Monday, May 22, 2017

“ባንዳ እና ዘረኛ” (ይድነቃቸው ከበደ)



“ባንዳ እና ዘረኛ”

[[ ዶ/ር ቴዎድሮስ እንዳይመረጡ በአብዛኛው የሚደረገው ተቃውሞ በሥራቸው እንጂ ‘በብሔራቸው’ እንዳልሆነ ግልጽ ነው። የእሳቸውን ‘ብሔር’ መሠረተ አድርጉ የሚቃወም ቢኖሩ ያ ሰው ዘረኛ ነው። ለዘረኛ ደግሞ ‘ተክላይ’ ሲሆን የሚወገዝ፣ ‘ከበደ’ ከሆነ ደግሞ የሚወደስበት ምን አይነት የተለየ ሚዛን የለም ! ]


የዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም የምረጡኝ ዘመቻ ተከትሎ በሃገር ውስጥ እና በውጪ የተለያዩ እንቅስቃሴዎች እየተደረጉ ነው። እሳቸውን በመደገፍ እና በመቃወም የሚደረገው እንቅስቃሴ በራሱ የሚበረታታ እና የሚደገፍ ነው። ይህ ማለት ግን በዘረኝነት እና በባንዳነት ደረጃ እዚህ እና እዚያ መስመር አስምሮ የሚደረገው ሰጣገባ ተገቢ ነው እያልኩ እንዳልሆነ ታሳቢ ይደረግልኝ።በምረጡኝ ዘመቻ ተፉካካሪ ባለበት አንዱን ከሌላ ማበላለጥ የምርጫ አንድ አካል ነው። እርግጥ ነው እሳቸው የሚወዳደሩት ከውጪ ሃገር ዜጋ ጋራ ነው። ይሁን እንጂ አብዛኛው የእሳቸውን መመረጥ የማይደግፍው ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖምን ከእንግሊዛዊ ዴቪድ ናባሮ ጋር በማወዳደር አይደለም።ዶ/ር ቴዎድሮስ በሃገር ውስጥ በሰሩት ሥራ ነው! ሥራቸው ደግሞ ምን እንደነበረ በእሳቸው ላይ ይቀርብ የነበረው ተቃውሞ እና ትችት መልስ ብሎ መመልከት ተገቢ ነው ። አብዛኛው ትችች እና ተቃውሞ እራሱን የቻለ በቂ ምክንያት አለዉ ! ይህን አሳማኝ ምክንያት ጠንቅቆ ካለመረዳት ወይም ለመረዳት አለመፈለግ ካልሆነ በስተቀር ።

እውነታው ይህ ሆኖ እያለ ፣ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም ለWHO የሚያደርጉት የምረጡኝ ዘመቻ መቃወም በዘረኛነት እና በባንዳነት የሚያስፈጅ መሆኑ ሊረሳ የማይችል ትዝብት ውስጥ ይከታል። በተለይ ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም ደጋፊ ነን የሚሉ እራሳቸውን በዘውግ/በሔርተኝነት አጥረው እነሱን ከሚመስሉ ጋር ህብረት ፈጥረው ፣ ለፈጠሩት ህብረት ዘብ የሚቆሙ የጎሳ ፖለቲካ አራማጆች ናቸው። ይህ ከሆነ ደግሞ እነሱ እንደሚሉት ለዘረኛነት የሚቀረበው ማነው ?! ሌላው ደግሞ ለእኛ ለኢትዮጵያዊን በታሪካችን እንደ ሃገር ለባንዳነት ማን ይቀርብ ነበር ?! መልሱ ቀላል ነው። ነገር ግን ከትላንት የጋራ ታሪካችን በጎውን ነገር በይበልጥ አጎልብተን ፣ ስህተት የነበረውን ትምህርት ወስደንበት ዛሬ ላይ ተሽለን መገኘት የሁላችንም የጋራ ኃላፊነት ነው። ዘረኝነትን በመጠየፍ ፣ከዚህ ቆሻሻ ሃስተሳሰብ በመጽዳት የተሻለ ሆኖ መገኘት ለሥጋም ለነብስም እረፍት
ነው።

