Tuesday, December 27, 2016

በጠራራ ጸሀይ አገር ሲዘረፍ (አቻምየለህ ታምሩ )



ፋሽስት ወያኔ ከኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ ታሪካዊ ቅርሶችን «በህጋዊ» መንገድ በጠራራ ጸሀይ «በቋሚነት» ወደ ትግራይ እያጓዘ ነው። ከትግራይ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ በተጻፈ ደብዳቤ በመላ ኢትዮጵያ የሚገኙ ቅርሳ ቅርሶች ሁሉ ተሰብስብው ወደ ትግራይ እንዲላኩ ትዕዛዝ ተላልፏል። ይህ የመለስ ራዕይ አንዱ አካል ነው። የመለስ ራዕይ ትግራይን በአፍሪካ ቀዳሚ የቱሪዝም መዳረሻ ማድረግ እንደሆነ ሲነገር ሰምተናል። እንደሌሎች የመለስ ራዕይ ግቦች ሁሉ በትግራይ ቱሪዝም መስክ የተቀመጠው የመለስ ራዕይ ውጤትም የሚሳካው በዘረፋ ነው። እየተተገበረ ያለው የመለስ ራዕይ የዘረፋ ራዕይ እንደሆነ ለማንም የተደበቀ አይደለም።
እነሆ በቱሪዝም መስክ የተቀመጠው የትግራይ ልማት የሆነው የመለስ ራዕይ ተፈጻሚ ይሆን ዘንድ ትዕዛዝ ተላልፏል። በአገሪቱ የሚገኙ የቱሪዝም ቅርሶች ሁሉ ተነቅለው ትግራይ ውስጥ እንዲከማቹ ጥብቅ ትዕዛዝ ተላልፏል። ካሁን በኋላ የአፄ ስርፀ ድንግል፣ የአፄ ፋሲል፣ የአድያም ሰገድ ኢያሱ፣ የአፄ ዳዊት፣ የአፄ በካፋ፣ የአፄ ኢያሱና የወይዘሮ ተዋበች ከልዩ ልዩ ማዕድናት የተሰሩ ዘውዶች የሚገኙት ትግራይ ውስጥ ነው። ካሁን በኋላ ጎንደር፣ ጎጃም፣ ወሎ፣ ሸዋ፣ ሐረር፣ ወለጋ፣ ባሌ፣ አዲስ አበባ፣ ወዘተ የሚጎበኙት ትግራይ ውስጥ ወያኔ ባስገነባው «አገራቀፍ ሙዚየም» ውስጥ ነው። ካሁን በኋላ አገር ጎብኚ ጎንደር፣ ጎጃም፣ ወሎ፣ ሸዋ፣ ሐረር፣ ወለጋ፣ ባሌ፣ አዲስ አበባ፣ ወዘተ መሄዱን ትቶ ኢትዮጵያን ለመጎብኘት ሲመጣ የሚተመው ወደ ትግራይ ነው።
ካሁን በኋላ ለመዝናናት ካልሆነ በስተቀር የኢትዮጵያን ታሪካዊ ቅርሶች ለመጎብኘት ወደ ጎንደር፣ ጎጃም፣ ወሎ፣ ሸዋ፣ ሐረር፣ ወለጋ፣ ባሌ፣ አዲስ አበባ፣ ወዘተ መሄዱ ይቀራል። ካሁን በኋላ ጣና ቂርቆስ፣ መርጡለ ማርያም፣ ብርብር ማርያም፣ አዳዲ ማርያም፣ ተድባበ ማርያም፣ወዘተ የሚገኙ ታሪካዊ ቅርሶችን ለመጎብኘት የሚሄድ ቱሪስት የለም፤ ቅርሶቹ ወደ ትግራይ እንዲሄዱ ታዝዟልና። ካሁን በኋላ ሥርዓተ ንግሥ ይፈጽሙባቸው የነበሩ አድባራትን፣ ዘውድ ይደፋባቸው የነበሩ ጥንታዊ ቤተ ክርስቲያናትን፣ነገስታቱ ቅብዓ መንግሥት ይቀቡባቸው የነበሩ አጥቢያዎችን፣ ብዙ ሊቃውንቶችና የተማሩ ቀሳውስቶች የሰለጠኑባቸው በየገዳማትና ዋሻዎች የሚገኙ መጽሀፍትን ለመጎብኘት የሚመጡ ቱሪስቶች የሚተሙት ወደ ትግራይ ነው።
ካሁን በኋላ በተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎች የነበሩ ነገሥታት፣ የራሶችና የእቴጌዎች እንዲሁም ሌሎች ከፍተኛ ባለሥልጣናት የነበሩ ሰዎች የክብር አልባሳት፣ መስቀሎች፣ ሥዕላት፣ የአንገትና የእጅ ጌጣጌጦች፣ የጦር መሳሪያዎች፣ ምስል የተቀረፀበት የክብር ዘንግ…እጅግ በርካታ ቅርሶች የሚገኙትና የሚጎበኙት ትግራይ ውስጥ ነው።
በተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍል የሚገኙ ቅርሶችን ዘርፎ ወደ ትግራይ ለመውሰድ ያመቸው ዘንድ ወያኔ በቅድሚያ ያደረገው ነገር ቢኖር አገር አቀፍ የቱሪዝም ማዕከል ትግራይ ውስጥ አስገነባ። ይህ ትግራይ ውስጥ የተገነባው የቱሪዝም ማዕከል አላማ ሌሎች የኢትዮጵያ አካባቢዎችን ሊጎበኙ የሚመጡ ቱሪስቶችን ጠቅልሎ ወደ ትግራይ በመውሰድ ትግራይን የአፍሪካ የቅርስ ሀብትና የቱሪዝም መዳረሻ ማድረግ ነው። ይህ የመለስ ራዕይ ተቀዳሚ አላማ ነው።
በተጻፈው ደብዳቤ መሰረት በጎንደር ቤተ መንግስት፣ በላሊበላ ውቅር አቢያተ ክርስቲያኖች፣ በአዲስ አበባ የተለያዩ አድባራት፣ ቅርስ ቤቶችና ቤተ መንግስት፣ በዲማ ጊዮርጊስ፣ በግሸን ማርያም፣ ወዘተ የሚገኙ ቅርሶች ወደ ትግራይ እንዲላኩ ከታዘዙት መካከል ይገኙበታል።
ባለፋው አመት በቀረበው የባህልና ቱሪዝም ሚንስትር መስሪያ ቤት ሪፖርት መሰረት ከቋሚና ተንቀሳቃሽ ቅርሶች ተያያዥ ጉብኝት የተገኝው አመታዊ ገቢ 3.5 ቢሊዮን ዶላር ነበር። የኢትዮጵያ ቅርሶች ወደ ትግራይ እንዲላኩ ትዕዛዝ የተላለፈበት ዋና አላማ ሌሎችን የቱሪዝም መዳረሻዎች አራቁቶ 3.5 ቢሊዮን ዶላር የቱሪዝም ገቢን የትግራይ ለማድረግ ነው። እሳና ሀፍረት የሌላቸው ፋሽስት ወያኔች ሌላውን ገፍፈውና ጾም ደፍተፍው የድሆችን ቅርስ ወደ መንደራቸው እያጓዙ ነው። የጉድ አገር! ይህን የዘራፊዎች አገዛዝ መታገል የነፃነት ብቻ ሳይሆን የጽድቅ ስራ መሆኑን ማንም መረዳት አለበት!

No comments:

Post a Comment