Tuesday, May 2, 2017

የአዲስ አበባ የታክሲ ሾፌሮች አመጽ ቀስቃሽ የታክሲ ጥቅሶችን በአስቸኳይ እንዲያነሱ ተነግሯቸዋል ተባለ


የአዲስ አበባ የታክሲ ሾፌሮች አመጽ ቀስቃሽ የታክሲ ጥቅሶችን በአስቸኳይ እንዲያነሱ ተነግሯቸዋል ተባለ
አመጽ ቀስቃሽ የታክሲ ጥቅሶችን በአስቸኳይ እንዲያነሱ ተነግሯቸዋል ተባለ – ካለፈው ሳምንት ሚያዚያ 11 ጀምሮ ለተከታታይ ቀናት ስቴዲየም በሚገኘው የመንገዶች ባለሥልጣን አዳራሽ በፈረቃ ከመንግሥት ሰዎች ጋር እየተወያዩ የሚገኙት ባለ ኮድ አንድ የታክሲ ሾፌሮች በቁጥር ከ5ሺ ይልቃሉ፡፡
ውይይቱ የተዘጋጀው በአዲስ አበባ መንገዶች ባለሥልጣን ሲሆን አዲስ የወጣውን የመንገድ ትራንስፖርት ትራፊክ መቆጣጠሪያ ደነብ ቁጥር 395/2009 ከሚመለታቸው አካላት ጋር ለማስተዋወቅ የተሰናዳ እንደሆነ ተመልክቷል፡፡ ኾኖም መድረኩ ቅሬታና የዓመታት ብሶት ገንፍሎ በወጣባቸው የታክሲ ባለንብረቶችና ሾፌሮች ቁጥጥር ሥር ወድቋል ለማለት ያስደፍራል፡፡
በሰባቱ ቀናት ስብሰባ የመናገር እድል የተሰጣቸው ተወያዮች መንግሥትን ክፉኛ የተቹ ሲሆን የብዙዎቹ አቤቱታ “መንግሥት እኛን እንደተቃዋሚ ፓርቲ እንጂ እንደ አገልግሎት ሰጪ አድርጎ አይመለከተንም” የሚል ነው፡፡
“እኛን ከመክሰሳችሁ በፊት ራሳችሁን ብትፈትሹ ጥሩ ነበር” ያሉ አንድ የታክሲ ባለንብረት “በአገሪቱ ሙስና የተፈለፈለው ከናንተ ቢሮ አይደለምን?” ሲሉ ጉቦ የማይጠይቅ ትራፊክ በአዲስ አበባ በተለይ ደግሞ በኦሮሚያ ፈልጎ ማግኘት እንደማይቻል የ15 ዓመት ልምዳቸውን በመጥቀስ አብራርተዋል፡፡
በየቀኑ ከ10 እስከ 20 የሚሆኑ ታዳሚዎች ሐሳባቸውን እንዲሰጡ በተደረገበት በዚህ ዉይይት ፖለቲካዊ መንፈስ የነበራቸው ድምጾችም ተሰምተዋል፡፡
“በ97 ምርጫ ዋዜማ ለሰልፈኞች ነጻ ትራንስፖርት ሰጥታችኋል ብላችሁ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በበጎ እንደማታዩን ይገባናል፡፡” ያሉ ሌላ ባለንብረት ንግግራቸው በጭብጨባ ከተቀቋረጠ በኋላ ሐሳባቸውን የቀጠሉ ሲሆን ሁሉም ዘርፎችን መንግሥት ባለው አቅም ሁሉ እየደጎመ ታክሲን ቸል ያለበት ምክንያት ከዚሁ የጠላትን ስሜት የመነጨ እንደሆነ እንደሚያምኑ ተናግረዋል፡፡ “ለመንግሥት ሠራተኛ በሰበብ አስባቡ ደመወዝ ትጨምራላችሁ፣ የኛን ታሪፍ ለማሻሻል ግን አንድ ቀን እንኳ አስባቸሁ ታውቃለችሁ?” ሲሉ ጠይቀዋል፡፡
