Wednesday, June 8, 2016

መድረክ ንጉሣዊ ነው እንዴ?

መድረክ ንጉሣዊ ነው እንዴ?

ለመድረክ ቅርብ የሆነ አንድ ወዳጄ የመድረክን የእሁድ ግንቦት 28/2008 ጉባዔን አስመልክቶ የነገረኝ ነገር መድረክ ንጉሣዊ ነው እንዴ? የሚል ጥያቄ እንዳነሳ አድርጎኛል፡፡ መቼም በመድረክ ስም ፓርላማ ስለነበርኩ ለመድረክ ቅርብ የምመሰላቸው ካሉ ተሳስተዋል፡፡ የመድረክ ስብሰባ እንደሚታወቀው ውሣኔ የሚሰጠው የጉባዔ አባላት ተሰብሰበው በውይየት አቋም ይዘው በነፃነት በሚሰጥ ድምፅ አይደለም፡፡ አባል ድርጅቶች አድማ መተው የሚመጡበት ነው፡፡ ሌላው በመድረክ ውስጥ ኃላፊነት የሚያዘው በአባል ድርጅቶች በዙር ነው፡፡ ከአባል ድርጅቶቹ ደግሞ የሚልኩትን መሪ ቀይረው የማያውቁት ደግሞ ፕሮፌስር በየነ እና ዶክተር መረራ ናቸው፡፡ አሁን ባለኝ መረጃ መሰረት መድረክን የመምራት ተራው የሀረና ነበር፡፡ ይህ ማለት ግን የስብሳቢነት ቦታው ለሀረና እንዲሲጠው ሀረና ለቦታ የሚያቀርበው ዕጩ ወሳኝነት አለው፡፡ ሰለዚህም ሀረና ያቀረበው ዕጩ ለመድረክ ሊቀመንበርነት አይደለም፣ ለምክትልም አይሆንም በሚል ቦታው በቃኝ ለማያውቁት ለፕሮፌሰር በየነ አንዲሰጥ ተደርጎ ዶክተር መረራም ምክትል ሆነው ቀጥለዋል፡፡
አቶ አስፋ ጫቦ በቅርቡ ባሳተመው መፅኃፍ ውስጥ የሸዋ ንግስና ከተመለሰ የእኛም መመለስ አለበት የሚል ስላቅ አቅርቦ ነበር፡፡ ፕሮፌሰር በየነም ቤተሰቦቻቸው በአካባቢው እንዲህ ዓይነት የንግሰና ጥያቄ ከመጠ ከሚጠይቁት ወገን ናቸው ስለሚባል፤ ይህ እስኪመጣ ድረስ መድረክን የንግስና መለማመጃ ያደረጉት መስለኝ፡፡ ይህ ካልሆነ ግን ብዙ ሙከራ አድርገው ያልተሳካላቸውን የአመራር ቦታ ቢቻል ፖለቲካውን ጭምር መተው ለምን ተቸገሩ?
ከወዳጄ ጋር ሰለምርጫው ስናወራ የፕሮፌሰሩ በተደጋጋሚ ከሚቀርብባቸው ከተቃዋሚ መሪነት እራሳቸውን ያግልሉ ጥያቄ ችላ ማለት ብቻ ሳይሆን ሃያም ሆነ ሰላሣ ሰዎች ድምፅ ሰጥተዋቸው በሃላፊነት የሚቆይቱ ባለፈው የሃላፊነት ዘመናቸው ምን ሰርተው ነው? የሚል ጥያቄ ለምን አያነሱም ነው፡፡ በፕሮፌሰር በየነ አመራር ወቅት መድረክ ምን ውጤት አስገኝቶ ያን ውጤት ለማስቀጠል ሲባል ነው የተሰጠው ሊባል የሚችል ውጤት አልታየም፡፡ በኦሮሚያ ለነበረው ህዝባው ንቅናቄ እንኳን በቂ ድጋፍ መስጠት ያልቻለ ስብሰብ እንደሆነ በስብሰባው ወቅት ጥያቄ ተነስቶበታል፡፡
