[የክቡር ሚኒስትሩ ሾፌር ፌስቡክ እያያ ይስቃል]

  • አንተ ሰውዬ አበድክ እንዴ?
  • ምነው ክቡር ሚኒስትር?
  • ብቻህን ምን ያስገለፍጥሃል?
  • ፌስቡክ እያየሁ ነው፡፡
  • እንዴ መቼ ተለቀቀ?
  • ደግሞ ማንን አስራችሁ ነበር?
  • ፌስቡክን ማን ለቀቀው?
  • ለነገሩ ፌስቡክ ራሱ ታስሮ ነበር ለካ፡፡
  • እኮ ማን ለቀቀው?
  • ትንሽ ቆየ እኮ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ምኑ ነው የቆየው?
  • ፌስቡክ ከተለቀቀ፡፡
  • ማነው ልቀቁ ያላቸው?
  • በነካ እጃችሁ ግን ሌሎቹንም ብትለቁ መልካም ነው፡፡
  • እነማንን?
  • በየጊዜው የምታጉሯቸውን ነዋ፡፡
  • ምን አልክ?
  • ግን ፌስቡክ ራሱ እንደ መብራትና ውኃ ልታደርጉት ነው ማለት ነው?
  • እንዴት ማለት?
  • በፈረቃ ነዋ፡፡
  • በፈረቃ ሳይሆን በጨረቃ ነው፡፡
  • እንዴት በጨረቃ?
  • ማታ ማታ ብቻ ነዋ የሚለቀቀው፡፡
  • እሷንም አታሳጣን ብንል ይሻላል፡፡
  • ለመሆኑ ምንድን ነው የሚያስቅህ?
  • እንኩ ይመልከቱት ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • የማነው ቦርጫም በእናትህ?
  • አዩት ዓሳ ነባሪውን?
  • የምን ዓሳ ነባሪ ነው?
  • ቅፅል ስሙ ነው፡፡
  • ይኼ ነው ያስገለፈጠህ?
  • እህሳ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ይኼ ያስለቅሳል እንጂ ምኑ ያስቃል?
  • ኢትዮጵያን ወክሎ ተወዳድሮ ነው እኮ፡፡
  • በምን?
  • በዋና፡፡
  • በዚህ ቦርጭ?
  • አይገርምዎትም ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • እና እንዴት ሆነ?
  • አዋረደን ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ግን ሲታይ ልማታዊ ይመስላል፡፡
  • እንዴት ማለት?
  • ቦርጩ የአገሪቷን ልማት ቁልጭ አድርጎ ያሳያል፡፡
  • ምን አሉኝ?
  • አታየውም እንዴ ቦርጩ ላይ የ11 በመቶ ዕድገቱን?
  • ይኼ የሚያሳየውማ ዕድገቱን ሳይሆን ውድቀቱን ነው፡፡
  • ስማ ሁሌ የመፍትሔ ሰው ነው መሆን ያለብህ፡፡
  • ምን ማለት ነው?
  • ይኼ ሰውዬ ኦሊምፒክ የላክነው ሆን ብለን ነው፡፡
  • ለምን ተላከ?
  • ለአገር ገጽታ ግንባታ፡፡
  • ይኼ ገጽታችንን ያፈርሰዋል እንጂ እንዴት ይገነባዋል?
  • ኢትዮጵያ ዓለም ላይ የምትታወቀው በረሃብና በድርቅ ነው፡፡
  • እሱማ ልክ ነው፡፡
  • እና ፈረንጆቹ በልተን ጠግበን የምናድር አይመስላቸውማ፡፡
  • አሁንም እኮ በልተው የጠገቡት ጥቂቶቹ ናቸው፡፡
  • ፖለቲካህን እዛው፡፡
  • እውነቴን ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ለማንኛውም እንደዚህ ዓይነት ቦርጫም ኢትዮጵያዊ ሲያዩ ፈረንጆቹ አመለካከታቸው ይቀየራል፡፡
  • እንዴት ይቀየራል?
  • ጠግበን እንደምናድር ያውቃሉ፡፡
  • ኧረ ክቡር ሚኒስትር ኦሎምፒኩን የተሳተፈው እኮ አባቱ የፌዴሬሽኑ ፕሬዚዳንት ስለሆኑ ነው ይባላል?
  • ታዲያ ቢሆኑ ምን አለበት?
  • እ . . .
  • አሁን የእኔ ዘመዶች ሁሉም የመንግሥት ባለሥልጣናት ናቸው፡፡
  • እሱስ ልክ ነው፡፡
  • ከባለሥልጣኖቹ ውጪ ነጋዴዎች ናቸው፡፡
  • ለነገሩ አገሪቷ በእጃችሁ ናት፡፡
  • ከእጃችን ልትወጣ አትችልም፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር ግን እንደዚህ እስከ መቼ ይቀጥላል?
  • ምን ማለት ነው?
