Tuesday, December 27, 2016

“እውን የአማራው ትግል #ኢትዮጵያዊነትን_ከአማራው ውስጥ #የማጥፋት_የወያኔ_ሴራ_ነውን?” መልስ ለሰርፀ ደስታ (ከአያሌው መንበር) ሳተናው By ሳተናው

ሰርፀ ደስታ በረጅም ፅሁፉበርካታ ጉዳዮችን ነካክቶ ግንዛቤ እንይዝ ዘንድ አስነብቦናል።እንደዚህ ተንተን ያለ ፅሁፍ ምናልባትም የሰዎችን ብዥታ ወይ ያጠራዋል አልያም የፀሃፊውን ወገንተኝነት ከየት እንደሚሆን ከፅሁፉ እንድንረዳ ያስችለንና የወገነበትን አካል አቋም እንድናውቅ ይረዳናል።
(ከተነተናቸው ውስጥ ኦነግ፣ግ7፣የአማራ ህዝብ ትግል፣ ኢትዮጵያዊነት…ይገኙበታል)
ይህንን እንደመግቢያ ካልኩኝ እኔ የአማራ ትግልን የሚመለከተውን የአማራ ብሄርተኝነት ጉዳይ ግን በገባኝና በማምንበት በኩል ትንሽ ልበል።
ከሰርፀ ጋር አንድ የሚያደርገን የአማራ ህዝብ ከየትኛውም የኢትዮጵያ ህዝብ የበለጠ መበደሉን ሁላችንም ማመናችን ነው።የገለፀበት መንገድ ይለያይና ቁስሉም የእኛን ያህል አይመመው እንጅ እርሱም ይህንን አልካደም።መልካም ነው።
እንግዲህ ለግልፀኝነት ይረዳ ዘንድ እኔ በገባኝ መልኩ የአማራውን ተጋድሎና የብሄርተኝነት እንቅስቃሴ ለመግለፅ ልሞክር።
ዋናው የአማራ ህዝብ ተጋድሎ መነሻም በሰነድ ጠላቴ ነህ በሚል የተዘጋጀን የአንድ መንግስት አቋም መቃወም፣ በህወሃትና ተባባሪዎቹ እየተፈፀመ ያለን የዘር እልቂት በማስቆም ህልውናንውን ማስቀጠል፣ በውሸት ታሪክ ፀሃፊያን የተፃፉ መፅሃፍትን በእውነት ፉርሽ ማደረግ፣ በፖርቲዎች የፕሮግራምና ቅስቀሳ ውይይት የሚታዩ የአማራን ህዝብ እና የቀድሞ የኢትዮጵያ መሪዎችን ወንጀለኛ የማድረግ አባዜ ስህተት መሆናቸውን ማሳየት፣ በአፈ ታሪክ እየተነገረ ያለውን መሰረት አልባ የአማራን ህዝብ እንደ ጨቋኝ የመቁጠር ውንጀላና ክስ ውድቅ አድርጎ የአማራን ህዝብ አሁን ብቻ ሳይሆን ቀደም ብሎም ያጣውን መብቱን አስከብሮ የሁለንተናዊ ተጠቃሚነትን ማረጋገጥ እና ሌሎችም ናቸው።
ህጋዊ በሚመስል መልኩ የዘር ማጥፋት እወጃ ተደርጎበት ዘሩን ማስቀጠል እንደሌለለበትና በሂደትም ይጠፋ ዘንድ መውለድ እንኳን እንዳይችል እየተደረገ ያለ ህዝብ ማን ነው ቢባል መልሱ እጅግ ቀላል ነው።ይህንን መዋጋትም እንዳለብን ማመን አጠያያቂ አይመስለኝም።ጥያቄው የሚሆነው በየት በኩልና የትኛው ይበልጥ አዋጭ ነው የሚለው ነው።
