Tuesday, May 2, 2017

ሕገ-መንግስቱን በሚጥስ አዋጅ የኦሮሚያን “ሕገ-መንግስታዊ ልዩ ጥቅም” ማስከበር አይቻልም! ስዩም ተሾመ

   



ካለፈው ዓመት ጀምሮ በአዲስ አበባ እና ኦሮሚያ ዙሪያ የተለያዩ ፅሁፎችን አውጥቼያለሁ። “ማስተር ፕላን፡ የችግሩ መነሻ እና መድረሻ” በሚለው ፅሁፍ የአዲስ አበባ ከተማ ገና ከአመሰራረቷ ጀምሮ የኦሮሞን ሕዝብ መብትና ተጠቃሚነት ያላረጋገጠች መሆኗንና ማስተር ፕላኑ ደግሞ ይሄን የሚያስቀጥል ስለመሆኑ፣ “የአዲስ አበባን ማስተር ፕላን ማቋረጥ ስህተትን እንደ መሳሳት ነው” በሚለው ፅሁፍ ከአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ጋር ተያይዞ ለተከሰተው ችግር ዘላቂ መፍትሄ መስጠት የሚቻለው የችግሩን ዋና መንስዔ መለየት ሲቻል እንደሆነ፣ በመቀጠል “ኦሮሚያን ለአመፅ፣ አዲስ አበባን ለቆሻሻ የዳረገች አንቀፅ” በሚል ርዕስ ባወጣሁት ፅሁፍ ደግሞ የኦሮሚያ ሕዝብ እና የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎች መብትና ተጠቃሚነት በዘላቂነት ሊረጋገጥ የሚችለው የሕገ-መንግስቱ አንቀፅ 49(5) ተግባራዊ ሲደረግ እንደሆነ በዝርዝር ገልጬያለሁ።
ከላይ በተጠቀሱት ሦስት ፅሁፎች በአዲስ አበባ እና በኦሮሚያ ክልል መካከል ያለው ግንኙነት ከጭፍን ደጋፍና ተቃውሞ በፀዳ መልኩ እንዲመራ እና የክልሉ ሕዝብና የከተማዋ ነዋሪዎች መብትና ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ፣ ለዚህ ደግሞ በሕገ-መንግስቱ አንቀፅ 49(5) አስፈላጊው የሕግ አዋጅ እና የአፈፃፀም መመሪያ መዘጋጀት አለበት በሚል መርህ ላይ የተመሰረቱ ናቸው። ስለዚህ፣ የኦሮሚያ ክልል በአዲስ አበባ ላይ ያለው ሕገ-መንግስታዊ ልዩ ጥቅም የሚያስከበር አዋጅ መውጣት አለበት እያልኩ በፅሁፎቼ ተከራክሬያለሁ። በጉጉት ስጠብቀው የነበረው ረቂቅ አዋጅ ግን እንዲህ ቅስሜን ይሰብረዋል ብዬ አልጠበቅኩም ነበር።
በመሰረቱ፣ በሀገር ወይም ክልል ደረጃ ሰላም፥ ልማትና ዴሞክራሲ ለማረጋገጥ በሚል የሚወጡ አዋጆች፣ ደንቦችና መመሪያዎች በምንም መልኩ ቢሆን ሕገ-መንግስታዊ መርሆችንና ድንጋጌዎችን መፃረር የለባቸውም። ሕገ-መንግስቱ በማንኛውም አካል ቢሆን ለሚወሰዱ የለውጥ እርምጃዎች እንደ መነሻ ሆኖ ያገለግላል የሚል እምነት አለኝ። “ሕገ-መንግስቱ በራሱ ክፍተቶች ስላሉበት አንቀበለውም” የሚሉ ወገኖች መኖራቸው እርግጥ ነው። ነገር ግን፣ “በሕገ-መንግስቱ ውስጥ የሚስተዋሉ ክፍተቶችን ራሱ ሕገ-መንግስቱ ላይ በተደነገገው አግባብ መሰረት መቀየርና ማሻሻል ይቻላል” የሚል ፅኑ አቋም አለኝ።

No comments:

Post a Comment