Tuesday, August 23, 2016

የህዝብን ቁጣ በሃይል መግታት እንደማይቻል ከታሪክ መማር አስተዋይነት ነዉ!!! (ፈርስት ሂጅራ ፋውንዴሽን )


የህዝብን ቁጣ በሃይል መግታት እንደማይቻል ከታሪክ መማር አስተዋይነት ነዉ!!!
ፈርስት ሂጅራ በአሜሪካ ከዛሬ ሃያ አመታት በፊት ሲመሰረት አንግቦ ከተነሳባቸው አላማዎች አንዱ ለኢትዮዽያ ሙስሊሞችና ብሎም ለመላው ኢትዮዽያዊ ወገናችን አጋር ለመሆንና በጎ ለመስራትም ነዉ። ታዲያ በነዚህ ባሳለፍናቸዉ አመታት በተለይ ከ1991 ለዉጥ ወዲህ እንደማንኛዉም ኢትዮዾያዊ ያገራችን የተስፋ ብርሃን ጭላንጭል እየታየን ሲጠፋ ከዛሬ ነገ ይሻላል በሚል ቆይተን ነበር። ነገር ግን አገሪቱን እያስተዳደረ ያለዉ አምባገነናዊ ስርአት ከአራት ዐመታት ወዲህ ሙስሊሙ ህብረተሰብ ላያ ይህ ነዉ የማይባል ህገወጥ የግፍ እርምጃ በመውሰድና በገሃድ በእምነቱ ጣልቃ በመግባት ሙስሊሙ በአገሩ ላይ ያለዉን ተስፋ ድቅድቅ ባለ ጨለማ ዉስጥ ጥሎታል።
በአገራችን ኢትዮጵያ ውስጥ ብዙ ውስብስብ ሰው ሰራሽ ችግሮች እንዳሉ ይታወቃል። ከዛሬ አራት አመታት በፊት ሙስሊሙ ህብረተሰብ ለመብቱ ሲል የጀመረዉን ሰላማዊ እንቅስቃሴን አስከትሎ በአምባ ገነኖች የደረሰበት ጭፍጨፋና መከራ ዛሬ በሌላዉ ወገን ላይ በአስከፊ ሁኔታ እየደረሰ ነዉ። በተለይ በአሁኑ ወቅት በኦሮሚያና በአማራ ክልል ያለው ሁኔታ እጅግ አስደንጋጭ እና አሳማሚ ደረጃ ላይ ደርሷል። አማራ እና ኦሮሞ ወገኖቻችን በአሰቃቂ ሁኔታ በመንግስት ሀይሎች እየተገደሉ ነው።
ጭፍጨፋው በቀላሉ የሚገመት አይደለም። መጠነ ሰፊና በቁጥር በውል የማይታወቁ ወገኖች ህይወታቸውን እንደዋዛ ሰውተዋል። ደማቸው ፈሷል። አሁንም የማፈንና የመግደል ዘመቻው በሰፊው እንደቀጠለ ነው። ለጀግናዉ የኦሮሞና የአማራ ወገኖቻችን ያለንን አድናቆት ከልብ በመነጨ ምስጋና ለመግለፅ እንወዳለን። በተለይ ባደረጉትና በሚያደርጉት ትእይንተ ህዝብ ላይ የሙስሊሙን የፍትሕ ጥያቄዎችን በማንሳታቸዉ ምን ጊዜም ዉለታችሁን እንደማንረሳ እናሳዉቃለን።
የፈርስት ሂጅራ ፋውንዴሽን አሁንም ቢሆን ከዚህ በፊት በአምባ ገነኑ የወያኔ ሰራዊት የተገደሉትን ለኢትዮጵያ ህዝብ ነጻነት እና ፍትሕ ሲሉ ህይወታቸውን የሰጡትን ሰማዕታት ሁልጊዜም በጸሎት (በዱዓዕ) እናስታውሳቸዋለን። ለሞቱለት ዓላማም ያለጥርጥር ፈለጋቸውን እንከተላለን። ለሙታን ቤተ ሰቦችም ትዕግስትን እና መጽናናትን እንመኛለን።
አሁን ባለው አስከፊ አምባገነናዊ አገዛዝ ብዙ ወገኖቻችን ማለትም የሰብዓዊ መብት ተከራካሪዎች፤ ጋዜጠኞች፤ ጦማሪዎች፤ የሙስሊሙ ህዝብ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴዎች፤ የሀይማኖት መሪዎች፤ ምሁራን እና የፖለቲካ ድርጅት መሪዎች እስካሁን ድረስ በእስር ቤት እየተሰቃዩ ነው። ምንም ወንጀል ያልሰሩ በአገሪቱ የሰፈነውን ጨቋኝ መንግስት በመቃወማቸውና ለሰላምና ለፍትሕ በመጮሀቸው ብቻ የታሰሩት የሀገሪቱ ውድ ልጆች በአስቸኳይ ከእስር እንዲለቀቁ ድርጅታችን በጥብቅ ይጠይቃል።
የህወሀት መንግስት የሰይጣን ጥይቱን ያነጣጠረው በሁሉም ሀይማኖቶች፤ ብሄረስቦች፤ ክልሎች፤ ባጠቃላይ በሁሉም ወገኖቻችን ላይ በመሆኑ በኢትዮዽያ ላይ ፍትሕን ለማስፈር በሚደረገዉ ትግል የዜጎች ተሳትፎ ስለሚጠይቅ ክፍፍልን በመተው ድል እንድንቀዳጅ አብረን በጋራ እንድንታገል እናመላክታለን።
ለዚህ ሁሉ ግፍ ያለጥርጥር የወያኔ መንግስት አገዛዝ ተጠያቂ ነው። የስርዓቱ መሳሪያ የሆነው የታጠቀው ሰራዊት አቅፎና ተንከባክቦ ያሳደገውን ኢትዮጵያዊ ወንድሙን እህቱን አባቱን እና እናቱን በአሰቃቂ ሁኔታ ከመግደል እንዲቆጠብ ከዚያም አልፎ መንግስትን ሳይሆን ህዝብን የማገልገል ሀላፊነት እንዳለበት አጥብቀን እንመክራለን።
ፍትሕ ለሁሉም ዜጎች!
ትግላችን ባንድነት እስከድል በአላህ ፈቃድ ይቀጥላል!!
አሏህ አክበር !!!
ፈርስት ሂጅራ ፋውንዴሽን
ዋሽንግተን ዲሲ

No comments:

Post a Comment