በዚህ አስተያየት የተበረታቱ ሌላ የታክሲ ባለንብረት የመናገር እድሉን ያገኙ ሲሆን “እዚህ አገር በሕዝብም በመንግሥትም እየተጠላን፣ ዘላለም እየተረገምን የምንሠራ እኛ ታክሲዎች ነን፡፡” ካሉ በኋላ “ተመስግነን አናውቅ፣ አትርፈን አናውቅ፣ ሕይወታችን ተለውጦ አያውቅ፡፡ እስቲ ከታክሲ ሥራ ተነስቶ እዚህ ደረሰ የተባለ ሰው ንገሩኝ” ሲሉ ታዳሚውን ጠይቀዋል፡፡ “እኔ ንግግሬን በሌላ አትውሰዱብኝና እኛ ታክሲዎች ጧት ተነስተን ባንሠማራ እኮ አገሪቷም ትቆማለች፡፡ መንግሥትም የሚሽመደመድ ይመስለኛል፣ ከናንተ ውስጥ ግን ይህን የሚያስብ ያለ አይመስኝም” ሲሉ ሐሳባቸውን ቋጭተዋል፡፡ ታዳሚውም በጭብጨባ ድጋፉን ገልጾላቸዋል፡፡
” ለመሆኑ የመኪና መለዋወጫ ዋጋን ታውቃላችሁ? ስፔርፓርት ስንት ነው?” በሚል ጥያቄ የሰነዘሩ ሌላ የታክሲ ባለንብረት፣ “ዛሬ አንድ ስፖኪዮ ቢሰበር ስንት ብር እንደሚያስወጣን ብታውቁ ደፍራችሁ እዚህ ባልጠራችሁን ነበር” ሲሉ ጠንከር ያለ ሀሳብ ሰጥተዋል፡፡ “ለነገሩ መንግሥት ሕዝብን መስማት ካቆመ ስለቆየ በናንተ አልፈርድባችሁም፤ እኛ ትዝ የምንላችሁ እኮ አድማ ስንመታ ብቻ ነው፤ ጃንሆይንም ታክሲ ነው ያወረዳቸው፣ ታሪክ ብታውቁ ደፍራችሁ እዚህ አትጠሩንም ነበር” ሲሉ አስተያየት የሰጡ አባት በመድረኩ አስተናባሪዎች ተግሳጽ ደርሶባቸዋል፡፡
” እዚህ መድረክ ስላገኘን ብቻ እንዳመጣልን መናገር ተገቢ አይመስለንም፡፡ ታክሲዎች ለሕዝብ አገልግሎት እንዲሰጡና ተጠቃሚ እንዲሆኑ የተለያዩ ጥረቶች እየተደረጉ ነው፡፡ በሚሊዮን የሚቆጠር ገቢ ይቅርብኝ ብሎ ያለቀረጥ ከአንድ ሺ በላይ ታክሲዎች ወደ አገር ቤት እንዲገቡ የተደረገውም በዚህ ምክንያት ነው፡፡ የትርፍ ህዳጋችን መጨመር አለበት፣ ሥራው በሚፈለገው መልኩ እያተረፈን አይደለም የሚለው ተገቢ ጥያቄ ነው፡፡ እኛ ካመጽን አገር ትቆማለች ማለት ግን ኃላፊነት የጎደለው ንግግር ነው፤ መንግሥት እናንተ የምታገኙት ትርፍ ወቅቱን ያገናዘበ እንዳልሆነ ይረዳል፡፡ ለዚህም ጥናት እያደረገ ነው፡፡ በዚህ ዓመት የታሪፍ ማሻሻያ ለማድረግ እየሠራ ነው፡፡” የሚል ምላሽ ከመድረክ መሪዎች በአንዱ ተሰጥቷል፡፡

No comments:

Post a Comment