Tuesday, May 30, 2017

የህወሓት ዳኛ መሰወር አነጋጋሪ ሆኗል




BBN News | የዳኛዉ መሰወር ህወሃት በሰዉ ከተጠቀመ በሗላ አዉጥቶ እንደሚወረዉር አመላካች ነዉ ተብሏል። ቢቢኤን የዳኛዉን መሰወር አስመልክቶ ቀደም ሲል የዘገበ ቢሆንም ዛሬ በጉዳዩ ላይ ተጨማሪ መረጃዎች አሉት።
የህወሓትን ፖለቲካ በዳኝነት ስም ሲያስፈጽሙ የነበሩት ግለሰብ መሰወር አነጋጋሪ ሆነ፡፡ ዳኛ ልዑል ገ/ማርያም የተባሉት እኚሁ ሰው ከስራቸው ላይ ከጠፉ ስምንት ወራት የተቆጠሩ ሲሆን፣ እስካሁን ድረስም የት እንዳሉ አይታወቅም ተብሏል፡፡ በፌደራል ከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ስምንተኛ ወንጀል ችሎት የሚያስችሉት እኚሁ ሰው፣ ያሉበት ቦታ ካለመታወቁም በላይ የተለያዩ አስተያየቶች እየተሰጡ ይገኛሉ፡፡ የገዥው ፓርቲ ፓርላማ ‹‹ዳኛው ዕድሜአቸው 57 ዓመት በመሆኑና በጤና ምክንያት መሥራት ስላልቻሉ፣ የጡረታ መብታቸው ተከብሮ ከግንቦት 1 ቀን 2009 ጀምሮ ይሰናበቱ፡፡›› የሚል ውሳኔ ማሳለፉን መረጃዎች ጠቁመዋል፡፡
ለከባድ ህክምና ኖርዌይ ናቸው የሚሉት እንዳሉ ሁሉ፣ አይ ደቡብ አፍሪካ ህክምና ላይ ናቸው የሚሉ ወገኖችም አሉ፡፡ የፌዴራል ዳኞች አስተዳደር ጉባዔ ለገዥው ፓርቲ ፓርላማ ባቀረበው የውሳኔ ሐሳብ፣ በ2009 ለተከታታይ ስምንት ወራት ‹‹በሕመም ምክንያት›› በሥራ ገበታቸው ላይ መገኘት አለመቻላቸውን ገልጿል፡፡ ሆኖም ግን ጉባዔው፣ ሰውዬው የተሰወሩት በህመም ምክንያት ይሁን አይሁን እርግጠኛ አለመሆኑም ተነግሯል፡፡ ግለሰቡ ያሉበትን ቦታ ባለቤታቸው ጭምር አያውቁም መባሉ ደግሞ ጉዳዩን የበለጠ እንቆቅልሽ አድርጎታል፡፡ ይህን ተከትሎም የገዥው ፓርቲ ፓርላማ ባካሔደው ስብሰባ ዳኛው ላለፉት ስምንት ወራት በስራቸው ላይ ባለመገኘታቸው ከስራ እንዲሰናበቱ መወሰኑን መረጃዎች ጠቁመዋል፡፡
አንዳንድ መረጃዎች እንደሚገልጹት ከሆነ ደግሞ፣ ዳኛው ምናልባት ከህወሓት ጋር ግጭት ውስጥ ገብተው በምስጢር ሳይገደሉ አልቀረም፡፡ የህወሓትን ትዕዛዝ በመቀበል በበርካታ ንጹኃን ዜጎች ላይ ፖለቲካዊ ፍርድ ሲያሳልፉ የነበሩት እኚሁ ሰው፣ ከዚህ ቀደም ካስቻሏቸው የፍርድ ቤት ጉዳዮች አንዱ፣ የቀድሞ ቅንጅት ፓርቲ ጉዳይ ይጠቀሳል፡፡ የ1997ቱን ምርጫ ተከትሎ በእነ ኢንጂነር ኃይሉ ሻውል መዝገብ በወቅቱ በርካታ ፖለቲከኞችን እስር ቤት መወርወራቸው አይዘነጋም፡፡ ከዚያ በኋላም የድምጻዊ ቴዎድሮስ ካሳሁንን ጨምሮ በርካታ ፖለቲካ ነክ መዝገቦችን ክህግ ውጪ በማስፈጸም፣ ህወሓትን ሲያገለግሉ ነበር፡፡

No comments:

Post a Comment