Thursday, February 9, 2017

አረና ትግራይና ድብቅ ማንነቱ! – ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው



አረና ትግራይና ድብቅ ማንነቱ!  – ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው
አረና ትግራይ ትላንትና 28,5,2009ዓ.ም. መቀሌ በሚገኘው ቢሮው (መሥሪያ ቤቱ) ባደረገው የፓርቲው (የቡድኑ) 4ኛ ጠቅላላ ጉባኤ ካሳለፋቸው ውሳኔዎች ሁለት ዋና ዋና ነጥቦች ትኩረቴን ሳቡትና ነው ይህችን ጽሑፍ ለመጻፍ የተነሣሁት፡፡
እነኝህ ነጥቦች 1ኛው አረና ትግራይ ከጎሳ ተኮርነት ወጥቶ ወይም ጎሳተኮርነቱን (ዘውገኝነቱን) ትቶ ተመሳሳይ የአንድነት አቋም ካላቸው ጋር በመሆን ሀገር አቀፍ የአንድነት ፓርቲ ለመመሥረት እንደሚንቀሳቀስ የተነገረው ሲሆን 2ኛውና ከላይ ከተናገሩት ነጥብ ጋር በቀጥታ የሚጣረሰው ነጥብ ደግሞ “ፓርቲው ወደፊት ተመርጦ ሥልጣን ቢይዝ የሕወሓት ባለሥልጣናት መጠቀሚያ የሆነውን የትእምትን (EFFORT) ሀብት በትክክል የትግራይ ሕዝብ ሀብት አደርጋለሁ!” ማለቱ ነው፡፡
ከዚህ ቀደም በተለያየ ጊዜ አረና ትግራይንና በትጥቅ ትግል ላይ ያለው ዴምሒትን ወይም ትሕዴንን በምሳሌነት በማንሣት “ተደራጀን!” የሚሉለትን ምክንያትና ዓላማ በመጥቀስ ከትግራይ ማሕፀን ኢትዮጵያን ማሰብ የሚችል ወይም ኢትዮጵያን የሚያስቀድም ፍትሐዊና ዲሞክራሲያዊ (መስፍነ ሕዝባዊ) መሠረት ያለው ፓርቲ (ቡድን) ፈጽሞ ሊወጣ ሊፈጠር እንደማይችል መናገሬ ይታወሳል፡፡ ለዚህ ድምዳሜየ ማስረጃየ እነኝሁ ፓርቲዎች ወያኔን አኩርፈው ከወያኔ እየተለዩ አረናንና ትሕዴንን የመሠረቱበት ምክንያት ነው፡፡ እነሱ በተደጋጋሚ እንደተናገሩት ከወያኔ ተለይተው የተጀራጁበት ምክንያት “ሕወሓት በረሃ እያለ ለትግራይ ሕዝብ የገባውን ቃል ሊፈጽም አልቻለም! የትግራይ ሕዝብ በሕወሓት ተክዷል!” በሚል ቅሬታ በመነሣሣትና ያንን ቃል ተፈጻሚ ለማድረግ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ የፓርቲዎቻቸውን ሥያሜ ትግራይን ማዕከል እንዲያደርግ ያደረጉበትም ምክንያት ይሄው ነው፡፡
እነኝህ ቡድኖች “ሕወሓት ተፈጻሚ አላደረገውም!” ከሚሉት ቃል የተገቡ ጥቅሞች አንዱ “ትግራይን በጎንደር በኩል ሌላው ቢቀር እስከ ደባርቅ ድረስ፣ በወሎ በኩል እስከ አለውኃና ከነባ ድረስ ማስፋት የሚለው አንዱ ሲሆን ሌላው ደግሞ የተለየ የኢኮኖሚ (የጥሪት) ተጠቃሚነት ነው፡፡
ለእነኝህ ፓርቲዎች (ቡድኖች) ወያኔ ከጎንደርና ወሎ ቆርሶ የወሰዳቸው ለምና ሰፋፊ መሬቶችና ከመጀመሪያው ጀምሮ ከኢትዮጵያ ሕዝብ እየተዘረፈ በሕገወጡ ኤፈርትና በሌላም አማካኝነት ትግራይ ላይ የሚፈሰው የግፍ የሀገሪቱ ሀብት እንዲሁም በመላ ሀገሪቱ ትግሬን ብቻ ተጠቃሚ ያደረገው የንግድ እንቅስቃሴና የሥራ ዕድል በጭራሽ በቂ አይደለም፡፡ በቂ ባለመሆኑም ከዚህ በላይ በሚፈልጉት መጠን ተጠቃሚ ለማድረግ በማሰብ እየታገሉ ይገኛሉ፡፡ በሌላ አገላለጽ ሰዎቹ የሚፈልጉት እያንዳንዳችንን በቁማችን ሥጋችንን ግጠው መብላት ነው የሚፈልጉት፡፡ የለየላቸው ጭራቆች ናቸው ሰዎች አይደሉም፡፡ እየታገሉ ያሉት በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ ከወያኔ እጅግ የከፋ ወያኔ ሆኖ ለመምጣት ነው፡፡ የወያኔን ኢሰብአዊ መራር ግፍ ምን ያህል መሸከም እንዳቃተንና በፍጹም እንዳልቻልን፣ በአፍጢማችን እንደደፋን አስቡና ከወያኔ የከፋን ሌላ ወያኔን አስቡ! መቋቋም እንችላለን? ታዲያ እነኝህ ሰዎች ናቸው?