እባካችሁን ! እናተ የዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም ደጋፊ ነን ባዮች፣ የሁላችንም በሆነችው ሃገራችን ላይ ዘረኝነትን በይፋ በማወጅ አንዱን ከሌላው ጋር ለመለያየት እና ለመከፋፈል መጥፎ መርዛቸውን አትርጩ ! ዶ/ር ቴዎድሮስ እንዳይመረጡ በአብዛኛው የሚደረገው ተቃውሞ በሥራቸው እንጂ ‘በብሔራቸው’ እንዳልሆነ ግልጽ ነው። ምን አልባት የእሳቸውን ‘ብሔር’ መሠረተ አድርጉ የሚቃወም ቢኖሩ አዎ ለእኔ ያ ሰው ዘረኛ ነው።
ለዘረኛ ደግሞ ‘ተክላይ’ ሲሆን የሚወገዝ፣ ‘ከበደ’ ከሆነ ደግሞ የሚወደስበት ምን አይነት የተለየ ሚዛን የለም።ሁለቱም ቆሻሻ የሆነውን ዘረኝነት መነሻ በማድረጋቸው ሊመከሩ ተዉ ይሄ ነገር አይጠቅምም ሊባሉ ይገባል። ምክር አልሰማ ያሉ እንደሆነ “ጨው ለራስ ስትል ጣፍጥ አለበለዚያ….” መባሉ ለምን ሆነና ። ወደ ጉዳያችን ስመለስ ዶ/ር ቴዎድሮስ እንዳይመረጡ መቃወም አንዳንዶቹ እንደ ሚሉት ‘መርህ’ አልባ አይደለም ! የዜጎች ሰብዓዊ እና ዲሞክራሲያዊ መብት መሠረት ያደረገ ነው። ይህ ደግሞ ተቃውሞው እውነተኛ ‘መርህ’ እንዳለው ማሳያ ነው። መርህ ሲያምች የምንቀበለው ሣይሆን ሲቀር የምንተወው ተራ ነገር አይደለም። መርህ መሰረታዊ የሆነውን ሃቅ የሚደግፍ እንጂ በፍጹም የሚጻረር አይደለም፣ መርህ ፍርደ ገምድልነትን አይቀበለም ። መርህ አንድን ነገር ከሌላው
ተመዝኖ የሚደገፍበት ትክክለኛ ሚዛን ነው።

ሃሳቤን ሳጠቃልል ኢትዮጵያዊ ማንነት ክፍ አድርገን በኢትዮጵያዊነታችን እንድመቅ ፣ በጎሳ(በብሔር)
መከፋፈሉ ይብቃ! ከዚህ ቀደም እንደገለጽኩት ዘረኝነትን አጥብቄ እቃወማለሁ! እኔ በግሌ የሰው ወገን የሆን ሁሉ አንድ ነን ብዬ አምናለሁ ! የራሴን ምክንያታዊ ሃሳብ ለማቅረብ ወይም የሌላውን ሃሳብ በአመክንዮአዊ አመለካከት ለመሞገት፤ እኔ እና የእኔ ቤተሰቦች የምንናገረው ቋንቋ ፣ የምንከተለው ሐይማኖት፣እንዲሁም የቆዳ ቀለማችን ፈጽሞ መመዘኛ አይሆነኝም። አንድን ሰው በሃሳቡ ወይም በሥራው ለመቃወም ሆነ ለመደገፍ የነገሩ ጠቃሚነት ወይም ጎጂነት ብቻ መስፈርቱ ሆኖ ያገለግለኛል ። ዘረኝነት “ከቀለም ወይም ከዝርያ ልዩነት የተነሣ ራስን የተሻለ አድርጎ በመገመት ሌላውን መናቅ መጨቆን የበታች አድርጎ ማየት” እንደሆነ ይነገርለታል፤እንዲህ አይነቱ አጸያፊ ነገር የምጠየፈው ቆሻሻ ነው። ግን ! ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም ለWHO የሚያደርጉት የምረጡኝ ዘመቻ መርህን መሰረት በማድረግ በምክንያት መቃወም “ባንዳ እና ዘረኛ ” ካስባለ አጋጣሚው መልካም ነው ። አዎ እሳቸው ለWHO የሚያደርጉት የምረጡኝ ዘመቻ እኔ አልደግፍም !

(ይድነቃቸው ከበደ)

No comments:

Post a Comment