Friday, May 26, 2017

ታጋዮችን በማሠር የሕዝብን ጥያቄ ማቆም አይቻልም!





ታጋዮችን በማሠር የሕዝብን ጥያቄ ማቆም አይቻልም!
ሰማያዊ ፓርቲ ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ ለለውጥ ቁርጠኛ አቋም ያላቸውን ወጣት ፖለቲከኞች ያፈራ የፖለቲካ ድርጅት መሆኑ ይታወቃል፡፡ ፓርቲው የሚደርስበትን ጫናና ፈተና ተቋቁሞ የኢትዮጵያ ሕዝብ እውነተኛ የሥልጣን ባለቤት እንዲሆን በፅኑ እየታገለም ይገኛል፡፡
ሆኖም ገዥው ፓርቲ በእያንዳንዱ የፓርቲው እንቅስቃሴ ውስጥ ጣልቃ በመግባት አመራርና አባላቱን እያፈሠ ወደ እስር ቤት መወርወሩ የተለመደ ተግባሩ ሆኗል፡፡ ሕዝብ መብቱን እንዲያውቅና እንዲጠይቅ ፓርቲያችን የሚያደርጋቸውን የአዳራሽና የአደባባይ ስብሰባዎች ህገ-መንግሥቱን በመጣስ በህገ-ወጥ መንገድ ከማፈኑም በተጨማሪ የፈጠራ ክስ እየፈበረከ በሰላማዊ መንገድ በድፍረትና በቆራጥነት የሚታገሉ አባላቶቻችንን ማሰርና ማንገላታቱን ዛሬም አባብሶ ቀጥሎበታል፡፡
በአቶ ጌታቸው ሽፈራውና በአቶ ዮናታን ተስፋዬ ላይ የተላለፈው የቅጣት ውሳኔ የኢህአዴግ አገዛዝ የፍትህ ሥርዓቱን ለፖለቲካ መጠቀሚያነት እያዋለው መሆኑን በግልፅ ከማረጋገጡ በላይ ሥርዓቱ ምንም ዓይነት የመሻሻል ምልክት ማምጣት እንደማይችል ማሳያ ነው፡፡
በእነ በድሉ መንግሥቱ፣ በእነ ማሩ ዳኘው፣ በእነ ብስራት አቢ፣ በእነ እየሩሳሌም ተስፋው፣ በእነ ቴዎድሮስ አስፋው፣ በእነ ሉሉ መሠለ፣ በእነ አግባው ሰጠኝ እና በሌሎችም የክስ መዝገቦች በፓርቲያችን አመራርና አባላት እንዲሁም ጋዜጠኞችና የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ላይ የሚደርሰው እንግልት ዜጐቹ ባላቸው የፖለቲካ አመለካከት ልዩነትና ሀሳባቸውን በነፃነት የመግለፅ ህገ-መንግሥታዊ መብታቸውን በመጠቀማቸው፤ ለሀገራቸውና ለወገናቸው ከመቆርቆራቸው የተነሳ መሆኑ ግልፅ ነው፡፡
ይህ የግፍ እስር በሌሎች የፖለቲካ ፓርቲዎች አመራርና አባላት ላይም እንደሚፈፀም እናውቃለን፡፡ በሰማያዊ ፓርቲ ውስጥ ከመሥራችነት ጀምሮ እስከ አመራርነት የደረሱ አባላትን ማሳደድ የቀጠለ ሲሆን፤ ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በፊት 94 አመራርና አባላት ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በኋላ ደግሞ በአዲስ አበባ 23፣ በባህር ዳር 20፣ በኦሮሚያ 17፣ በደቡብ 26 አባላቶቻችን በእስርና በእንግልት ላይ መሆናቸውን በተለያዩ ጊዜያት መግለፃችን የሚታወስ ነው፡፡
በመሆኑም መንግሥት የሕዝብን ጥያቄ በአግባቡ ከመመለስ ይልቅ በአምባገነንነት በሕዝብና በፓርቲያችን አባላት ላይ የሚፈፅመውን የግፍ ተግባር እንዲያቆም በአፅንኦት እንጠይቃለን፡፡ “ታጋይና ምስማር ሲመቱት ይጠብቃል” እንዲሉ ታጋዮችን በማሠር የሕዝብን ጥያቄ ማቆም እንደማይቻል እያሳወቅን፤ ሰማያዊ ፓርቲም ሕዝብ የስልጣን ባለቤት እስኪሆን ድረስ ትግሉን አጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን እንገልፃለን፡፡
“ኢትዮጵያ በነፃነትና በክብር ለዘላለም ፀንታ ትኖራለች!”
ግንቦት 18 ቀን 2009 ዓ.ም.
አዲስ አበባ

No comments:

Post a Comment