Wednesday, September 14, 2016

የኮንሶ የድረሱልን ጥሪ– የአድማጭ ያለህ !!!


የኮንሶ የድረሱልን ጥሪ– የአድማጭ ያለህ !!! – ይጠይቃሉ ?? ?? ?? ?? ?? ይህን ጥያቄ ለአገራችን የፖለቲካ ኃይሎችና ልህቃን አድርስልን ፣አደራ ያሉን የኮንሶ ህዝባዊ እምቢተኝነት በንቃት እየተሳተፉ ያሉ ወጣቶች፣ የመንግስት ሠራተኞችና በህግ ሙያ /ዳኝነት ሥራ የተሰማሩና በክረምት የዩኒቨርስቲ ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ የሚገኙ የህዝቡ ብሶት ተጋሪ የኮንሶ ልጆች ናቸው፡፡
ከየትኛው ዳገት ላይ ሆነን ስንጮህ ይሆን ድምጻችንን የምትሰሙት (ዘጠኝ ወራት ሙሉ ከከተማ እስከ ገጠር፣ ከክልል እስከ ፌደራል መንግስት ፣ አልፎም በአደባባይ ለዓለም ህዝብ ጮሄናል) ? ከዚህ የከፋ ምን ሲደርስብን ይሆን ህመማችን የሚያማችሁ (ወጣቶች የጥያት እራት የሆኑበት፣ መንደር ሙሉ ተቃጥሎ ነዋሪው የተሰደደበት፣ አምስት ወር ሙሉ ደመወዝ የተከለከለበት፣ …) ? ምን ስናደርግ ይሆን ከትግላችን ተሞክሮ የምትቀስሙት (የባህል መሪ፣ ኃይማኖት አባቶች፣ ከህጻናት እስከ አረጋዊያን፣ ከመንግስት ሠራተኛ እስከ አርሶአደር፣ ከገጠር እስከ ከተማ፣…በአንድ የቆሙበት፣ተፈናቃይና ተጎጂዎችን ህዝቡ በአቅሙ የደገፈበት ..) ? የተበጣጠሰና የተከፋፈለ የተናጠል ትግል መስዋዕትነቱን ያበዛዋል፣ የመከራና ሥቃይ ጊዜኣችንን ያረዝመዋል፡፡
በተለያዩ የአገራችን ክፍሎች የሚደረጉትን የ‹በቃኝ› ህዝባዊ እምቢተኝነት የለውጥ ትግል አስተባብሮና አቀናጅቶ የሚመራ አንድ ጠንካራ ፖለቲካዊ ኃይል/ማዕከል ያለመፈጠሩ ነው እነዚህን ጥያቄዎች እንድናነሳ ያስገደደን፡፡ እርግጥ ነው በአገር ውስጥም በውጪም የሚታየው ከመቼውም ጊዜ የተለየ የአንድነት /ትብብር ስሜት የሚያበረታታን የትግል ስንቅ ሆኖናል፤ ግን እስከመቼ ነው ከፖለቲካ ኃይሎችና የአገራችን ልህቃን በዚህ መልክ በተናጠል ስንመታ፣ ስንታፈን በተናጠል ቆማችሁ የምትመለከቱት ? ስለምንስ የአገራችን የፖለቲካ ኅይሎችና ልህቃን በአንድ መቆም ተሸነፋችሁ ? የድረሱልን – የአድማጭ ያለህ ጥሪያችን- የኮንሶ ህዝብ ብቻውን በተናጠል የድል፣ የመብቱና ነጻነቱ ባለቤት አይሆንምና ስለ ኮንሶ ህዝብ ብቻ አይደለም ፡፡ጥያቄኣችን ኢትዮጵያዊ ነው፤ ይህን በአራቱም የአገራችን አቅጣጫ የተፋፋመውን ህዝባዊ እምቢተኝነት የሚያስተባብር አንድ የአመራር ኃይል/ ማዕከል በመፍጠር፣ ትግሉን በማቀናጀት፣ በዝቅተኛ ዋጋ የሥቃይ ዘመናችንን ለማሳጠር በአንድ የምትቆሙት ወይም ምክክር እንኳ የምትጀምሩት ወይም በቪዥን-አትዮጵያ/ኢሳት የተጀመረውን የምትቀጥሉት፣ የምስራች የምታሰሙን መቼ ነው የሚል፡፡
ለዚህ ተግባራዊ የጋራ መልስ እንጂ የተናጠል ድርጅታዊ መግለጫችሁ፣ በመገናኛ ብዙሃንና በሰልፍ መርዶኣችን መንገራችሁ ፣ የመረረ ሃዘናችንን መግለጻችሁና ማስተጋባታችሁ፣… የዲፕሎማሲያዊ ዘመቻችሁ ፣ ትግሉን ቢያግዝም ፣ለድሉ አስተዋጽኦ ቢኖረውም …የሚከፈለውን መስዋዕትነት በሚቻለው መጠን አይቀንሰውም፣ የድሉን ቀን እስከሚቻለው አያቀርበውም፣ ከድል በኋላ የሚመጣው ለውጥ ዘላቂ፣አስተማማኝና የተረጋጋ ለመሆኑ መተማመኛ አይሆንም፡፡ ስለዚህ አሁንም ደግመን ደጋግመን የምንጠይቃችሁ- መቼ ነው– አገራችንን ህዝባችን ላይ ስለደረሰውና እየደረሰ ስላለው፣ የጋራ ድምጻችሁን የምንሰማው፣ የተቀናጀ የትግል አመራራችሁን፣ … የምንጠብቀው፣ አስተማማኝና ዘላቂ የጋራ የመፍትሄ አማራጫችሁን በትብብር የምታቀርቡል ??
በድል ታጅበን ከአዲሱ የለውጥ ዘመን ለመድረስ የጀመርነውን ጉዞ በጋራና በመተባበር አጠናክረን እንቀጥል፣ ወደፊት፡፡
አዲስቱ አንዲት ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኖራለች፤ አንጠራጠርም፡፡ መስከረም 03/ 2009 ፡፡

No comments:

Post a Comment