢትዮጵያዊነት ጋር እንዲጋጩና እንዲፋቱ  ማድረግ ነው።
ብሔርተኞቹ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነትን ለማጥፋት ፣ኢትዮጵያዊነኝ ብሎ የሚያምነውን ማጥፋት ብለው አስበው፣ አቅደውና ፕሮግራም ነድፈው ከምድረ ኢትዮጵያ እያጠፉት  ያለው ዐማራውን ነው። ይህ የገባቸው የነገዱ አባሎች ፣ ዐማራው በደረሰበት ግፍ ጉድ ብለው የተደነቁ ወገኖች፣ ነገዱ ራሱን ከጥፋት አድኖ ኢትዮጵያዊነትን እንዲታደግ ጥረት በማድረግ  ላይ ይገኛሉ። ሆኖም ፀረ-ዐማራ የሆኑ ቡድኖችና ግለሰቦች ዐማራው ራሱን ከጥፋት ለማዳን ጥረት የሚያደርጉ ወገኖችን ለማሰናከል ወይም ጥረቱን ለመገደብ የሚችሉ መስሏቸው የተለያዩ መሰናክሎችን ለመፍጠር ሲውተረተሩ ይታይል።  እነዚህ ፀረ ዐማራ ቡድኖችና ግለሰቦች የሚያደርጉት መውተርተር ዐማራው ለኅልውናውና ለማንነቱ የሚያደርገውን ጥረት በምንም ተዓምር ሊገድቡትም ሆነ ሊያቆሙት አይቻላቸውም። ግን አንድ ነገር ያደርጋሉ። ራሳቸውን ከትዝብት ላይ ይጥላሉ። ኋላ በፀፀት ራሳቸውን ይገርፋሉ። እየሠሩ ያለው ሥራ የልጆች ሥራ ስለሆነ በሠሩት ሥራ ያፍራሉ። እየተጋጩ ያሉት እንደተራራ ከቆመ ደረቅ ሐቅ ጋር ነውና በግጭቱ የሚጎዱት ራሳቸው  ይሆናሉ። ይህም ፀፀትን ተሸካሚ ያደርጋቸዋል። የዐማራው የኅልውናና የማንነት ትግል የድርጅቶችንና የግለሰቦችን ስም በማጥፋት ይቆማል፣ወደ ኋላ ይመለሰል ብለው የሚያስቡ ግለሰቦችም ሆኑ ቡድኖች፣ ነባራዊ ሁኔታውን መገንዘብ ያልቻሉ ግብዞች  ናቸው እና የዐማራው የኅልውናና የማንነት ትግል ድል በድል ላይ እየተረማመደ የኢትዮጵያን አንድነት ትንሳዔ የሚያበስርበት ቀን ሩቅ አይሆንም።
በዚህ አጋጣሚ፣ የዐማራ ልጅ የሆንክ፣ የሆንሽ፣ በወገኖቻችን ላይ የተፈጸመውና እየተፈጸመ ያለው ግፍ ሊደንቀን፣ሊያስገርመን ይገባልና ወደ ኅሊናችን ተመልሰን፣ ለምን? እንዴት በማለት ተገቢ የመፍትሔ ሀሳብ ለማፍለቅ ከወገኖቻችሁ ጎን እንድትቆሙ ትጠየቃላችሁ!
ዐማራን ከፈጽሞ ጥፋት እንታደጋለን!
የዐማራው ኅልውና መጠበቅ፣ ለኢትዮጵያ አንድነት መጠበቅ ዋስትና ነው!

No comments:

Post a Comment