Wednesday, August 17, 2016

በተለያዩ ከተሞችና በአዲስ አበባ የተካሄዱ ሠልፎች ባስከተሉት ጫና ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ መከሰቱ ተሰማ፡፡


Reporter Amharic : ባለፈው ሳምንት በተለያዩ ከተሞችና በአዲስ አበባ የተካሄዱ ሠልፎችና ግጭቶች ባስከተሉት ጫና ምክንያት ወደ አዲስ አበባ ይገቡ የነበሩ የምግብ ሸቀጦች አቅርቦት እንደ ልብ እንዳይኖር ካለማስቻላቸው በተጨማሪ፣ ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ መከሰቱ ተሰማ፡፡
የሪፖርተር ምንጮች እንዳብራሩት ወደ ከተማው የገበያ ሥፍራዎች በየቀኑ ይገቡ የነበሩ እንደ አትክልትና ፍራፍሬ ያሉ በቶሎ የሚበላሹ ምርቶች፣ በተከሰቱት ግጭቶች ምክንያት ሊገቡ አልቻሉም፡፡ በተለይ በአትክልትና ፍራፍሬ ምርቶች በኩል ትልቁ የከተማ ገበያ በሆነው አትክልት ተራ ይህ ችግር ጎልቶ ታይቷል፡፡
ምንጮች እንደገለጹት፣ ምርቶቹን ከሚመረቱባቸው አካባቢዎች እንደ ወትሮው አጓጉዞ ለማስገባት ፀጥታ ችግሮች በመከሰታቸው፣ የሰው ሕይወትና ንብረት ላይ የሚደርሱ ጉዳቶችን ጨምሮ መንገዶች በመዘጋታቸው ምርት እንደሌላው ጊዜ ወደ ገበያዎቹ ሊመጣ አልቻለም፡፡
በዚህ ሳቢያ እጥረት ከመፈጠሩም በላይ በዋጋ ረገድም ከፍተኛ ጭማሪ ተከስቶ ቆይቷል፡፡ እስከ ሳምንቱ ማገባደጃ ድረስ የምርት አቅርቦቱ ቀድሞ በነበረው መጠን ሊሆን እንዳልቻለ ለማወቅ ተችሏል፡፡ በአትክልት ተራ ለአብነት በቀን በአማካይ እስከ 30 ተሽከርካሪዎች የቲማቲም ጭነት ይገባ ነበር፡፡ እስካለፈው ሳምንት ማገባደጃ ግን ከአራት ያነሱ ተሽከርካሪዎች በመግባት ላይ እንደሚገኙ ታውቋል፡፡
እንደ ምንጮች ማብራሪያ፣ ከግጭቶቹ በኋላ መጠነኛ መረጋጋት ቢታይም ከማክሰኞ ነሐሴ 10 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ያልታሰበና ምክንያቱ ያልታወቀ ጭማሪ እየታየ ነው፡፡ በግጭቱ ሰሞን ለአብነት አንድ ኪሎ ግራም ቲማቲም ከ20 ብር በላይ ሲሸጥ ታይቷል፡፡ ይህ ዋጋ ከግጭቱ ወዲህ በነበሩ ቀናት ወደ 16 ብር ቢቀንስም፣ መልሶ ወደ 20 ብር ገደማ በማሻቀብ ላይ ይገኛል፡፡
ከዚህም ባሻገር ዘግይተው እየገቡ የሚገኙ ምርቶች ብልሽት እየደረሰባቸው ወደ ገበያ በመግባት ላይ እንደሚገኙ የሪፖርተር ምንጮች ይጠቁማሉ፡፡ በጠቅላላው ሽንኩርት፣ ድንች፣ ቲማቲምና እንዲሁም ሌሎች ለዕለት ፍጆታ የሚውሉ የምግብ ሸቀጦች ላይ ያልተጠበቀ የዋጋ ጭማሪ ታይቷል፡፡ ምንጮች እንደሚሉት በዋጋውም ሆነ በምርት አቅርቦት መጠን ላይ ከቀን ወደ ቀን መሻሻል እየታየ ቢሆንም፣ ምርቶችን ወደ መሀል አገር ለማጓጓዝ አሽከርካሪዎች ሥጋት ውስጥ በመሆናቸው አሁንም እንደ ልብ እየቀረቡ አይደለም፡፡
ስለዚህ ሁኔታ ማብራሪያ እንዲሰጡ በንግድ ውድድርና ሸማቾች ጥበቃ ባለሥልጣን የገበያ ጥናት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ኤቲሳ ደሜን ለማነጋገር በተደጋጋሚ ቢሞክርም ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ ሪፖርተር ባደረገው የስልክ ጥሪዎች መረጃዎች እየተጠናቀሩ እንደነበር ቢገለጽለትም፣ ስብሰባ ላይ በመሆናቸው ከመንግሥት ወገን ያለውን መረጃ ለማወቅ አልተቻለም፡፡

No comments:

Post a Comment