እንግዲህ እንዲህ ዓይነት የነቀዘ የገማ ኢፍትሐዊ አስተሳሰብ ያለው አረና ነው እንግዲህ በትናንትናው ጉባኤው ላይ ከጎሳ ተኮር ወይም ዘውገኛ አስተሳሰብ ወጥቶ ሀገር አቀፍ አስተሳሰብ ካላቸው ወገኖች ጋር በመሆን ሀገር አቀፍ የአንድነት ፓርቲ የመመሥረት ዓላማ እንዳለው ያስታወቀው፡፡
ይህ አባባሉ አዲስ የማወናበጃ መንገድ ለመፍጠር የታሰበ አባባልና አረና መቸም ቢሆን ከጎሰኝነት ደዌው ሊፈወስ የሚችል አለመሆኑን የሚያረጋግጠው “ወደፊት ሥልጣን ብይዝ የኤፈርትን ሀብትና ንብረት በሙሉ የትግራይ ሕዝብ ሀብት እንዲሆን አደርጋለሁ!” ካለበት የምኞት ቃሉ ላይ ታገኙታላቹህ፡፡
አረናዎች ሕገወጡ ኤፈርት ሀብቱን በምን በምን ዓይነት ሕገወጥ መንገድ የኢትዮጵያን ሕዝብና የሀገርን ሀብት ዘርፎ እንዳከማቸና እያከማቸ እንዳለ ከማንኛችንም በላይ ያውቃሉ፡፡ ወያኔ በረሀ በትግል ላይ እያለ ትግራይና ሰሜን ጎንደር የመንግሥት (የሕዝብ) ባንኮችን እየዘረፈ፣ ሥልጣን ከያዘ በኋላም ከብሔራዊ ባንክ በቢሊዮኖች ልብ በሉ በቢሊዮኖች (በብልፎች) ነው ያልኩት የሚቆጠር የሕዝብና የሀገር ገንዘብ በማናለብኝነት ወስዶ ነው የኤፈርትን አቅም የገነባው፡፡ ከዚህም ባሻገር ኤፈርት በሕገወጥ መንገድ ተቋቁሞ ቀረጥና ግብር ሳይከፍል፣ የመንግሥትን ንብረቶች በሕገወጥ መንገድ እየተገለገለና እየተጠቀመ የሚንቀሳቀስ ሕገ ወጥ ድርጅት እንደመሆኑ ከፍተኛ የሀገርና የሕዝብ ዕዳ አለበት፡፡
ዛሬ ላይ ኤፈርት በአቦይ ስብሐት አገላለጽ “በሀገሪቱ ተወዳዳሪ በሌለው ካፒታል (አቅመ ንዋይ)” እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፡፡ ኤፈርት እንደ ፋብሪካዎች (መምረቶች) እና ኢንዱስትሪዎች (ምግንባቦች) ያሉ ቋሚ ንብረቶቹን መቀመጫቸውን ትግራይ ላይ ሲያደርግ ሌሎች ገቢ የሚያገኝባቸውን እንደ ባንክ (ቤተ ንዋይ) ፣ ኢንሹራንስ (ዋስትና) ፣ ትራንስፖርት (መጓጓዣ) ፣ የብዙኃን መገናኛ (ማስ ሚዲያ) ፣ ገቢና ወጪ (ኢንፖርት ኤክስፖርት) ንግድ፣ ግብርናና ማዕድን፣ ኮንስትራክሽን (ግንባታ) ወዘተረፈ እንቅስቃሴውን ደግሞ በመላ ሀገሪቱ አንሰራፍቶ ፍርፋሪውን ብቻ በመተው በሕገወጥ መንገድ በብቸኝነት ተቆጣጥሮ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፡፡
