Tuesday, February 14, 2017

በእነ ጉርሜሳ አያኖ (አቶ በቀለ ገርባ እና የኦፌኮ አመራሮች ) መዝገብ ቀሪ የአቃቤ ህግ ምስክሮችን አቃቤ ህግ ማቅረብ አልቻለም | የአቃቤ ህግ ምስክር የመሰማቱ ሂደት ተጠናቋል

(የካቲት 3/2009)

በእነ ጉርሜሳ አያኖ መዝገብ አቃቤህግ የቀሩኛል ያላቸውን ሁለት ምስክሮች ለመጨረሻ ጊዜ አቅርቦ እንዲያሰማ ለየካቲት 3 2009 ተቀጥሮ ነበር። አቃቤ ህግ በዛሬው ችሎት ይቀሩኛል ያላቸው ሁለት ምስክሮች እንዳልቀረቡ ገልፆ፤ አንደኛው ምስክር ለፓሊስ ቃሉን ሲሰጥ ባስመዘገበው አድራሻ ሊገኝ አለመቻሉን እና በጠቀሰውም አድራሻ እንደማይኖር ከቀበሌ የተፃፈ ማስረጃ እንዳቀረበ ተናግሯል። ይህ ምስክር በዳዳ ድሪብሳ የሚባል ሲሆን 2ኛ ተከሳሽ በሆነው ደጀኔ ጣፋ ላይ ይመሰክር የነበረ መሆኑን አቃቤ ህጉ ተናግሮ፤ ምስክሩ ለፓሊስ የሰጠው ቃል በወንጀለኛ መቅጫ ስነስረአት ህግ 145 መሰረት በማስረጃነት እንዲያዝለት ጠይቋል።
ሁለተኛውን ምስክር በተመለከተ ፓሊስ እንዲያቀርበው ወይም በአድራሻው እንደማይገኝ የሚገልፅ ማስረጃ ከቀበሌ እንዲያቀርብ ታዞ እንደነበረ አቃቤ ህግ አስታውሶ፤ ፓሊስ ምስክሩን ያላቀረበበትን ወይም በአድራሻው የማይገኝ መሆኑን ማስረጃ ያላቀረበበትን ምክንያት ቀርቦ እንዲያስረዳ ተለዋጭ ቀጠሮ እንዲሰጥ ጠይቋል። ይህ ምስክር አንገፎ አብደላ እንደሚባል እና 3ኛ ተከሳሽ አዲሱ ቡላላ ላይ ይመሰክር የነበረ መሆኑን አቃቤ ህግ ተናግሯል።
የ2ኛ እና 3ኛ ተከሳሽ ጠበቃ የሆኑት አቶ አብዱልጀባር ሃሰን አቃቤ ህጉ ያቀረባቸው ጥያቄዎች ተገቢ አይደሉም ሲል የሚከተሉትን ነጥቦች በመከራከሪያነት አቅርበዋል።
1ኛ በባለፈው ቀጠሮ ለዛሬ ቀጠሮ ሲሰጥ የመጨረሻ ተብሎ ነበር
2ኛ በባለፈው ቀጠሮ ምስክሮች በአድራሻቸው አለመገኘታቸውን የሚያሳይ ማስረጃ ፓሊስ እንዲያቀርብ በተደጋጋሚ ታዞ አለማምጣቱ ስህተት መሆኑ ተገልፆ ስለነበረ አሁን ተጨማሪ ጊዜ ሊፈቀድ አይገባም
3ኛ በወንጀለኛ መቅጫ ስነስርአት ህጉ 145 መሰረት ለፓሊስ የተሰጠ ቃል በማስረጃነት እንዲታይ ቢፈቅድም አንቀፅ 145(2) ላይ እንደተገለፀው ምስክሩ ችሎት ቀርቦ የመሰከረው እና ለፓሊስ የሰጠው ቃል በሚለያይበት ወቅት (አስጠቂ ምስክር የሆነ) እንደሆነ በግልፅ ያስረዳል። አቃቤ ህግ ለፓሊስ የሰጠው የምስክር ቃል ይያዝልኝ የተባለለት ምስክር ደግሞ በችሎት ቀርቦ የመሰከረ አይደለም። እንዲሁም በህገመንግስቱ አንቀፅ 20(4) የተደነገገውን አንድ ተከሳሽ በምስክርነት የቀረበበትን ሰው የመጠየቅ (መስቀለኛ ጥያቄ) መብት የሚጥስ ነው። መስቀለኛ ጥያቄ እና የፍርድ ቤት የማጣሪያ ጥያቄ ያልቀረበበት የምስክርነት ቃል መያዝ አይኖርበትም።
