Tuesday, September 20, 2016

የኮንሶው ቀውስ እያወዛገበ ነው :: ጥያቄያችን በኦሮሚያ ክልል እስከመጠቃለል ይዘልቃል::


በኮንሶ ስለተፈጠረው ተቃውሞና ግጭት የኮንሶ ጥያቄ ኮሚቴ አባል የሆኑትን አቶ ገመቹ ገንፌ በተፈጠረው ግጭት መነሻ ምክንያት ዙሪያ እንዲሁም አሁን ስላለበት ሁኔታ
“ጥያቄያችን በኦሮሚያ ክልል እስከመጠቃለል ይዘልቃል” አቶ ገመቹ ገንፌ፤ – የኮንሶ ኮሚቴ አባል
ከኮንሶ የዞንነት ጥያቄ ጋር በተያያዘ በተፈጠረ ግጭት የበርካቶች ህይወት ጠፍቶና በሺህ የሚቆጠሩ ቤቶች ተቃጥለው ዜጎች የተፈናቀሉሲሆን የኮንሶ ህዝብ ኮሚቴ፤ ጥያቄያችን ወደ ኦሮሚያ ክልል እስከመጠቃለል ይዘልቃል ብለዋል፡፡
በአካባቢው እስከ ትናንት ድረስ ግጭቶች መቀጠላቸውንና የታጠቁ የመንግስት ኃይሎች የተኩስ ልውውጥ ሲያደርጉ እንደነበር የኮንሶ ኮሚቴ አባል አቶ ገመቹ ገንፌ ለአዲስ አድማስ የገለፁ ሲሆን በሰሞኑ ግጭት ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ በርካታ ሰዎች መገደላቸውንና አስክሬናቸው እስከ ትናንት ድረስ ለቤተሰብ እንዳልተሰጠ ተገናግረዋል።
የኮሚቴው አባል አቶ ገመቹ፤ ጥያቄያችን በፌደሬሽን ምክር ቤት ተቀባይነት ካላገኘ በሪፈረንደም ወደ ኦሮሚያ ክልል ለመጠቃለል ጥያቄ እናቀርባለን ብለዋል፡፡
‹‹ወደ ኦሮሚያ ክልል መጠቃለል እንፈልጋለን”
በኮንሶ (ትናንት ነበር ቃለ ምልልሱ የተደረገው)
ያለው ሁኔታ ምን ይመስላል?
በኮንሶ (ትናንት ነበር ቃለ ምልልሱ የተደረገው) ያለው ሁኔታ ምን ይመስላል?
ከትናንት የቀጠለ በዞኑ ውስጥ ያሉ ሌሎች ወረዳዎች በማስተባበር፣ ተዋጊ ኃይሎች ከዚያ ውስጥ መልምለው በሁለት ቀበሌዎች ላይ የከፈቱት ጦርነት ዛሬም እንደቀጠለ ነው፡፡ ከቡርጂ፣ ከአማሮና ከደራሼ የተመለመሉ ተዋጊ ሚሊሺያዎችን በ9 መኪና አስተባብረው በኮንሶ ህዝብ ላይ አዝምተዋል፡፡ ሃሙስ ከሰዓት የጀመረው ግጭት ዛሬም (ትናንት) ቀጥሎ እንደዋለ ነው፡፡ ከዚያ ውጪ በሶስት ቀበሌዎች ላይ ባለፉት 3 እና 4 ቀናት በፊት የጀመሩት ዘመቻ ወደ ሌሎች ቀበሌያት እየተዛመቱ ነው፡፡ በተለይ ትናንት ማለዳ የኮሚቴ ተወካዮችን ቤት የማፍረስ፣ የመፈተሻ ስራ ውስጥ ናቸው፡፡ እቤት ያሉ ዶክመንቶች ተዘርፈዋል፡፡ በርካታ ሰዎች ታስረዋል፡፡ ያገኙትን ሰዎች በሙሉ እያሰሩ ነው፡፡ ዛሬ (አርብ) ማለዳ ብቻ 25 ሰዎች መታሰራቸውን መረጃው ደርሶናል፡፡ ህዝቡ በሰላማዊ መንገድ ጥያቄውን ለማቅረብ የተማማለ በመሆኑ ምንም የተለየ እንቅስቃሴ አላደረገም፡፡ እነሱ ግን ህዝቡን እያስጨነቁና እያስገደዱ ነው፡፡ በመሳሪያ አካባቢውን እያስጨነቁ ነው፡፡
