Wednesday, December 21, 2016

ብርሃኑ ነጋን ውድቅ የማደርገው በዛሬ ክሽፈቱ ላይ ተመርኩዤ እንጂ ባለፈ ታሪኩ መዝኜ አይደለም:: (ኄኖክ የሺጥላ)

ብርሃኑ ነጋን ውድቅ የማደርገው በዛሬ ክሽፈቱ ላይ ተመርኩዤ እንጂ ባለፈ ታሪኩ መዝኜ አይደለም:: (ኄኖክ የሺጥላ)
እነ ኢንጅነር ሃይሉ ሻወልን ፥ እነ ዶ/ር ታዬ ወ/ሰማያትን እና ሌሎችንም የአማራ (ኢትዮጵያዊ ) ሊህቃንን አዋርደው ፥ ፈርጀው ፥ ሰድበው ፥ ዘልፈው ፥ ከትግሉ ሜዳ ባስወጡበት መንገድ የአማራ ታጋዮችን ማጣጣል እና ማናናቅ ጀምረዋል ። ያልተረዱት አንድ ነገር ••• እንደማያቆሙን ! እርግጥ በአስተሳሰባችን ቆስላችኋል ! ስትቋምጡለት የነበረው ስልጣን መንበሩ ወዲያ ተንፏቋል! እናዝናለን••.!!
የብሽቀታቸው ሁነኛ ማሳያዎች አሁንም የህዝብን ጥያቄዎች ከመመለስ ይልቅ ፥ የድርጅት አፎች በሆኑ ዋልጌ ደጋፊዎቻቸው እና ምንደኛ ፖለቲከኞቻቸው በተከታታይ የስም ማጥፋት ዘመቻ ማካሄድ ነው ።
ለምሳሌ እህታችን ርስቴ ተስፋዬን ፥ ከዚህ ቀደም ለኢሳት የሰጠችውን ቃለ መጠይቅ በመቆራረጥ ክብረ ነክ የሆኑ የስም ማጥፋት ዘመቻ ላይ ተጠምደው ፥ በቅርብ የማውቃቸው እና በዚህ ደረጃ ያንሳሉ ብዬ የማልገምታቸው ሳይቀሩ ፥ የዚህ የርካሽ ተግባር ተሳታፊ ሆነው ይህንን መሰረት የሌለው ነውረኛ ነገር ሲለዋወጡ እያስተዋልን ነው።
ርስቴ የወያኔ ታጋይ ነበረች፥ እውነት ነው እሷም አልካደችም ! ዛሬ ግን ርስቴን በወያኔነት ያስፈረጃት ከወያኔ ጋር መስራቷ ሳይሆን ከእነርሱ ጋር አለመቆሟ ነበር ። ያ ቢሆን ኖሮ ኤርሚያስ ለገሰም ወያኔ ተብሎ በተሰደበ ነበር ። ኤርሚያስን ድሮ በነበረው ሳይሆን አሁን በሆነው ነው እኔ በግሌ የምመዝነው ። ዛሬ ምን እየሰራ ነው በሚለው ነው የምለካው። በድሮ ታሪኩ ልመዝነው ብል አጠገቤ መቆም የሚያስችል ታሪክ ያለው ሰው አይደለም ! በረከት ስምዖን ቢሮ አጠገብ ( ወይም ድረስ ) ቢሮ ማሰጠት የሚያስችል አድርባይነትን ተሸክሞ የኖረ ፥ ምናልባትም በአንዳንድ ወንጀሎች ላይ የተሳተፈም ሰው ሊሆን እኮ ይችላል። ግን ኤርሚያስን የምመዝነው ዛሬ በቆመለት አላማ እንጂ በትናንት ማንነቱ አይደለም።
እናውራ ከተባለ እና በትናንት ማንነታቸው መዝነን ዛሬ አይረቡም የሚል ድምዳሜ ላይ የምንደርስ ከሆነ ፥ መሳይ መኮንን የኢትዮጵያ መንግስት ጋዜጠኛ ነበር ። ከመንግስት ጋር ያጋጨው የመጀመሪያ አብይ ምክንያትም የአስተዳደሩ ክፋት ሳይሆን « እርሱ እንዳጫወተኝ እና እራሱም በተወሰነ ደረጃ ይፋ አድርጎ እንደገለጠው ወይም (እንዳወጣው ) በምንግስታቱ ድርጅት ኢትዮጵያ የሰላም አስከባሪ ሃይል ሆና በተሰለፈችበት ወቅት መሳይ መኮንን በጋዜጠኝነት ይሰራ እንደነበርና ኋላ ላይ የውጭ ሃገራት የከፈሉትን ደሞዝ ወያኔ ቀርጥፎ በመብላት ( የሁነኛ ደሞዙን የግማሽ ግማሽ ግማሽ በመከፈሉ ) በተነሳ ንትርክ እና ገንዘቤን አምጡ ፥ የምን ገንዘብ ሂድ ወዲያ በሚል ጠብ እንደሆነ ይታወቃል ። ዛሬ መሳይ እየሰራ ያለውን ስራ በትናንት ታሪኩ መዝኜ አልተቸውም ። ብተቸውም እንደ ጋዜጠኛ ያጎደለውን እንጂ ፥ ስብዕናውን አይደለም ! አይሆንምም ! ይህ ነውር ነው!
ብርሃኑ ነጋ ከበረከት ስምዖን ጋ ውስኪ ይራጭ የነበረ ሰው ነው ። መለስ ዜናዊን ለማገልገል ከዚህ በደብዳቤ የሄደ ( እሱ ግን አላውቅም እዚያ ስደርስ ነው የማውቀው ብላል•• ይሁንለት ) ሰው ነው ። ያም ሆኖ ባለፈ ታሪኩ መዝኜ አይደለም ብርሃኑን ውድቅ የማደርገው ፥ ብርሃኑን ውድቅ የማደርገው በዛሬ ክሽፈቱ ላይ ተመርኩዤ እንጂ ። ያም ቢሆን ብርሃኑን እንደ ግለሰብ ስብዕናው ለመወረፍ መዳዳት አግባብ ነው ብዬ አላስብም ! የፖለቲካ ስህተቶቹ ግን የሚተቹ ናቸው ! በግድፈት የተሞሉ ግዝፈቶች ናቸውና !
ሌሎቹም እንዲሁ ! ይልቅ ከወያኔ ጋ ቁመን የሚያሳይ አንዳች ሰባራ መረጃ ባልቀረበበት ፥ ባልዋልንበት እና በማንውልበት ሁኔታ ውስጥ ያለንን ሰዎች ወያኔ ብሎ መፈረጅ ፥ የአማራ መደራጀት ምን ያህል የቁም ቅዠት እንደሆነባችሁ ማሳያ ነው ።
እንደ መደምደሚያ
አማራ በቁስም ሆነ በሞራል ወይም ከታሪክ ባለውለታነት አንፃር ባላው ቦታ ከማንም ሳያስን የሚኖርበትን ኢትዮጵያ እንፈጥራለን ! ይህንንም ለማድረግ የማንምሰው ተራራ የማንፈነቅለው ድንጋይ አይኖርም ! አማራ አክብሮ ብቻ ሳይሆን ተከብሮ የሚኖርባት ሃገር እስክትኖረው ድረስ ፥ የመጣውን ሁሉ ስድብ እና ዘለፋ ፥ ዛቻ እና ሀሜት ፥ አሉባልታ እና ፍሬ ከርስኪ ፍረጃ ሁሉ ችለን መታገላችንን እንቀጥላለን ። ለአማራ ህልውና ስጋት ናቸው የምንላቸውን ፥ በመረጃ የተደገፉ ፥ ማናቸውም አይነት እንቅስቃሴዎችን እናደርጋል ። ይህንን የአማራ ትንሳኤ ለማብሰር ፥ በመኣው አለም የሚገኙ የአማራ ተወላጆች ከጎናችን እንዲቆሙ ጥሪ እናቀርባለን ። ጥሪው መረጃዎችን በማድረስ ፥ ድጋፍ በመስጠት ፥ ጠላቶችን በመለየት ፥ የውስጥ አርበኛ በመሆን እና ወዘተ የአማራ ተጋድሎ መርዳት እንደሆነም ልናስገነዝብ እንወዳለን !
ከተነሳልነት እና ከቆምንለት አላማ አንፃር አሉባልታ እና ሀሜት የመጀመሪያዎቹ ተራ ነግሮች ናቸው !
አማራ ተነስ
ኄኖክ የሺጥላ

No comments:

Post a Comment