Tuesday, September 6, 2016

“የሰላም ኮንፈረንሱ” ሰላም አያሰፍንም! (ሳምሶን ኃይሌ)

የሰላም ኮንፈረንሱ” ሰላም አያሰፍንም!
(ሳምሶን ኃይሌ)
ሕዝባችን በወሮበላው የወያኔ ቡድን በኃይል የተነጠቀውን መሬት ለማስመለስ፣ ራሱን ያለ ወያኔ ጣልቃ ገብነት ለማስተዳደርና በአገር አቀፍ ደረጃ የሚገባውን ውክልና ለማስጠበቅ እየተዋደቀ እና ከፍተኛ መስዋዕትነት እየከፈለ ነው፡፡ የአማራ ሕዝብ መብቱን በሚጠይቅበት በአሁኑ ሰዓት፣ ነብሰ ገዳዩ የወያኔ ቡድን በሕዝባችን ላይ የዘር ማጥፋት ጦርነት ከፍቶ ሕጻናትንና እናቶችን ሳይቀር እየጨፈጨፈ ይገኛል፡፡ ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮሃል እንደሚባለው አሸባሪው ወያኔ በሕዝባችን ላይ ጦርነት የከፈተው ራሱ ሆኖ ሳለ፣ የአማራን ወጣቶች በጸረ ሰላምነትና በሁከት ፈጣሪነት ሲከስ እየታዘብን ነው፡፡ ጸረ ሕዝብም ሽብር ፈጣሪም የሰላም ጠላትም ራሱ ነብሰ ገዳዩ ወያኔ ሆኖ ሳለ፣ እንደለመደበት የሕዝብ ጩኸት ለመቀማት የማይፈነቅለው ድንጋይ የለም፡፡
በሚያሳፍር መልኩ የአማራ ወጣት ትዕግስቱ አልቆ ከመሣሪያ ጋር ትንቅንቅ እየገጠመ የወያኔን ጸረ ሕዝብ አገዛዝ የሚቃወመው “የሰላምን ዋጋ ባለማወቁ ነው” እየተባለ ነው፡፡ በእርግጥ ወያኔ ከዚህ ውጪ ሊያስብ አይችልም፡፡ ከእውነት ጋር አይተዋወቅምና፡፡ እኛ ግን በሕዝባችን ላይ የዘር ማጥፋት ጦርነት አውጆ ልጆቻችን የሚፈጀውና ሽብር የሚፈጥረው የሕዝባችን ግንባር ቀደም ጠላት የሆነው ወሮበላው ወያኔ መሆኑን አሳምረን እናውቃለን፡፡ በጎን “በዚህ በሰለጠነ ዘመን ችግሮቻችን በሰላም መፍታት ይገባል” እያለ፣ እዚያው በዚያው በሕዝባችን ላይ ግልጽ ጦርነት ያወጀውና ብዙ ንጹሐን ልጆቻችን የጨፈጨፈው፣ በብዙ ሺሕ የሚቆጠሩ ንጹሐን የአማራ ልጆችን በየእስር ቤቱ አጉሮ ቶርቸር የሚፈጽመው ወያኔ መቼም ቢሆን ለሰላም ቦታ ኖሮት አያውቅም፡፡
እንግዲህ በዚህ ሁኔታ ነው የአማራ ሕዝብ “የሰላም ኮንፈረንስ” በሚባለው ጉግማንጉግ እየተቀጠቀጠ ያለው፡፡ ሰላም እንዲሰፍን ካስፈለገ ልጆቻችን ያለምንም ቅድመ ሁኔታ መፈታት አለባቸው፡፡ ሆኖም የሁለተኛ ደረጃና የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ከእስር ተለቀው ወደትምህርት ገበታቸው መመለስ ሲገባቸው እስካሁን አልተፈቱም፤ ይልቁንም ወያኔ አሁንም እስሩንና ግድያውን ገፍቶበታል፡፡ በዚህ ሁኔታ ሰላም የለም፡፡ አይታሰብም፡፡ ልጆቻችን ታስረው የምን ሰላም ነው?
ወያኔ የችግሩ ዋና መነሻ የሆነውን የወልቃይት ጠገዴን ጉዳይ አስመልክቶ የሚያራምደው አቋምም ጨርሶ ሰላም የሚፈጥር አይደለም፡፡ ወያኔና ተላላኪው ጠቅላይ ሚኒስትር ለትግራይ ክልል ያመለከተ የወልቃይት ኮሚቴ የለም ብለው ተራ የዱርዬ ክህደት ፈጽመዋል፡፡ አሁን ደግሞ ይህን ርካሽ ንግግር በተናገሩበት አንደበታቸው፣ አንዴ የወልቃይት ኮሚቴ ጥያቄውን ለትግራይ ክልል ካቀረበ ችግሩ ይታያል ይላሉ፤ ሌላ ጊዜ ችግሩን ሁለቱ ክልሎችና ሁለቱ ድርጅቶች ተወያይተው ለመፍታት ተስማምተዋል እያሉ ይቀጥፋሉ፡፡ አንድ አስተዋይ የአማራ አርሶ አደር፣ “ሰውን ማመን ቀብሮ ነው፤ ወያኔን ማመን ግን በላዩ ላይ ሙጃ ከበቀለበት በኋላ ነው” ሲሉ የተናገሩት ትልቅ እውነት አለው፡፡ እውነትም ወያኔን ማመን በላዩ ላይ ሙጃ ከበቀለበት በኋላ ነው፡፡
ከዚህ የወያኔ ሰይጣናዊ ተፈጥሮ ተነስተን ነው፣ የሚሰበከው የሰላም ኮንፈረንስ ለውጥ አያመጣም፤ እንዲያውም ለበለጠ እልቂት ይዳርገናል የምንለው፡፡ ከዚህ በኋላ የመቀሌን መሬት የሚረግጥ የወልቃይት አማራ አይኖርም!! በኃይል የተወሰደውን መሬታችን ብንችል በኃይል እናስመልሰዋለን፤ እኛ ካልቻልን ጉዳዩን ለወንድሞቻችንና ለልጆቻችን አውርሰናቸው እናልፋለን፡፡ ከዚህ ውጪ ምንም ምርጫ የለንም፡፡ በወያኔ መንገድ ሰላም አይመጣም፤ ኖሮም አያውቅም፡፡
ሁሉም የአማራ ልጅ ለማይቀረው ትግልና መስዋዕትነት መዘጋጀት ይኖርበታል፡፡ በትግላችንና በመስዋዕትነታችን መሬታችን ይመለሳል!! ነጻነታችንም ይከበራል!! መፍትሔው ያለው በእጃችን ነው፡፡

No comments:

Post a Comment