Thursday, January 26, 2017

በአፋር የሚገኘው የኤርታዓሌ እሳተ ጎመራ ገንፍሎ እየፈሰሰ ነው

(ዘ-ሐበሻ) በመንግስት ቁጥጥር ሥር የሚገኙት የመገናኛ ብዙሃን ዛሬ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲን ጠቅሰው እንደዘገቡት በዓፋር ክልል የሚገኘው ኤርታዓሌ እሳተጎመራ ከፍተኛ እንቅስቃሴ አድርጎ ሞልቶ እየፈሰሰ ነው::
ፕሮፌሰር ገዛኸኝ ይርጉ ለመንግስት መገናኛ ብዙሃን በሰጡት መግለጫ “የዓለምና የአገር ውስጥ ቱሪስቶች መስህብ የሆነው አስደናቂው ኤርታዓሌ እሳተጎመራ ከባለፈው ሳምንት ጀምሮ ፍሳሹ ገንፍሎ መልቶና ከዋናው መያዣው ጉድጓድ ወጥቶ በብዛት እየፈሰሰ ነው:: የኤርተዓሌ የቀለጠው ዓለት ፍሳሽ አልፎ ተርፎ የተወሰነ ኪሎ ሜትሮችን ርቆ ሄዶ ሌላ ጕድጓድ ሞልቶ በተጨማሪ ወደ ደቡብ እየፈሰሰ መሆኑን ነው” ብለዋል::
ፕሮፌሰሩ ጨምረውም “አዲስ ክስተት የተፈጥረው ወደ ኤርታዓሌ መሄጃ በስተቀኝ በኩል አንድ ሌላ ስንጥቅ ተከፍቶ እንደዚሁ ተመሳሳይ ፍሳሽ ወይም ላቫ እየወጣና እየፈሰሰመሆኑን የአካባቢው ሰዎች ነግረውናል:: አከባቢው ሩቅ ነው በዙም ነዋሪም ስለሌለው በአሁን ሰዓት የሚያመጣው ችግር የለም፤ እየቀጠለ ከሄደ ግን አደጋ ሊያመጣ ይችላል” ካሉ በኋላ ሆኖም ግን እንዲያውም ወደ ደቡብ አቅጣጫ ወደ አፍዴራ ከተማ ፍሳሹ እየሄደ በመሆኑ ሁኔታው በዚሁ ከቀጠለና ካልቆመ አስቸጋሪ ሁኔታ ሊፈጠር እንደሚችል ማመልከታቸውን መንግስታዊ መገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል::

No comments:

Post a Comment