Monday, June 20, 2016

የክቡር ሚኒስትሩ ሹፌር በጠዋት ከቤታቸው ሊወስዳቸው መጣ]


  • እንቅልፍ አልተኙም እንዴ ክቡር ሚኒስትር?
  • ምን እንቅልፍ አለ?
  • ለምን አልተኙም?
  • ግጥሚያውን ሳይ ነዋ፡፡
  • አሸነፍን ተሸነፍን?
  • እኛ እኮ የለንበትም፡፡
  • ከተፋላሚዎቹ አንደኞቹ እኛ አይደለን እንዴ?
  • ከመቼ ጀምሮ ነው እኛ አውሮፓዊ የሆነው?
  • ስለምን እያወሩ ነው ክቡር ሚኒስትር?
  • ስለአውሮፓ ዋንጫ ነዋ፡፡
  • እየቀለዱ ነው ክቡር ሚኒስትር?
  • የምን ቀልድ ነው?
  • ያመሹት እኮ ሥራ ላይ መስሎኝ?
  • በቃ በዊኬንድም አትረፉ ነው የምትሉን፡፡
  • አይ ያው ዊኬንዱ የሚታረፍበት አልነበረም ብዬ ነዋ፡፡
  • ዊኬንዱማ ሰላማዊ ነበር፡፡
  • ሁሉን ነገር እርግፍ አድርገው ትተውታል ማለት ነው?
  • ሳትራገፍ ማራገፍ አይሻልም ብለህ ነው?
  • እና ምንም ወሬ አልሰሙም?
  • ያው የቤተሰብ ወሬማ ሰምቻለሁ፡፡
  • ኧረ ስለጦርነቱ፡፡
  • ስማ ጦርነት እኮ ቆሞ አያውቅም፡፡
  • የትኛው ጦርነት?
  • ከድህነት ጋር የሚደረገው ጦርነት፡፡
  • ምን አሉኝ?
  • ከሙስናና ከኪራይ ሰብሳቢነት ጋር የሚደረገው ጦርነት፡፡
  • ማሞ ሌላ መታወቂያው ሌላ አሉ፡፡
  • ከመልካም አስተዳደር ጋር የሚደረገው ጦርነት፡፡
  • ከእነርሱ ጋ ግን ተዋግታችሁ ታውቃላችሁ?
  • ሌት ተቀን ነዋ፡፡
  • ታዲያ በየጊዜው ለምን እየጨመሩ ይሄዳሉ?
  • አየህ አጠቃቅህ ስትራቴጂካዊ መሆን አለበት፡፡
  • እንዴት ሆኖ?
  • በጣም እስኪያድጉ ዝም ብለህ ትመለከታቸዋለህ፡፡
  • ከዛስ?
  • ከዛማ ሳያስቡት ባንዴ ትገነድሳቸዋለህ፡፡
  • ግን መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡
  • ምን ዓይነት ጥንቃቄ?
  • እነሱ እንዳይገነድሷችሁ፡፡
  • አንተን ራስህን መገንደስ ነበር፡፡
  • ለማንኛውም እኔ የምልዎት ጦርነት ሌላ ነው፡፡
  • የምን ጦርነት ነው?
  • ከኤርትራ ጋር የነበረው ጦርነት?
  • ምን?
  • ምንም አልሰሙም?
  • የምን ጦርነት ነው?
  • የኢትዮጵያ ሠራዊት ከኤርትራ ሠራዊት ጋር ተጋጭቶ ነበር፡፡
  • በምን ምክንያት?
  • እሱን ነበር ልጠይቅዎት የነበረው፡፡
  • እሱማ አይነገርም፡፡
  • ለምን?
  • ወታደራዊ ሚስጥርን መጠበቅ አለብህ፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር ዋናው ችግርዎት እኮ ይኼ ነው፡፡
  • ምንድን ነው?
  • የማያውቁትን ነገር እንደሚያውቁ ሲያወሩ ነዋ፡፡
  • የግጭቱን ችግርማ አውቀዋለሁ፡፡
  • እሺ ምንድን ነው?
  • ምቀኝነት፡፡
  • ምን ማለት ነው ክቡር ሚኒስትር?
  • በቃ በአገራችን ዕድገት የከፋው የኤርትራው መሪ ተመቅኝቶ ነው ውጊያ የጀመረው፡፡
  • አይ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • በቃ ከዚህ ሌላ ምንም ምክንያት የለውም፡፡
  • ድንቄም ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ምን አልክ?
  • ድንቅ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ለመሆኑ ፍልሚያውን ማን አሸነፈ?
  • አቻ ነው የወጣነው፡፡
  • እንዴት ማለት?