ከዚህ በኋላ ምን እንደሚያደርጉ የምናውቀው ነገር የለም፡፡ ፍተሻውና ማዋከቡ ተጠናክሮ ቀጥሏል። የታሰሩ ሰዎችን መጠየቅ አይቻልም፤ ምግብም አያገኙም፡፡ ሰው ዘመድ ጥየቃ ከሄደ ይታሰራል። ኮንሶ ከአሁኑ ጊዜ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለች ሳትሆን በልዩ ፕላኔት ላይ የተቀመጠ፣ እንዲጠፋ የተፈረደበት ህዝብ ይመስላል፡፡ የመንግስት ሰራተኞች ደሞዝ እያገኙ አይደለም፤9 ወር ደሞዝ ያላገኙ አሉ። አካባቢው ድርቅ የሚያጠቃው እንደመሆኑ የሴፍቲኔት ተጠቃሚ የነበረ ነው፡፡ ይሄን እርዳታ አመቱን ሙሉ አላገኘም፡፡ ህፃናትና እናቶች ህክምና ማግኘት አልቻሉም፡፡
በግጭቱ በሰው ህይወትና ንብረት ላይ የደረሰው ጉዳት ምን ያህል ነው?
እስከ ነሐሴ 4 ሰው ተገድሎ ነበር፡፡ ሰሞኑ ግን የሟቾች ቁጥር በርካታ እንደሆነ ይገመታል፡፡ አስክሬን ማንሳት ስላልተቻለ ለማወቅ ያስቸግራል። አስክሬኖች ለቤተሰብ አልተሰጡም፡፡ ትናንት ማታ (ሀሙስ) 6 አስክሬኖች አንድ ቦታ ተቀምጠው ሰዎች እንዳያነሱ መሳሪያ እየተተኮሰ እየተጠበቀ ነው። በተለያየ አቅጣጫ አስከሬን ውሰዱ እየተባለም ከፖሊስ ጣቢያዎች ይደወላል፡፡ ግን ሰው ፈርቷል፤ ከሄደ እንታሰራለን ብሎ ይሰጋል፡፡ እስካሁን በእጃችን ተረክበን የቀበርነው ሁለት አስክሬን ብቻ ነው፡፡ አንደኛዋ ወልዳ ቤት ውስጥ ያለች አራስ ሴት ናት፤ በጥይት የሞተችው፡፡ አራስ ህፃኑ ወዴት እንደወሰዱት እናውቅም፡፡ ከሷ ውጭ ሌላ አንድ ሰው ተገኝቶ ተቀብሯል፡፡ ሌሎች ግን በርካታ ሰዎች ጠፍተውብናል፡፡ በርካታ ቤቶች ተቃጥለዋል፣ በርካቶች ተሠደዋል፡፡
የክልሉ መንግስት ችግሩ ከተፈጠረ በኋላ እናንተን ጠርቶ ለማናገር ሙከራ አድርጓል?
ከክልሉ መንግስት ጋር ልናደርግ የሚገባንን ውይይት ከዚህ ቀደም አድርገን አጠናቀናል። ጥያቄያችንን ለመመለስ ፍቃደኛ አይደለም፡፡ ጥያቄውን ካልመለሳችሁ፣ በቃ በዚህ ጉዳይ ከእናንተ ጋር መወያየት የለብንም፤ ነገር ግን በሌሎች ጉዳዮች ላይ እንወያይ ብለናቸው ነበር፤ ነገር ግን በጉዳዩ ላይ ውይይት የማናደርግ ከሆነ ሌላ የሚያገናኘን ነገር የለምና አናውያያችሁም የሚል ድምዳሜ ላይ የደረሱት፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ነው ሠራተኞቹ ደሞዝ አጥተው በሌሎችም ላይ ጫና እያደረሠ ያለው፡፡ ባለፈው ጊዜ በምክር ቤት ስብሰባም ሆነ በደህዴን ስብሰባ ‹‹ከዚህ በኋላ የኃይል እርምጃ ይወሰዳል›› ብለዋል፡፡
ህዝቡ ነው ሠላማዊ እንጂ እነሱ ነገሩን በኃይል ለማስተናገድ ነው የተዘጋጁት፡፡ ድርድር አያስፈልግም በሚል ነው የሃገር ሽማግሌዎችን እንኳ ለማነጋገር ሳይፈልጉ፣ የኃይል እርምጃ እየወሰዱ ያሉት፡፡
የሠራተኞች ደሞዝ ያለመከፈል ጉዳይ ላይ የክልሉ መንግስት ለፋና ሬድዮ በሠጠው ምላሽ፤ ‹‹የመንግስት ደሞዝ እንዳትቀበሉ›› በሚል ሰራተኞች ላይ ማስፈራርያ በመድረሡ ነው ያልተቀበሉት እንጂ ክልሉ ደሞዝ አይከፈልም አላለም ብለዋል እርስዎ ደግሞ ደሞዝ አልተከፈለም እያሉ ነው፡፡ ሁለቱን እንዴት ነው ማስታረቅ የሚቻለው?
