Saturday, December 17, 2016

አሜሪካና ኢትዮጵያ ግልፅ ንግግሮችን ለማድረግ ተስማሙ


ዩናይትድ ስቴትስ እና ኢትዮጵያ አስተዳደርና ሰብዓዊ መብቶችን በሚመለከቱ ስፋት ያላቸው ጉዳዮች ላይ በግልፅነት ለመወያያት መስማማታቸውን አዲስ አበባ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ ዛሬ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
በዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት የዴሞክራሲ፣ የሰብዓዊ መብቶችና የሥራ ረዳት ሚኒስትር ቶም ማሊኖውስኪና በኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ወርቅነህ ገበየሁ የሚመሩት የሁለቱ ሃገሮች ቡድኖች ዛሬ ያደረጓቸው ውይይቶች የኢትዮጵያ መንግሥት የሃገሪቱን የምርጫ አያያዝ ለማሻሻል የገባውን ቃል እንዲገፋበት ማሳሰብን ጨምሮ ስፋት ባላቸው ጉዳዮች ላይ መወያየታቸውን ኤምባሲው አክሎ አመልክቷል፡፡
በተጨማሪም በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ወቅት ሕገ-መንግሥታዊ መብቶች እንዲከበሩ፣ ለውይይት ሁኔታዎች አንዲመቻቹ፣ ጠንካራ መገናኛ ብዙኃን እንዲኖሩም ውይይቱ ትኩረት አድርጎ መነጋገሩን መግለጫው ጠቁሟል፡፡
መሠረታዊ ነፃነቶች እየተከበሩ የጥላቻ ንግግሮችን ለመቆጣጠር እንዲቻልና የሲቪል ማኅበረሰብ አስፈላጊ ጫና ለመልካም አስተዳደርና ለዓመታዊው የዩናይትድ ስቴትስ የሰብዓዊ መብቶች ሪፖርት ያለውን ጥቅም አንስተው የሁለቱ ሀገሮች ቡድኖች መክረዋል፡፡
በኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ሂሩት ዘመዴነህና በኢትዮጵያ የዩናይትድ ስቴትስ ጉዳይ ፈፃሚ ፒተር ቨርማን ተባባሪ ሊቀመንበርነት የተመራው ይህ ሰባተኛው የሥራ ቡድን ስብስባ ወደፊት በሚያደርጓቸው ውይይቶች በግልፅነት ለመነጋገር መስማማታቸውን የኤምባሲው መግለጫ አመልክቷል፡፡

No comments:

Post a Comment