  • መንግሥት ተመጣጣኝ ዕርምጃ ወስጃለሁ ነው ያለው፡፡
  • ለነገሩ ያን ምቀኛ መሪ ምን ማድረግ እንዳለብን አውቃለሁ፡፡
  • ምን ሊያደርጉት?
  • ቂጡን በሳንጃ መውጋት!
[ክቡር ሚኒስትሩ ጸሐፊያቸው ጋ ደወሉ]
  • ምን ሆነሽ ነው ሥራ ያልመጣሽው?
  • ችግር ገጥሞኝ ነው፡፡
  • የምን ችግር?
  • ሐዘን ላይ ነኝ፡፡
  • ቻንድራ ሞተ እንዴ?
  • ኧረ አልሞተም፡፡
  • ታዲያ ዛራ ሞተች?
  • ዘሩ ነው የሞተው፡፡
  • ማነው ዘሩ?
  • ጐረቤቴ ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ምን ሆኖ ነው የሞተው?
  • ዱርዬዎች ነው የገደሉት፡፡
  • ለምን ገደሉት?
  • ማጅራት መቺዎች ናቸዋ፡፡
  • ባለሀብት ነው እንዴ?
  • ባለሀብት ቢሆንማ በቪ8 ነበር የሚሄደው፡፡
  • ታዲያ እሱ በምንድን ነው የሚሄደው?
  • በቪ11፡፡
  • ቪ11 ካለውማ ከቪ8 ስለሚበልጥ ከፍተኛ ባለሀብት ነበር ማለት ነው?
  • ቪ11 እኮ ማለት በሁለት እግሩ ነው የሚሄደው ለማለት ነው፡፡
  • መቼም የማታመጪው ነገር የለም?
  • ክቡር ሚኒስትር ይኼ የዝርፊያ ጉዳይ ግን ቢታሰብበት መልካም ነው፡፡
  • እንዴት ማለት?
  • ይኸው ይኼኛው እኮ በ15 ቀናት ውስጥ ሁለተኛው ሞት ነው፡፡
  • አንቺ ሰፈርሽ ሞቃዲሾ ነው እንዴ?
  • ክቡር ሚኒስትር የሥራ አጡ ቁጥር እየጨመረ መጥቶ ማጅራት መምታት ሥራ ከሆነ ሰነባበተ፡፡
  • አሁን እዚህ አገር ላይ ሥራ አጣሁ የሚል ሰው ነው የሚገርመኝ?
  • ምኑ ነው የሚገርምዎት?
  • አገሪቷ በፍጥነት እያደገች ባለችበት በዚህ ወቅት ገና ከቤትሽ ስትወጪ አይደል እንዴ ሥራ የሚያገኝሽ?
  • አገር ቀየሩ እንዴ ክቡር ሚኒስትር?
  • ማን? እኔ?
  • ታዲያ ስለየትኛው አገር ነው የሚያወሩት ብዬ ነዋ?
  • እኔ ወሬ አልወድም፣ ሥራ ብቻ ነው የምወደው፡፡
  • ለነገሩ ክቡር ሚኒስትር እነዚህ ማጅራት መቺዎች የእርስዎ አለቃ ለመሆን ስማቸው ላይ ሚኒስትር የሚለው ብቻ ነው የጐደላቸው፡፡
  • ማን ነው ስማቸው?
  • ጠቅላይ፡፡
  • ወሬማ ማን ብሎሽ?
  • ለማንኛውም የሚዘርፉትም ተደራጅተው ነው ተብሏል፡፡
  • በምን?
  • በአነስተኛና ጥቃቅን!
[ክቡር ሚኒስትሩ አማካሪያቸውን አስጠሩት]
  • የተመደበልንን በጀት እንዴት አየኸው?
  • ክቡር ሚኒስትር ከፍተኛ በጀት ነው፡፡
  • ጥሩ ነዋ፡፡
  • ምን ጥሩ ነው?
  • እንዴት ማለት?
  • ባለፈው ከተመደበልን በጀት 30 በመቶውን ብቻ ነው እኮ የተጠቀምነው፡፡
  • ከባለፈው ስህተታችን ትምህርት ወስደናላ፡፡
  • የባለፈው ችግራችን እኮ የአቅም ማነስ ነው፡፡
  • እኮ አሁን አቅማችንን እናጠናክራለና፡፡
  • አቅማችን እኮ ምንም አልተጠናከረም፡፡
  • የእኔ አቅም ተጠናክሯል፡፡
  • እንዴት ክቡር ሚኒስትር?
  • በቅርቡ የጭስ አልባ ኢንዱስትሪውን ለመቀላቀል ወስኛለሁ፡፡
  • አልገባኝም?
  • በቃ ባለአምስት ኮከብ ሆቴል ለመሥራት አቅጃለሁ፡፡
  • ምን?