የሚያሣዝነው ነገር ይሄ ነው፡፡ የክልሉ መንግስት ‹‹በሬ ወለደ›› ውሸት ነው የሚዋሸው፡፡ መንግስት እንደ መንግስት መዋሸቱ በጣም ያሳዝናል፡፡ ግለሠብ ሰዎች ቢዋሹ ምንም አይደለም፡፡፡ የሚዋሸው እኮ ወደፊት አስተዳድረዋለሁ የሚለውን ህዝብ ነው። ያንን ህዝብ እንዲህ እየዋሸ ነገ በምን ሞራል ነው ፊቱ መጥቶ የሚቀመጠው፡፡ አንድ ሰራተኛ ስራ ላይ የሚቀመጠው የስራ አከባቢው ደህንነትና ሰላም ሲጠበቅለት ነው፡፡
በኮንሶ ያለው እውነት ጥያቄውን ካልተዋችሁ መስራት አትችሉም ነው፡፡ ሠራተኛ ለስራ ሲሄድ ስብሰባ ነው የሚጠሩት፡፡ እኛ በኢትዮጵያ ህገ መንግስት መሰረት ነው የጠየቅነው፡፡ ጥያቄውን የማትመለሱ ከሆነ በስርአቱ በፅሁፍ ምላሽ ስጡን ነው  ያለው ህዝቡ፡፡ ይሄ ነው ያለው እውነታ፡፡  ሰራተኛ ሲወጣና ሲገባ ይታሠራል፡፡ የሰው ሃይል አስተዳደር ሃላፊዎች ሁሉ ከስራቸው ተባርረዋል። ሰራተኛውን በተለያዩ መንገዶች እያዋከቡ ነው። በመጨረሻ ላይ ያደረጉት ቢሮዎች መቆለፍ ነው። ቢሮ ከተቆለፈ በኋላ ሰራተኛ የት ገብቶ ይሰራል? ቢሮዎች ደግሞ በልዩ ሃይል ነው የሚጠበቁት። ሠራተኞች ወደ አካባቢው ከሄዱ ይደበደባሉ፣ ይታሠራሉ፡፡ ሠራተኛው ስራ ተው የሚሉት በዚህ መንገድ ነው፡፡ ለጥያቄያችን መልስ ስጡን ስንል ‹‹የትም ብትሄዱ የተለየ ነገር አታገኙም፡፡ ፌደራል ብትሄዱም እኛው ነን ያለነው ይሉናል፡፡ ሰራተኛው አማራጭ በማጣቱ ነው ቤቱ ቁጭ ያለው፡፡ የሚሉት ሁሉ ውሸት ነው፡፡
የክልሉ መንግስት ምላሽ ሰጥቻለሁ ብሏል፡፡ እናንተ ደግሞ ጥያቄያችንን እንቀጥላለን ብላችኋል በምን አግባብ ነው ጥያቄውን የምትቀጥሉት?