  • በየቀበሌው ራሱ ሲኬድ ሁሉም በወንዝ ነው የተደራጀው፡፡
  • ኧረ አንተስ ወንዝ ይዞህ ይሂድ፡፡
  • ምን አደረኩ ክቡር ሚኒስትር?
  • ወሬ ታበዛለህ፡፡
  • አገራችን ተዋረደች እያልኩዎት እኮ ነው፡፡
  • ገጽታ ግንባታ ነው አልኩህ?
  • ታዲያ ሰውዬው ዋናተኛ መባል የለበትማ፡፡
  • ምን ይባል ታዲያ?
  • በላተኛ!
[ለክቡር ሚኒስትሩ ከውጭ ስልክ ተደወለላቸው]
  • ምን እያደረጋችሁ ነው ክቡር ሚኒስትር?
  • እያደግን ነዋ፡፡
  • ኧረ ይኼ ያሳፍራል፡፡
  • ምኑ ነው የሚያሳፍረው?
  • እየሠራችሁት ያለው ነገር፡፡
  • አገራችንን ማሳደጋችን ነው የሚያሳፍረው?
  • እንደዚህ እየቀለዳችሁ ግን እስከ መቼ ነው የምትቀጥሉት?
  • ገና እየጀመርን አይደል እንዴ?
  • ቀልዱን ነው?
  • ምን ይላል ይኼ?
  • ክቡር ሚኒስትር ይህቺ የተከበረች አገር እያዋረዳችኋት ነው?
  • እያከበራችኋት ነው ማለትህ ነው?
  • ይኸው አንገታችንን አቀርቅረን እንድንሄድ አደረጋችሁን፡፡
  • ስማ አቀርቅረህ መሄድህ እኮ ጥሩ ነው፡፡
  • ምን እያሉ ነው?
  • እንቅፋት እንዳይመታህ ነዋ፡፡
  • ኧረ ይኼ ማላገጥ ይቅር ክቡር ሚኒስትር?
  • የምን ማላገጥ ነው?
  • ኦሊምፒክ የላካችሁት ሰውዬ ምንድን ነው?
  • የቱ ሰውዬ?
  • ዓሳ ነባሪው ነዋ፡፡
  • ሆን ብለን ነው የላክነው፡፡
  • ምን?
  • ለአገር ገጽታ ግንባታ ነው፡፡
  • ይኼ የአገር ገጽታን ያበላሻል እንጂ ምን ይገነባል?
  • አየህ ፈረንጆች የሚያውቁን በድርቅና በረሃብ ነው፡፡
  • አሁንስ ቢሆን ከእሱ መቼ ተላቀቅን?
  • ስለዚህ እንደዚህ ዓይነት ቦርጫም ዋናተኛ ትልክና አገሪቱ ውስጥ ጥጋብ መኖሩን ታሳያለህ፡፡
  • ግን እንደዚህ እየቀለዳችሁ የምትዘልቁ ይመስላችኋል?
  • ምን እያልክ ነው?
  • በዚህ ጉዳይ በዓለም ደረጃ አገራችን ነው የተዋረደችው፡፡
  • ለምንድን ነው የተዋረደችው?
  • ለነገሩ እናንተ ራሳችሁ አዋራጆች ናችሁ፡፡
  • ምን አድርገን?
  • ስንት ዓለም አቀፍ ውሎችና ውሳኔዎችን በሚገባ ማንበብና መረዳት አቅቷችሁ፣ አዋርዳችሁን የለ እንዴ?
  • ምን ትዘባርቃለህ?
  • እናንተ ፖለቲከኞቻችን ከዋናተኛው አትሻሉም፡፡
  • ምን እያልክ ነው?
  • እናንተም ከሌሎች የምዕራባውያን አገሮች ሚኒስትሮች ጋር ብትወዳደሩ እንደምታዋርዱ እርግጥ ነው፡፡
  • ሰውዬ አደብህን ግዛ፡፡
  • ለነገሩ እንደነገርኩዎ ከዚህ በፊትም አዋርዳችሁን ታውቃላችሁ፡፡
  • ምን ይላል ይኼ?
  • አሁን ዋናተኛው ምን እየተባለ እንደሆነ ያውቃሉ አይደል?
  • ምን ተባለ?
  • ሮቤል ዘ ዌል፡፡
  • እ . . .
  • እኔ ደግሞ ለእርስዎ ስም አውጥቼልዎታለሁ፡፡
  • ምን ልትለኝ?
  • ሚኒስትሩ ዘ ዌል!
[ክቡር ሚኒስትሩ ከአማካሪያቸው ጋር እያወሩ ነው]
  • የተናደዱ ይመስላሉ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • አንዱ እኮ ሰድቦኝ ነው፡፡
  • ለምንድን ነው የሰደበዎት?
  • በዚህ በዋናተኛው የተነሳ ነዋ፡፡
  • ታዲያ እርስዎ ምን አደረጉ?
