Tuesday, September 6, 2016

በቃለቲ ወህኒ ቤት በጥይት ተመተው ከቆሰሉት 2 ታሳሪዎች መካከል አንዱ ተደብድቦ መገደሉ ታወቀ፡፡


መንግስት በጥይት መቶ ያቆሰለውን እስረኛ በሚሰቀጥጥ ሁኔታ ደብድቦ ገደለ
7 የሚሆኑ የኦሮሚያ ተወላጅ እስረኞችም ለሕዝቡ የድረሱልን ጥሪ እያሰሙ ነው
በቃለቲ ወህኒ ቤት በጥይት ተመተው ከቆሰሉት 2 ታሳሪዎች መካከል አንዱ ተደብድቦ መገደሉ ታወቀ፡፡ ከ2 ቀናት በፊት ቅዳሜ ነሐሴ 28/2008 ለሊት የቃሊቲ እስርቤት ጠባቂዎች 2 እስረኞችን ገድለው 2ቱን ደግሞ ማቁሰላቸው ተዘግቦ ነበር፡፡ ዛሬ በደረሰኝ መረጃ መሠረት ከ2ቱ በጥይት ቆስለው ከተረፉት እስረኞች መካከል አንዱን የእስርቤቱ ታጣቂዎች እሁድ ነሐሴ 30/2008 በአሰቃቂ ሁኔታ ደብድበው እንደገደሉት ለማወቅ ችያለሁ፡፡ ይህም በቃሊቲ እስርቤት ባለፉት ቅዳሜ እና እሁድ የተገደሉት እስረኞችን ቁጥር ወደ 3 ከፍ ያደርገዋል፡፡ በተጨማሪም እነዚህ አራቱም እስረኞች የአማራተወላጆቹ ሲሆኑ ይህ በጥይት ከቆሰለ በኋላ በሚዘገንን ሁኔታ ተደብድቦ የተገደለው ወጣትም ስሙ ወንዴ እንደሚባልና በቃሊቲ እስርቤት በዞን 1 ታስሮ እንደነበርም መረጃው ያስረዳል፡፡

በተያያዘ ዜናም ከ14 አመት በፊት መስከረም 01/1995 በአዲስ አበባ ፒያሳ በሚገኘው ትግራይ ሆቴል መንግስት እራሱ አቀናብሮታል ተብሎ በሚጠረጠረው የቦምብ ፍንዳታ ተወንጅለው በእነ መስፍን መዝገብ የተከሰሱ በሚል የሚታወቁትና ከ20 አመት እስከ እድሜ ልክ እስራት የተበየነባቸው በእስር የሚገኙት 7 የኦሮሚያ ተወላጆች የድረሱልን ጥሪ እያሰሙ ይገኛሉ፡፡ እነዚህን ታሳሪዎች የቃሊቲ እስርቤት አስተዳደር አስጠርቷቸው ቀጣዩ የርሸና ተራ የእነሱ መሆኑን የዛተባቸው ሲሆን ‹‹እርምጃ ቢወሰድባችሁ ቢበዛ የሚዲያ ሽፋን ታገኛላችሁ እንጂ ምንም አታመጡም›› በማለት በቀጣይ ሊፈፅምባቸው ያሰበውን የግድያ ወንጀል አስረግጦ ነግሯቸዋል፡፡ ከቀናት በፊት በቅሊንጦ እስርቤት እስረኞችን እስከነ ሕይወታቸው በቁም ያቃጠለው አረመኔው መንግስት ይህን ዛቻውን ከመፈፀም ወደኋላ እንዲል የሚያደርገው ነገር ይኖራል ተብሎ አይጠበቅም፡፡

እኚህ 7ቱ ታሳሪዎችም በአሁኑ ወቅት ከፍተኛ ጭንቀት ውስጥ የሚገኙ ሲሆን በአምባገነኑ መንግስት እርምጃ ሳይወሰድባቸው በፊት የኢትዮጵያ ሕዝብ እንዲደርስላቸው በእጅጉ እየተማፀኑ ይገኛሉ፡፡

የእያንዳንዱ እስረኛ ሕይወት መንግስት ጫንቃ ላይ ያለ በመሆኑ በየጊዜው በሚጠፋው ሕይወት ሁሉ የዚህ ድራማ አቀናባሪ ባለሥልጣናት በፍፁም ከጥያቄ ሊያመልጡ አይችሉም!

በሕግ ስር የሚገኙ እስረኞችን መረሸን ይቁም!

No comments:

Post a Comment