Thursday, May 18, 2017

በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒዬም ሜዲካል ኮሌጅ ዲን በማዕከላዊ እየተሰቃየ ነው



ተመራማሪ የሺወንድም ሹምዬ ከጎንደር የመጣ ዘመድ አሳድረሃል በሚል በማዕከላዊ እየተሰቃየ ነው፤ Brannamedia

አገዛዙ የዐማራ ወጣቶችን፣ ምሁራንና ፖለቲከኞችን በግፍ ማሰር ቀጥሎበታል፡፡ በየትኛውም አካባቢ የሚኖሩ የዐማራ ተወላጆች ሰበብ አስባብ እየተፈለገ በጂምላ እየታሠሩ በማዕከላዊ የቶርቸር ሰለባ ሆነዋል፡፡
ወጣቱ ምሁር የሺወንድም ሹምዬ በወያኔ የቶርቸር ሰለባ ከሆኑ የዐማራ ምሁራን አንዱ ነው፡፡ ጥር 12 ቀን 2009 ዓ.ም ጠዋት ከቤተ ክርስቲያን ደርሶ ሲመለስ በትግሬ ደኅንነቶች ተይዞ ወደ ማዕከላዊ ከገባ አራት ወራት አልፈውታል፡፡ ከአራት ጊዜ በላይ ፍርድ ቤት ቀርቧል፤ እስካሁን በማዕከላዊ ቶርቸር እየተፈጸመበት ነው፡፡
ተመራማሪ የሺወንድም ሹምዬ በአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ በሜዲካል ቴክኖሎጅ የትምህርት ዘርፍ በመጀመሪያና በሁለተኛ ዲግሪ የተመረቀ ሲሆን በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒዬም ሜዲካል ኮሌጅ ዲን በመሆን ያገለግል ነበር፡፡ የሺወንድም በበርካታ ዓለም አቀፍ የትምህርት ጆርናሎች ላይ ጥናታዊ ጽሑፎችን ያሳተመ ሲሆን  በአሜሪካን አገር ከሚገኘው ሚቺጋን ዩንቨርሲቲ ጋር በመተባበር አንድ ለአገር የሚጠቅም ጥናት በማጠናቀቅ ላይ ነበር፡፡ ወጣቱ ተመራማሪ ወደ አሜሪካን ተጉዞ በሚቺጋን ዩንቨርሲቲ ጥናቱን ያቀረበ ሲሆን መጠናቀቅ የሚገባቸውን ጉዳዮች ለመጨረስ ወደ አገር ቤት በተመለሰ በ15ኛ ቀኑ ወደ ማዕከላዊ ገብቶ የቶርቸር ሰለባ የሆነው፡፡
ወጣቱ ተመራማሪ በማዕከላዊ ቀርቦበት የነበረው ክስ ‹‹ለዐማራ ታጋዮች የዩንቨርሲቲ ምግብ እንዲያገኙ አድርገሃል›› የሚል ቢሆንም የሺወንድም የተማሪዎች ዲን እንጅ የምግብ ክፍል ኃላፊ አለመሆኑን በማስረዳቱ ክሱም እንደማያስኬድ ሲታወቅ የክስ ጭብጡ ተቀይሯል፡፡ በተቀየረው ክስ ‹‹ከጎንደር የመጣ አሸባሪ አሳድረሃል›› በሚል አዲስ ፋይል ተከፍቶበት በቶርቸር መካከል ፍርድ ቤት እንደሚመላለስ ለማወቅ ተችሏል፡፡
ወጣት ተመራማሪው የሺወንድም ከጎንደር የመጣ አብሮ አደግ መምህር ጓደኛውን የጥምቀት ዕለት አግኝቶት ከቤቱ አብረው ያደሩ ሲሆን መምህር ጓደኛውም እስካሁን አብሮ በማዕከላዊ በስቅይት ላይ ነው፡፡ የሺወንድምን ከእናቱ፣ ከእህቱና ከባለቤቱ ውጭ ማንም ሰው መጠየቅ አይችልም፡፡ በአራት ወራት ውስጥ በአማራነቱ ብዙ ስቃይና ሥነ ልቦናዊ ጉዳት ደርሶበታል፡፡ ከሚችጋን ዪንቨርሲቲ ጋር እየሠራው የነበረው ጥናታዊ ጽሑፍም ተቋርጧል፡፡

No comments:

Post a Comment