Thursday, September 22, 2016

ከእኛ በላይ ፉጨት ….. አፍ ማሞጥሞጥ! ከናሆም ግርማ


… ጅብ ብዙ ወለደች አሉ። ታዲያ ልጆችዋን አስቀድማ ስትጓዝ አንዳቸውም ሳይቀሩ ያነክሳል በሁኔታው በጣም አዝና ‘’ አያችሁ ልጆች ሁላችሁም ታነክሳላችሁ እናም ከእንግዲህ አረማመድ ከእኔ መማር አለባችሁ’’  ብላ ከፊታቸው ቀድማ ልታሳያቸው ሞከረች። ከእነርሱ በባሰ ሁኔታ ማነከሷን ያዩ ልጆች ….. ‘’ በነገርሽን ይበቃ ነበር’’ አሏት አሉ።
በዚህ በምኖርበት የምዕራቡ አገር ተወላጅ የሆነ አንድ ወዳጄ አንድ ቀን ‘’ለምንድን ነው ከሁሉም ስሞቻችሁ ጎን ’’ዲሞክራሲያዊ የሚል ቃልን የምታስቀድሙት ብሎ ይሽው እስከዛሬ ልመልሰው ያልቻልኩትን ጥያቄ እንደጠየቀኝ አስታውሳለሁ። አብዮታዊ
ዲሞክራሲያዊ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ፣ ፍትሀዊ፣ ዲሞክራሲያዊ… ኧረ ስንቱ በስሙ ውስጥ ካለው ትርጓሜ እና ተግባራዊነቱ አንፃር በአለም ከመጨረሻዎቹ አስር አገራት አንዱ ሆነን ሳለን የሀገራችን ፓስፓርት /passport/ እንኳን ሳይቀር በፊቱ ገፅ ላይ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፓብሊክ ተብሎ መገሸሩ እጅግ አስገራሚም አሳፋሪም ነው።
ከእኛ በላይ ፉጨት አፍን ማሞጥሞጥ ነው እንዲሉ ከክፋታቸው ይልቅ በጎነታቸውን ያጎላላቸው ይመስል ዛሬ የኢትዮጵያን የመገናኛ ብዙሀን ዜና ትእግስቱ ኖሮት ለአስር ደቂቃ ያደመጠ አንድ ሰው ሰላሳ ወዳጆቹን በየ እስርቤትና በየመቃብሩ እንዳልሸኘ ሁሉ ሰላሳ ግዜ ዲሞክራሲያዊ ውይይይ፣ ዲሞክራሲያዊ ልማት፣ ዲሞክራሲያዊ ትግል፣ ዲሞክራሲያዊ ምክክር፣ ዲሞክራሲያዊ ተሳትፎ….. ወዘተ የሚሉ ቃላትን መስማቱ አይቀሬ ነው ሌላው ቀርቶ 95 ሚሊዮን ህዝብን ይወክላል ብለው በሚዘምሩት ብሄራዊ መዝሙር ውስጥ እነ ዲሞክራሲ እነ ፍትህና የህዝብ ክብር የተሰኙ ቃላቶች ተሰልፈው ሲዜሙ ምን ያህል ወያኔ በዜማ እና በአሽሙር እያላገጠበት መሆኑን መረዳት ይቻላል።
በአሜሪካን የሚገኘው የአልበርት አነስታይን ተቋም በየወቅቱ የዲሞክራሲን ፅንሰ ሀሳብ በተለይ ሰሶስተኛው ዓለም አገሮች ከአምባ ገነንነት ወደ ዲሞክራሲ ሽግግር በሚል በተለታዩ ጊዜ የፅንሰ ሀሳብ ንድፎችን እየነደፈ ያስነብባል። እናም ታዲያ እ.ኤ.አ በሜይ 2010 በአራተኛ ህትመቱ ላይ በተለይ በአለም ታሪክ የሰው ልጆችን በደቦ በመግደል ወደር ያልተገኘለትን ጨካኙን ሂትለር ግራዚያኒን ጠቅሶ ሰውዬው ሰላም ነፃነትና ፍትህ የተሰኙ ቃላቶችን በንግግሩ ውስጥ በመጠቀም ወደር ያልተገኘለት እንደነበረ ያስነብበናል።
ታዋቂዋ የእንግሊዝ ገጣሚና አክቲቪስት አላይስ አስዋርድ /Alice osward/ ደግሞ ዲሞክራሲን በመልካም ዝናብ ትመስለዋለች። በተመጠነ ጠብታ፣ በሁሉም ስፍራ በእኩልነት ከላይ የሚወርድ ቢመስልም በጎ ሀገራት በሌሉበት ሀገራት ላይ ስሙ ብቻ ስለሚገን ጎርፍ ሆኖ ብዙሀኑን ጠራርጎ መጨረሱ አይቀሬ ነው ትለናለች።
ታዲያ ዛሬ ሀሳብን ለምን ተናገርክ ተብሎ በየጎዳና በጥይት የሚቆላው ወገናችን የተፃረረው የትኛው ዲሞክራሲ ህገ መንግስት እንደሆነ ከቶም ሊገባን አልቻለም። ምክርና ቡጢ ለሰጪው ቀላል ነው እንዲሉ የዛሬው መንግስት ተብዬው ምክሩንም ቡጢውንም እራሱ እየሰጠ ዲሞክራሲ ዘንቦልሀልና እምልህን ብቻ አድምጥ ብሎ በግድያና በእስር ጎርፍ መጥረጉ በእጅግ ያሳዝናል።
መቼም የወያኔ ዲሞክራሲ ቃሉ ሲፈታ ከሰሙ ይልቅ ወርቁ ይልቃልና መንገድ በተቆፈረለት ጉድጓድ በተቀለሰለት መንገድ፣ በተማሰለት ቦይ መፍሰስ ብቻ ግድ ሆነ። በመሆኑም በቃኝ ያለ ህዝብ፣ ተበደልኩ ያለ ወገን ቀለቡ ጥይት እንጂ ከቶም ሰሚ ጆሮ አይደለም። ዲሞክራሲ ለወያኔ፣ ነፃነት ለህወሀት ሰሙ ነው እንጂ ወርቁ እኔ ያልኩትን ተቀበል፣ እኔ ያልኩህን ስማ፣ ያለ እኔ ማንም አያውቅልህም ማለት እንደሆነ ግልፅ ነው። የአገዛዙ ተጠቃሚና ባለ ካዝናዎች እንደ መሪያቸው የሚያነክሱና ራስ ወዳዶች የራሱ ብሄር ዘሮች መሆናቸው እንኳንስ ሰፊው ህዝን አለም ሁሉ ጠንቅቆ ያውቀዋል።
ለአንድ ሀገር ማንነቱ በውስጡ ያለው ህዝብ ነው። ሀገር ያለ ህዝብ ህዝብ ደግሞ ያለሀገር አይኖርም። በመሆኑም የአንድ ሀገር ምሉእነት አገሩቷ በእኩልነት የሁሉም መሆን የቻለች ጊዜ ብቻ ነው። ወያኔ የመረጠውን ዘርና የተመቸውን አካል ብቻ ይዞ አገርን አስተዳድራለሁ ሊለን አይችልም። መሆኑም በዲሞክራሲ ስም ብቻ ሰፊውን ህዝብ የሚበላ በልቶም የሚጨርስ የአገዳ ትል እንጂ ከቶም ለህዝባችን የሚበጅ መንግስት እንዳልሆነ ልብ ሊሉ ይገባል።
ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኖራለች

No comments:

Post a Comment