  • ፖለቲከኞቻችንም ያው ናችሁ ብሎ ነዋ፡፡
  • ምን ብሎ ሰደበዎት?
  • ሚኒስትሩ ዘ ዌል፡፡
  • ኪኪኪ . . .
  • ምን ያስገለፍጥሃል?
  • ስድቡ አስቆኝ ነው፡፡
  • ወይኔ፡፡
  • ወያኔ ነው ያሉኝ?
  • ምን ትቀባጥራለህ?
  • ግን ተዋረድን እኮ፡፡
  • በምንድን ነው የተዋረድነው?
  • በኦሊምፒክ ነዋ፡፡
  • እንዴት ሆኖ?
  • ይኸው በወንዶች አሥር ሺሕ ሜትር አሸነፈን እኮ፡፡
  • ማን ነው ያሸነፈን፡፡
  • ሞ ፋራህ ነዋ፡፡
  • ኃይሌ የት ሄዶ?
  • ክቡር ሚኒስትር እርሱ ውድድር ካቆመ ቆየ እኮ፡፡
  • ቀነኒሳስ?
  • እሱም የመመረጫ ውድድሩ ላይ አቋርጦ ወጣ፡፡
  • ታዲያ ማን ነበር የተሳተፈው?
  • አይ ክቡር ሚኒስትር በደንብ አላቃቸውም፡፡
  • እና ምንድን ነው ችግራቸው?
  • ያው በወንዶች እንደ ድሮ ማሸነፍ ተስኖናል፡፡
  • ለምንድን ነው ማሸነፍ የተሳነን?
  • እኔን’ጃ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ለመሆኑ ሯጮቻችን ልማታዊ ናቸው?
  • አዎን ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • በምን አወቅህ?
  • ሁሉም እኮ ሕንፃ እየገነቡ ነው፡፡
  • አየህ ውስጣቸው ግን ልማታዊ ላይሆን ይችላል፡፡
  • ምን እያሉ ነው?
  • ለመሆኑ በአብዮታዊ ዴሞክራሲ ተጠምቀዋል?
  • እነሱ እኮ ፖለቲከኞች ሳይሆኑ ሯጮች ናቸው፡፡
  • አየህ ችግሩ ይኼ ነው፡፡
  • የምኑ ችግር?
  • የማያሸንፉት ለዛ ነው፡፡
  • እንዴት ሆኖ?
  • አብዮታዊ ዴሞክራሲ ማለት ሌላ ትርጉሙ አሸናፊ ማለት ነው፡፡
  • በለው፡፡
  • እኛ በፓርላማ መቶ ፐርሰንት ያሸነፍነው ለዛ ነው፡፡
  • ይኼ እኮ ታይቶ የማይታወቅ ነው፡፡
  • አየህ አትሌቶቻችንም ታይቶ የማይታወቅ ድል እንዲያገኙ መጠመቅ አለባቸው፡፡
  • በምን?
  • በአብዮታዊ ዴሞክራሲ!
[ክቡር ሚኒስትሩን የውጭ ጋዜጠኛ ኢንተርቪው ሊያደርጋቸው ቢሯቸው ገባ]
  • ይህንን ቃለ መጠየቅ ለማድረግ ስለተስማሙ አመሰግናለሁ፡፡
  • እኛ የምንደብቀው ነገር ስለሌለ ችግር የለውም፡፡
  • ጥያቄዬን መጀመር እችላለሁ?
  • ቀጥል፡፡
  • በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ሕዝቡ ድምፁን እያሰማ ነው፡፡
  • እንግዲህ አገራችን እያስመዘገበችው ባለው ዕድገት ሕዝቡ ደስተኛ ስለሆነ በየቦታው የደስታ ድምፅ ሊሰማ ይችላል፡፡
  • አልገባዎትም ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ምኑ ነው ያልገባኝ?
  • ሕዝቡ በተለያዩ አካባቢዎች የተቃውሞ ድምፅ እያሰማ ነው?
  • እንዳልኩህ አገሪቱ 11 በመቶ እያደገች ስለሆነ ሕዝብ የእልልታ ድምፅ በየቦታው ያሰማል፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር እኔ ሕዝብ ስለሚያሰማው ተቃውሞ ነው የምጠይቀዎት?
  • በመስኮት እንደምትመለከተው ይኼ ሁሉ የሕንፃ ጫካ የልማቱ መገለጫ ነው፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር የተግባባን አይመስለኝም፡፡
  • እንዴት እንግባባለን?
  • የጠየኩዎትን ጥያቄ ለምን አይመልሱልኝም?
  • መለስኩልህ እኮ፡፡
  • ምን ብለው?
  • እያደግን ነው፡፡
  • አሁን የሕዝብ ችግር እየገባኝ ነው፡፡
  • ምንድን ነው?
  • የሚያዳምጠው የለም!