4ኛ ምስክሩ ለፓሊስ ቃል ሲሰጥ አድራሻውን የተሳሳተ (የማይገኝበትን አድራሻ) ማስመዝገቡ፤ የሰጠው ምስክርነት የሃሰት መሆኑን ግምት መያዝ ይቻላል።
2ኛ ተከሳሽ ደጀኔ ጣፋም የሚከተሉትን ተጨማሪ ሃሳቦች አንስቷል።
– ምስክሮች ችሎት ቀርበው ቃለመሃላ የሚፈፅሙበት አንዱ ምክንያት የቃላቸውን እውነተኝነት ለማረጋገጥ ነው። ይህ ባልሆነበት ሁኔታ ቃሉ መያዝ አይኖርበትም።
– ኢትዮጵያ ተቀብላ ያፀደቀችውን በአለም አቀፍ ሰብአዊ መብት ኮንቬክሽን አንቀፅ 9(4) የተደነገገውን የተፋጠነ ፍትህ የማግኘት መብት እና ተያያዥ መብቶችን ይፃረራል።
– ምስክሩ ከግዴታው መሸሹ እራሱ ተአማኒነት የሌለው ምስክርነት እንደሆነ ያሳያል።
– ምስክሮች አድራሻ መሰወራቸው የሰጡት የምስክርነት ቃል እምነት ይጣልበታል ተብሎ አይታመንም።
ደጀኔ ጣፋ ፍርድ ቤቱ ከላይ የጠቀሳቸው ሃሳቦች ከግምት ውስጥ አስገብቶ የተፋጠነ ፍርድ እንዲሰጠን ሲል ጥያቄ አቅርቧል።
ዳኞች በአቃቤ ህግም በተከሳሾች በኩልም የቀረበውን ክርክር አድምጠው ውሳኔ ሰጥተዋል። አቃቤ ህግ ቃሉ እንዲታይለት የጠየቀለትን ምስክር በተመለከተ፤ የወንጀለኛ መቅጫ ስነስርአት ህጉ አንቀፅ 145 (2) ምስክሩ ፍርድ ቤት ቀርቦ ምስክርነቱን የሰጠ እንደሆነ ብቻ እንደሚሰራ፤ ምስክሩ ደግሞ ፍርድ ቤት ቀርቦ ምስክርነት ስላልሰጠ ለፓሊስ የሰጠው ቃል መያዝ የለበትም ሲሉ ውሳኔ ሰጥተዋል። ፓሊስ ማስረጃ ያላቀረበበትን ሌላኛው ምስክር በተመለከተ፤ በባለፈው ችሎት ፓሊስ በአካል ቀርቦ የመጨረሻ ቀጠሮ ተብሎ ተሰጥቶት ስለነበረ ተጨማሪ ቀጠሮ መሰጠት የተከሳሾችን የተፋጠነ ፍትህ እንዳያገኙ ያጓትታል፤ ስለሆነም አቃቤ ህግ የጠየቀውን ተጨማሪ ቀጠሮ ተገቢ አይደለም በማለት ውሳኔ ሰጥተዋል።
ከውሳኔው በኋላ አቃቤ ህግ የሲዲ ማስረጃ እንዳለው ጠቅሶ ለማሳየት ቀጠሮ እንዲሰጠው ጠይቋል። በዚህም መሰረት የካቲት 10/2009 ቀን ሲዲውን በችሎት ለማየት ቀጠሮ ተይዟል። ከቀጠሮው ቀን ቀደም ብሎ ሲዲውን ለዳኞች እንዲያቀርብ አቃቤ ህግ ታዟል። የተከሳሾች ጠበቃ አብዱልጀባር የሲዲ ማስረጃ በሚቀርብበት ጊዜ በኤግዚቢትነት የተያዙ እቃዎችም እንዲቀርቡ እንዲታዘዝ ጠይቆ የነበረ ቢሆንም ዳኞች መዝገቡን በምንመረምርበት ወቅት አስፈላጊ ሆኖ ካገኙት እንደሚያስቀርቡት በመግለፅ፤ ሲዲው በሚቀርብበት ወቅት መቅረቡ አስፈላጊ እንዳልሆነ ተናግረዋል።

No comments:

Post a Comment