Thursday, February 23, 2017

በጃናሞራ የዐማራ ገበሬዎች በአገዛዙ ላይ ተቃውሞ እንዳነሱ ተሰማ

   


በጃናሞራ የዐማራ ገበሬዎች በአገዛዙ ላይ ተቃውሞ እንዳነሱ ተሰማ | ኃይለማርያም የወልቃይት የዐማራ ብሔርተኝነት ጥያቄን ካዱ
ከሙሉቀን ተስፋው

– የዐማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኛዎች በዳኛ ቢኒያም ዮሐንስ ላይ የተወሰደውን እርምጃ ተቃወሙ፤
– በጃናሞራ የዐማራ ገበሬዎች በአገዛዙ ላይ ተቃውሞ እንዳነሱ ተሰማ፤
– በወገራ የገበሬዎች ቤት የወያኔ ወታደሮች ካምፕ እንደሆነ ተገለጸ
– ኃይለ ማርያም ደሳለኝ የተነሳ የማንነት ጥያቄ የለም ሲሉ የወልቃይት የዐማራ ብሔርተኝነት ጥያቄን ክደዋል
– በነማስረሻ ሰጤ መዝገብ የተከሰሱ የዐማራ ወጣቶች በሐሰት ውንጀላ ጥፋተኛ ተባሉ፤

ዝርዝር፤
፩ ትናንት የካቲት 14 ቀን 2009 ዓ.ም. በሰሜን ጎንደር ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት ዳኛ የሆኑት አቶ ቢኒያም ዮሐንስ ችሎት ላይ እንዳሉ የወያኔ ደኅንነቶች አፍነው መውሰዳቸውን ተከትሎ የዐማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኞች ዛሬ ተቃውሟቸውን መግለጻቸው ተሰምቷል፡፡ ዳኞቹ የፍርድ ቤትን አሠራርንና ሕገ መንግሥትን በጠራራ ፀሐይ ሙልጭ አድርጎ የጣሰ የማፍያ ሥራ መሆኑን ለፍትኅ ቢሮ አስታውቀዋል ተብሏል፡፡ ወያኔ ምንም እንኳ በዳኞች ውሳኔ ላይ ጣልቃ በመግባት ይህ የመጀመሪያው ባይሆንም እንዲህ ያለው ዐይን ያወጣ የማፍያ ሥራ ግን በታሪክ ታይቶ አይታወቅም ሲሉ ተችተዋል፡፡ አብዛኛዎቹ ዳኞች መደበኛ ሥራቸውን እንዳላከናወኑ ተገልጧል፡፡
አቶ ቢኒያም ዮሐንስን እንዲታሰር ያደረገው አዲሱ የጎንደር ማረሚያ ቤት ሹም የትግራይ ተወላጁ ጀማል ሰኢድ ሲሆን በዳባት ማረሚያ ቤት በነበረ ጊዜ ለበርካታ ወጣቶች እንግልትና ሞት ተጠያቂ እንደሆነም መረጃዎች እየወጡ ነው፡፡
፪ በሰሜን ጎንደር ዞን የጃናሞራ ዐማራ ገበሬወች ዛሬ የካቲት 15 ቀን 2009 ዓ.ም ተጋድሎ መጀመራቸው ተሰምቷል፡፡ ገበሬዎቹ የወልቃይት ጠገዴ ጠለምት ጉዳይ በአስቸኳይ መፍትሔ ካልተሰጠው እና በዐማራ ወጣቶች ላይ የሚደርሰው ግድያ እና እስራት ካልቆመ ተጋድሏቸውን እንደማያቆሙ ተነግሯል፡፡ በአካባቢው የስልክ አገልግሎት አስቸጋሪ በመሆኑ ዝርዝር ጉዳዮችን ማግኘት አልቻልንም፡፡
፫ በተያያዘ ዜና ደግሞ በወገራ ወረዳ የእንቃሽ አካባቢ ገበሬዎች መኖሪያ ቤቶች ወደ ወታደር ካምፕነት መቀየራቸውን የጎብዝ አለቆች ገልጸውልናል፡፡ ‹‹ቤታችን አቃጥለውት እንደገና ለመሥራት እየሞከርን ነበር፤ ሆኖም ባለፈው ሳምንት መጥተው እንደገና ጦርነት ከፈቱብን፡፡ ተታኩሰን ወደ ጫካ ወጣን፡፡ ካልያዝን ወይም ካልገደልን አንመለስም ብለው ቤታችንን እንደካምፕ እየተጠቀሙ እዚያው እየኖሩ ነው›› ሲሉ አንድ የጎበዝ አለቃ ማምሻውን ገልጾልናል፡፡ እንደ ጎበዝ አለቃዎቹ ገለጻ አሁን ላይ ዝናብ እየዘነበ ሲሆን እርሻም ማረስ የሚጠበቅ ቢሆንም በግፍ ከቤታችን ተፈናቅለን በጫካ ለመኖር ተገደናል ብለዋል፡፡
፬ የወያኔዎቹ አሽከር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ትናንት ባአከር ኹመራ ላይ ከትግሬ ሰፋሪዎች ጋር ባደረገው ንግግር የተነሳ የማንነት ጥያቄ የለም ሲል እንዲናገር የታዘዘውን አስተጋብቷል፡፡ ይህም በመቶ የሚቆጠሩ የዐማራ ወጣቶች ሕይወት የጠፋበትን የወልቃይት ጠገዴ የዐማራ ማንነት ጥያቄን ነው የደመሰሰው፡፡ በሌላ በኩል የብአዴኑ ደመቀ መኮነን በሳምንቱ መጀመሪያ ከጎንደር ከተማ ሕዝብ ጋር ባደረገው ስብሰባ የወልቃይት የማንነት ጥያቄ ዋናው የመወያያ አጀንዳ እንደነበር እንዲሁም እርሱም በአፋጣኝ ሊፈታ እንደሚችል ተናግሮ ወጥቷል፡፡ የፋና ብሮድካስቲንግ የወልቃይት ጠገዴን የማንነት ጥያቄ አፈታት በተመለከተ ዜና ሰርቶ በወያኔዎች ትእዛዝ ወዲያውኑ አንስቶታል፡፡ ስለሆነም ከትግሬ ጠባብ ብሔርተኞች ጋር የሚደረገው የሞት የሽረት ተጋድሎ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የአካባቢው ተወላጆች ተናግረዋል፡፡
፭ በነማስረሻ ሰጤ የክስ መዝገብ በተከሰሱ 6 የዐማራ ወጣቶች ላይ የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ 4ኛ ምድብ ችሎት የእስር ውሳኔ መስጠቱ ተገልጧል፡፡ በስድስቱ የዐማራ ወጣቶች ላይ የቀረበው ክስ ከግንቦት 7 ጋር የተያያዘ እንደሆነና ከ6 እስከ 10 ዓመት የሚደርስ ጽኑ እስራት መሆኑን መረጃውን የላኩልን ሰዎች ተናግረዋል፡፡
የዐማራ ተጋድሎ ያሸንፋል/

No comments:

Post a Comment