እንደ አንድ የአማራ ወጣት ይህንን እጅግ አደገኛ የተጠና አካሄድ ማስቆም ቀርቶ መከላከል እንኳን መሞከር የሚቻለው በግለሰብ ሳይሆን ሁሉንም በስነ ልቦና ባህልና ታሪክ አማራ ነህ እየተባለ የችግሩ ገፈት ቀማሽ የሆነን አርሲ ያለ አማራ ከወልቃይቱ፣ የጅጅጋውን አማራ ከራያው ጋር በማስተሳሰር ወደ አንድ ጥላ ስር በማምጣት የብሄርተኝነት ስራን በመስራት እንጅ በአንድ ለአምስት በጎጥ በማደራጀት አይደለም ብየ አምናለው።ወይንም ደግሞ ስለዚህ ጉዳይ ብታወራው ፊልም የሚመስለውን ኢትዮጵያዊ በማሰባሰብ ይሳካል ብየም አላምንም።
እየተሰራ ያለው ስራ ይህ ነው ብየም አምናለው።ይህም ውጤት አምጥቷል።የአማራን ህዝብ በአንድ ጥላ ስር የማሰባሰብ የብሄርተኝነት እንቅስቃሴ ቀድሞ የተጀመረና በህወሃት የተንኮል ሴራ የከሸፈ ቢሆንም ባለፉት ሁለት አመታት ግን በተለይም አማራ በመሆናቸው ራሳቸው፣ ቤተሰቦቻቸው አልያም ጎረቤቶቻቸው እየደረሰባቸው ያለው መከራ ዕረፍት የነሳቸው ምሁራንና ወጣቶች በሰሩት ያለሰለሰ ጥረት ውስጥ ውስጡን በሀገር ቤት የመንግስት ተቋማትና በነዋሪው ዘንድ በተደረገ የእውነተኛ መረጃና ማስረጃ ማዳረስ ተግባር ባለፊት ወራቶች ለተካሄደው የአማራ ተጋድሎ ውልደት ምክንያት ሆኗል።
እናም ሰርፀ እንዳለው የአማራ ህዝብ ትግል ኢትዮጵያዊነትን የማጥፋት ወይም የጎሳ ፖለቲካን የማራመድ አባዜ ያለበት ትውልድ ስብስብ አይደለም።ይልቁንም አማራ በመሆኑ የስቃዮች ሁሉ ስቃይ የደረሰበት፤ መፍትሄውም ጠንካራ የአማራ ማህበረሰብን በመፍጠር መክቶ ጠላትን ማስወገድ ነው ብሎ የሚያምን ነው።በእርግጥ አንተ እንዳልከውና እንደምትፈልገው ኢትዮጵያ እየተባለ ሲዘፈን እምባው ከአንተ ቀድሞ የሚመጣው ላይሆን ይችላል።ምክንያቱም እኛ እየኖርንበት ባለው ሀገርና ስርዓት በልበ ሙሉነት ኢትዮጵያዊ ነኝ የሚለው ይኸው ህዝብ ሁኖ ሳለ በደሉ ለምን እዚህ ህዝብ ላይ ከፋ የሚልን ጥያቄም መጠየቅ ጀምሯልና።አንተ ደግሞ እየተገደለም፤ ዘሩም እየጠፋ ኢትዮጵያዊ ነኝ ይበል ያልክ ትመስላለህ።ይልቁንስ የዚህን ህዝብ ትግል አድማሱን አስፍቶ እንዴት በሁሉም የኢትዮጵያ ክፍል ማድረግ ይቻላል? የሚል ጥያቄ ብታነሳ መልካም ነው እልሃለው።