  • ጥራቱን የጠበቀ ሆቴል ነው የምገነባው፡፡
  • ከየት አምጥተው?
  • ስነግርህ? ከሚቀጥለው በጀት ዓመት ተመላሽ የምናደርገውን ገንዘብ አይኖርም፡፡
  • ሌላስ?
  • በግሌ ያሉኝን አምስት ቤቶችም ቢቻል ከእጥፍ ለመጨመር አስቤያለሁ፡፡
  • ካልተቻለስ?
  • ቢያንስ አንድ ሦስት መጨመር አለብኝ፡፡
  • እ…
  • ከዛም ባለፈ ወደ ኢንዱስትሪ ዘርፉ መግባት አለብኝ፡፡
  • ምን አሉኝ?
  • መንግሥት ይኼን ሁሉ የኢንዱስትሪ ፓርክ የገነባው እኮ እኛ እንድንገባበት ነው፡፡
  • ኧረ የግል ባለሀብቶች እንዲገቡበት ነው?
  • እኛ አርዓያ መሆን አለብን፡፡
  • እንዴት ማለት?
  • በተደጋጋሚ ባለሀብቶች እንዲገቡ ተጨቃጭቀን አሻፈረኝ ስላሉ እኛ ገብተን እናሳያቸዋለን፡፡
  • ለመሆኑ ገንዘቡን ከየት ነው የሚያመጡት?
  • ለጋሽ አገሮች ለመንግሥት ለዘላቂ ልማት ፕሮግራሞች በጀት መድቧል፡፡
  • አዎን ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • እኔም ለፕሮጀክቶቼ ከመንግሥት በጀት እመድብላቸዋለሁ፡፡
  • የእርስዎ ፕሮጀክቶች ምንድን ነው የሚባሉት?
  • የሚኒስትሩ የዘላቂ ልማት ፕሮግራሞች!
[ክቡር ሚኒስትሩ በፓርቲያቸው ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ እየተገመገሙ ነው]
  • ክቡር ሚኒስትር ምን ይሻልዎታል?
  • ልማት ነው የሚሻለኝ፡፡
  • የእርስዎ ሌብነት እኮ አሳፋሪ ሆነ፡፡
  • እኔ የሚገርመኝ እናንተ የማትሰርቁ ነው የምትመስሉት?
  • የእርስዎ ግን ባሰ፡፡
  • ምን ማስረጃ አላችሁ?
  • ይኸው በአሥሩም ክፍለ ከተማ በስምዎት ሕንፃ አለዎት፡፡
  • ቢኖረኝስ?
  • በስምንት ክፍለ ከተማ ደግሞ የመኖሪያ ቤቶች አልዎት፡፡
  • ብርቅ ነው ታዲያ? ማን የሌለው አለ?
  • ለልማቱ ፀር እየሆኑ ነው፡፡
  • ከዚህ በላይ ልማት ምን አለ?
  • እርስዎ እኮ አስለሚ እንጂ አልሚ አይደሉም፡፡
  • እንግዲህ ቃላት እየሰነጣጠቃችሁ አታደናግሩን፡፡
  • ምን ማለት ነው?
  • እኔ እስከሚገባኝ የእኔ መልማት የልማታዊ መንግሥት መገለጫ ነው፡፡
  • መንግሥት የግሉ ዘርፍ በልማቱ ውስጥ እንዲሳተፍ እኮ ነው የሚፈለገው፡፡
  • እኔም እኮ በግሌ ነው እያለማሁ ያለሁት፡፡
  • እርስዎ ግን የመንግሥት ባለሥልጣን ነዎት፡፡
  • የግል ባለሀብቱ እምቢ ሲል እኮ ነው አርዓያ መሆን አለብኝ ብዬ የተነሳሁት፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር የእርስዎ ሙስና ከመጠን ያለፈ ሆኗል፡፡
  • እኮ እኔ ምን ላድርግ?
  • በቃ እርስዎ ላይ ዕርምጃ መወሰድ አለበት፡፡
  • ኧረ እኔ በቃ ግለ ሒስ አደርጋለሁ፡፡
  • እርሱን ካደረገ ችግር የለውም፡፡
  • ሙስና በቃ ሱስ ሆኖብኛል፡፡
  • ከዚህ ሱስዎት መላቀቅ አለብዎት፡፡
  • ይቻላል?
  • በሚገባ፡፡
  • እስቲ ራሳችሁ ተላቃችሁ አሳዩኝ፡፡
  • ምን ዓይነት አስቸጋሪ ሰው ነዎት?
  • ለመጨረሻ ጊዜ የምናገረው ነገር አለ፡፡
  • ምንድን ነው እሱ?
  • ሙስና ውስጤ ነው

No comments:

Post a Comment