ጥያቄውን በአግባቡ አሁንም ቀጥለናል፡፡ የክልሉ መንግስት አመቱን ሙሉ አልመልስም ሲለን ቆይቶ፣ መጨረሻ ላይ አሁን ‹‹ባላችሁበት ቆዩ›› የሚል ምላሽ ሰጥቶናል፡፡ ይሄን ውሳኔ በመቃወም ወደ 81 ሺህ ሰው ፊርማ ተሰብስቦ፤ ወደ ፌደሬሬሽን ም/ቤት አስገብተናል፡፡ አሁን ጉዳዩ ያለው በፌደሬሽን ም/ቤት እጅ ነው፡፡
የፌዴሬሽን ም/ቤት አፈ ጉባኤ ለፋና ሬድዮ በሰጡት ምላሽ፤ ጥያቄው የማንነት ሳይሆን የአስተዳደር ጉዳይ ነው ሲል ምላሽ ሰጥቷል…
እኛ እንደውም ለፌዴሬሽን ም/ቤት ሁለት አማራጮች ነው ያቀረብነው፡፡ ፌዴሬሽን ም/ቤት ጥያቄያችንን ውድቅ የሚያደርግበት አንዳችም ህገ መንግስታዊ የሆነ መሠረት የለውም፡፡ ምክንያቱም ሟሟላት ያለብንን መስፈርት በሙሉ ነግረውን  አሟልተናል፡፡
ሶስት መስፈርቶች ነበሩ የነገሩን፡- አንደኛ የክልሉ የብሄረሠቦች ም/ቤት ውሳኔ፣ ሁለተኛ ይሄን ጥያቄ እንዲከታተሉ የተወከሉ ሰዎች ውክልና 3ኛ ደግሞ ከህዝቡ አጠቃላይ ብዛት 5 በመቶ ፊርማ ነበር የተጠየቅነው፣ እኛ ግን ወደ 26 በመቶ ህዝብ ፊርማ ነው ያቀረብነው፡፡ ስለዚህ ይሄን ጥያቄ ውድቅ የሚያደርግበት ምክንያት የለም፡፡ ይሄን ውድቅ የሚያደርግ ከሆነ በፊት ‹‹እዚህም ፌደራል ያለነው እኛው ነን፤ የትም ብትሄዱ አይሳካም›› የተባለው እውነት ይሆናል ማለት ነው፡፡
ምላሽ ካላገኛችሁ የመጨረሻው አማራጫችሁ ምንድን ነው የሚሆነው?
ሪፈረንደም እንጠይቃለን፡፡ ውድቅ የሚሆንብን ከሆነ ሪፈረንደም እንጠይቃለን፡፡ ከዚህ በኋላ ክልሉ እንደሚለው ኮንሶ በዚያ ዞን ውስጥ ተጠቃሎ ሊኖር አይችልም፡፡ ሪፈረንደም ስንል፣ አንድም ብቻችን እንደ አንድ ልዩ ዞን ሆነን፣ ተጠሪነቱ ለፌደራል መንግስት ሆኖ እንዲኖር፣ ካልሆነ ደግሞ ወደ ኦሮሚያ ክልል በዞንነት ለመጠቃለል እንጠይቃለን። የኮንሶ ህዝብ በባህልም፣ በቋንቋም፣ በማህበራዊ ስነ ልቦናም ሆነ ዋና ምንጩ ኦሮሚያ ስለሆነ፣ ወደ ኦሮሚያ ክልል መጠቃለል እንፈልጋለን፡፡ ኢህአዴግ ወደ ስልጣን እንደመጣ፣ የኮንሶ ህዝብ ወደ ኦሮሚያ ነው መሆን የምፈልገው ብሎ ህዝቡ የመረጠውን አንዳንድ ግለሰቦች አጭበርብረው ነው ወደ ደቡብ የጠቀለለው እንጂ የኮንሶ ህዝብ ድሮም ቢሆን ሲመርጥ የነበረው ከኦሮሚያ ጋር መኖርን ነው፡፡ የኦሮሚያ ክልል ደግሞ በአሁኑ ጊዜ የህዝቡን የዞንና የወረዳ ጥያቄ በአግባቡ እየመለሰ መሆኑን እያየን ነው፡፡
እንዲህ የህዝብን ችግርና ጥያቄ ሰምቶ ምላሽ የሚሰጥ ክልል እያለ እኛን ረግጦ እያማረረ፣ ከሚያስተዳድረን ክልል ጋር የምንኖርበት ምንም ምክንያት የለም፡፡

No comments:

Post a Comment