ከዚያ ውጭ ቅማንት አማራ አይደለም፣አገው አማራ አይደለም ወዘተ የሚል መሰረተ ቢስ ትርክትም አካተሃል።አዎ በደም ቆጠራ ከሄድክ ላይሆን ይችላል።እኛ የምናራምደው ግን የስነ ልቦና አብሮነት መለኪያ የጤናማ ብሄርተኝነት እንጅ አንተ እንዳልከው በዘረመል የተመሰረተ የኔጋቲቭ ብሄርተኝነት አይደለም።እንዲያውም አደጋ የሚሆነው የአማራ ስነልቦና ያለውን ህዝብ ራሱ ሳይጠይቅ እንዳንተ አይነቱ ግን ቅማንት ነህ ብሎ ሲገፋው ነው።የአማራ ህዝብ እኮ (አገው አማራ፣ ቅማንት አማራ፣አርጎባ አማራ…)አንድ ህዝብ ነን ብሎ ነው ወልቃይት ላይ የተነሳን የማንነት ጥያቄ ደግፎ ቻግኒ ላይ የሚገኝ አገው አማራ “ሞት ቢደገስልንም እልንፈራም” በማለት ወልቃይት አማራ ነው ያለው።”አንተ የአማራ ወጣት ሆይ ሞትን ብትፈራ” ….ብሎ የክብር ሰንደቁን ከፍ አድርጎ ሲያውለበልብ እኮ ነው ደብታትቦር ላይ ጀግናው የአማራ ወጣት በህወሃት ሳራዊት የተሰዋው።የባንዳነት ስራ በተደራጀ የአማራ ተጋድሎ ይከሽፋል ፤ ወልቃይት አማራ ነ ው ብሎ ስወለጣ እኮ ነው በርካታ የባህር ዳር ወጣት የጥይት ራት የሆነው።ምናልባት ፎቶና ቪዲዮ ካስፈለገም በዘርፍ በዘርፉ ላያይዝልህ እችላለው።
ሌላው ወልቃይት የጠየቀው ጎንደሬነትን እንጅ አማራነትን አይደለም (አማራጭ ስላጣ ነው ላልከው) እንግዲህ ይህንን እንዲመልሱት የምተወው ለእነ ኮሎኔል ደመቀ ይሆናል።ምክንያቱም በህይወት አሉና።እስከዚያው ግን የ13 ደቂቃ ቪዲዮ ዩቱብ ላይ ተመልከትና ህዝቡን ሲያስተምር ምን እንደሚል ተመልከተው(ለግንዛቤ እንዲህ ይላል…ባህላችን አማራ፣ቋንቋችን አማርኛ፣ስሜታችን አማራ፣ፈቃደኝነታችን ደግሞ ከአማራ ህዝብ ከጎንደር በጌምድር ጋር ነው ይላል)
እያደረግን ያለነው የአማራ ህዝብ ትግል እንጅ የአማራ ነገድ የዘረ መል ትግል አይደለም።በነገራችን ላይ አንድ ትልቁ ነገር ከዚህ በፊት አማራ የለም በማለት አማራ እንዳይሰባሰብና እንዳይደራጅ ትልቅ ስራ ሰርተው ነበር።አሁን አማራ እያለ የለም ማለታቸው አሳፋሪ መሆኑን ከታሪክ ማስረጃ እንስከ ነባራዊ ሁኔታው ሲቀርብላቸው ደግሞ የአማራውን መኖር አመኑና የአማራውን መሰባሰብ ግን የነገድ ትግል ነው በማለት አሁንም ሌላ ነገር ይዘው ብቅ አሉ።እነዚህ የህልም እንጀራን የሚጋግሩ አካላት ለእኔ ቦታ አልሰጣቸውም።ምክንያቱም ለሺህ አመታት የኖረን ህዝብ ያለምንም ማስረጃ በደረቀ ብዕሩ አማራ የሚባል ህዝብ የለም ብሎ የተነሳ አካል ዛሬ የአማራን ትግል በጤነኝነት ሊያየው የሚችል አለመሆኑ ግልፅ ነውና።ቀድሞውንም ቅን አስተሳሰብ የለውም።