የተነሳው ጥያቄም “በኦሮሚያ ለነበረው እንቅስቃሴ ኦፌኩ ብቻውን ለምን ተንቀሳቀሰ?” በሚል ነበር፡፡ መልሱ ግን የበለጠ አስደማሚ ነበር፡፡ “ኦሮሞዎች የተለየ ጉዳይ ስለነበረን ነው” የሚል እንደምታ ያለው መልስ ተሰጥቷል፡፡ አስገራሚው ነገር በአንድ ወቅት ሀብታሙ አያሌው “ሰለ ኦሮሞ ችግር ለመናገር ኦሮሞ መሆን አያስፈልግም ሰው መሆን ይበቃል” ብሎ በሰጠው አስተያየት መድረክ አጀንዳ አድርጎት ኦሮሞ ያልሆነ የኦሮሞ ችግር አይገባውም የሚል መልስ ተሰጥቶ አንድነት እና ሀረና ታዲያ እዚህ ምን እንሰራለን? በሚል ስብሰባው ተቀውጦ እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡ አሁንም መድረኮች አብረን ነን ይበሉ እንጁ የትግሬው ችግር የሀረና፣ የኦሮሞ ችግር የኦፌኮ አድርገው በመያዝ ዳር ይዘው ተቀምጠዋል፡፡ በነገራችን ላይ መድረኮች አንድነትን ካስወጡ በኋላ የአማራ ተወካይ የሚያደርጉት ወይም የሚመስልላቸው ሳያገኙ እስከ አሁን አሉ፡፡ በቅርቡ የተመሰረተው የአንድነት ሽራፊ “ነፃነት” የሚባለው ፓርቲ ይህን ቀዳዳ ለመሙላት ተሰፋ ሳያደርጉ አይቀሩም፡፡ ወይም “ሰመያዊ” ፓርቲ ዓይኑ በጨው ታጥቦ ሊቀላቀላቸው ይችላል፡፡ የመድረክ አመራሮች ይህ ያለባቸውን የአማራ ወኪል ክፍተት በመሙላት “ፎርጂድ” የኢህአዴግ ኮፒ አደረጃጀት እንዲሳካ መጣራቸው የማይቀር ነው፡፡ ለህወሃት-ሀረና፣ ለኦህዴድ-ኦፌኮ፣ ለደህዴን-የበየነ ፓርቲዎች፣ ለብአዴን- ? ? ? ? – ፡፡ ክፍቱን ቦታ ለመሙላት እንግዲ ነፃነትና ሰማያዊ እድሉ አላቸው፡፡
የሀረና ልጆች በመድረኮች ፊት ዓይን የማይሞሉ ሆነው የተገኙት በመተካካት ፖሊሲ የቀድሞውን መሪ አቶ ገብሩ አስራትን ለዕጩነት ባለማቅረባቸው ነው፡፡ አስገራሚው ነገር በመድረክ አንፃር የተሻለ የውጭ ደጋፊ ያለው ሀረና ለክፉም ለደጉ በሚል የፋይናንስ ኮሚቴ ሃላፊነት እንደተሰጠው ተሰምቷል፡፡ በእርግጥ ዶክተር መረራም ከውጭ ድጋፍ ያለው ቢሆንም ድጋፉን በግል ከፈለገ ለኦፌኮ ካልሆነ ለመድረክ የማድረግ ፍላጎት የለውም፡፡ ለማነኛውም ፕሮፌሰሩ ሲመሩት ከነበሯቸው ድርጅቶች የተወሰኑትን “ምርጫ ቦርድ” ተብዬው ቢሰርዘውም በንግሰና በሚመስል መልኩ የመድረክን ሃላፊነት አለቅ ብለው ቀጥለው፡፡ ወይም ደግሞ አባላቱ በግድ ጭነውባቸዋል፡፡ በዚህ የሃላፊነት ዘመናቸው መቼም በቀጣይ ሊያድርጉት ያሰቡትን መርዓ ግብር በሆነ መልኩ ይፋ ያድርጋሉ ብለን እንጠብቃለን፡፡ በእኔ ግምት የመድረክ ሰዎች ይህን ኃለፊነት ይዘው መቆየት የፈለጉት በአንድ አጋጣሚ ኢህአዴግ ሸብረክ ቢል አለን!!! ለማለት ካልሆነ በስተቀር በተጠና ሰትራቴጂ ትግሉን መርተው መንግሰት ለመሆን አይደለም፡፡ እራሱን ለመንግሰትነት ያላዘጋጀ ፓርቲ/ሰብሰብ፣ ህዝቡን ለማድራጀት የማይተጋ ስብስብ ፋይዳው አይታየኝም፡፡
ሀገራዊ ሰብስብ ነኝ የሚል መድረክ ጠቅላላ ጉባዔ ሲያካሂድ በማህበራዊ ድረ ገጽ እንኳን የውይይት አጀንዳ አለመሆኑ አሳዝኖች ይህችን አካፈልኳቹ፤ እናንተስ ምን ታዘባችሁ፡፡ ከመድረክ ስብሰባ ተካፋዮች ዝርዝር እንጠብቃለን ….. ዘላለማዊ ስልጣን ….
Posted by

No comments:

Post a Comment