ከዚህ በተረፈ ግን ኢትዮጵያን ለፈጠረ ህዝብ ኢትዮጵያዊነትን ሊያጠፋ ተነሳ ማለት ምፀትም ንቀትም ነው።አማራ የሚባል የለም የሚል አስተሳሰብ ተገዥ የሆነ ደቀመዝሙር ለእኔና መሰሎቸ ኢትዮጵያዊነትን ሊያስረዳኝ አይችልምና።ይልቅስ ኢትዮጵያን የመሰረተ ህዝብ ዛሬ አደጋ ተጋርጦበታልና ይህንን ህዝብ ታድገን እንዴት ሀገራችን እንታደጋት የሚለው ቁልፍ ጥያቄ ነው።በዚህ መስመር ካልመጣችሁ ከመንገዳችን ዘውር በሉ ነው እያልን ያለነው።
በዚህ መሰረት ፀሃፊው በርካታ ጉዳዮችን በገባውና በሚያምንበት ዘርዝሯል።የኦነግን የኦሮሞ እንቅስቃሴና ኢትዮጵያዊነትን፣ የግንቦት 7ን ሀገር ውስጥ ገብቶ አለመታገል እና የአማራን ህዝብ ትግል ዳስሷል።የፀሃፊው በግ7 ጠንካራ ትችቶችን አልሰነዘረም።ለምን።በክረምቱ የአማራ ትግል ሀገር ቤት አልገባም? ብሎ ነው ያለፈው።ግን ኦነግን እንደተቸው ሁሉ ብዙ መሞገቻ ሀሳብ ማንሳት ይገባው ነበር።ህወሃት ላይም እንዲሁ።በሌላ በኩል የአማራን ትግል ከኦነግ የተገንጣይነት አስተሳሰብ ጋር እኩል በተመሳሳይ ጎን ለጎን የሚሄድ አስመስሎ ነው ያቀረበው።ስለዚህ የግለሰቡን ፅሁፍ ባከብረውም መነሻውና መድረሻው ግን ኢትዮጵያን መታደግ አይደለም ብየ እንድገመግም እገደዳደለው።
አንድ ሚዛናዊ ህሊና ያለው ሰው የአማራን ህዝብ ትግል ከኦነግ አስተሳሰብ ጋር ሊያገናኘው አይችልም።ሁለቱ እጅግ የተለያዩና ተፃራሪም ናቸውና።የአማራ ትግል የኦነግን የትግል መስመር ብቻ ሳይሆን ኦነግን ራሱንም ይታገለዋልና።ምክንያቱም ኦነግም፣ ሻዕቢያም እንደ ህወሃት አማራ ላይ የራሳቸው ያሳረፉት ዘመን ተሻጋሪ ጠባሳ እና የተጣመመ እይታ አላቸውና።የአማራ ህዝብ ትግል (አማራ ተጋድሎ) በወያኔ እንደሚመራ ወይም የወያኔ አጀንዳ ነው ለማለት ወይም ኢትዮጵያዊነትን ይፃረራል ለማለት መጀመሪያ የአማራን ህዝብ ትግል ምንነት ማወቅ ይጠይቃል።በእርግጥ ፀሀፊው ይህ ጠፍቶት አይመስለኝም።
ለማንኛውም በዚህ ሰዓት ለኢትዮጵያዊው አማራ ኢትዮጵያዊነትን ማስተማር ሳይሆን የሚቀድመው አደጋ ውስጥ ላለው ለኢትዮጵያ ፈጣሪው አማራ እንዴት እንድረስለት የሚለው ነው።
(በነገራችን ላይ እንዲያው የተሰማኝን ለመግለፅ እንጅ ለአማራ ወጣት ታሪካዊ ሰንደቅ አላማውን ይዞ እየሞተ ላለ ህዝብ ኢትዮጵያዊነትን ለማስተማር የሞራል ብቃት የለኝም።ሌላውም እዚህ ላይ ጊዜ ባያጠፋ እመክራለው)
ድል ለአማራ ህዝብ ሞት ለጠላቶቹ!!!
ቸር ይግጠመን

No comments:

Post a Comment