አረናዎች የኤፈርት ሀብት በእንዲህ ዓይነት ዝርፊያ፣ ውንብድናና ሕገወጥ መንገድ ከኢትዮጵያ ሕዝብ ዘርፎ ሀብቱን እንዳካበተ እያወቁ ነው እንግዲህ “የትእምትን ወይም የኤፈርትን ሀብትና ንብረት ሁሉ በትክክልም የትግራይ ሕዝብ ሀብት እንዲሆን እናደርጋለን!” እያሉን ያሉት፡፡ ምክንያቱም መቸም ቢሆን ሊለወጡ፣ ከጎሰኝነት ደዌያቸው ሊፈወሱ አይችሉምና፡፡
አረና “የኤፈርትን ሀብት የኢትዮጵያ ሕዝብ ሀብት እንዲሆን አደርጋለሁ፣ ኤፈርት ፋብሪካዎቹን (መምረቶቹን) እና ኢንዱስትሪዎቹን (ምግንባቦቹን) ኢፍትሐዊ በሆነ መንገድ ትግራይ ላይ አከማችቷቸዋልና ሁሉም የሀገሪቱ ክፍል በእኩልነት ተጠቃሚ ሊሆኑ በሚችሉበት ሁኔታ ተነቅለው በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች መተከል አለባቸው!” ብሎ ቢሆን ኖሮ “ጎሰኝነት እንደማይጠቅምና ሀገርንና ሕዝብንም በእጅጉ እንደሚጎዳ ተገንዝቤያለሁ!” ማለቱን አምነን በመቀበል አረና ትግራይ ከጎሰኝነት ደዌው ተፈውሷል፣ የበሰለ የፖለቲካ (የእምነተ አሥተዳደር) ግንዛቤ ላይ ደርሷል፣ ኢትዮጵያን አስቀድሟል፣ ኢትዮጵያዊነት ተሰምቶታል ባልን ነበር፡፡
ነገር ግን ጠባብ ጎሰኝነት ከትግራይ ማሕፀን ለሚወለዱ ድርጅቶች ካንሰራቸው (ነቀርሳቸው) በመሆኑ ከዚህ ደዌያቸው ሊፈወሱ አይችሉምና “አስተሳሰባችን ወደ ሀገር አቀፍ የአንድነት ደረጃ አድጓል፣ ጎሰኝነትን እንደማይጠቅም አውቀን ትተናል!” እያሉ ባሉበትም ጊዜ “ወደፊት ተመርጨ ሥልጣን ብይዝ የኤፈርትን ሀብት የትግራይ ሕዝብ ሀብት እንዲሆን አደርጋለሁ!” ሊሉ ቻሉ፡፡
ወያኔ ኤፈርትን ሲመሠርት ምክንያት ያደረገው “በ17 ዓመቱ የደርግ ዘመን ትግራይ የጦርነት ቀጠና ሆና በመቆየቷና በመጎዳቷ ትግራይን መልሶ ለማቋቋም ነው!” የሚል ሐሰተኛ ምክንያት በመስጠት ነበር፡፡
የነበረው እውነታ የሚያሳየው ግን ነገሩ ተገላቢጦሽ መሆኑን ነው፡፡ በ17 ዓመቱ የደርግ ዘመን ትግራይም ሆነች ኤርትራ የጦርነት ቀጠና በመሆናቸው ከተቀረው የሀገሪቱ ክፍል በተሻለ ተጠቃሚ የነበሩ መሆናቸውን ነው እንጅ ተጎጂ መሆናቸውን አይደለም፡፡ በሁለት ምክንያቶች፡፡ አንደኛው ደርግ በዘመኑ የሀገርን ከፍተኛ በጀት ለሀገር መከላከያ በጅቶ (መድቦ) ይንቀሳቀስ የነበረ በመሆኑ ያንን ያህል የሀገር ሀብት ይንቀሳቀስ የነበረው ትግራይና ኤርትራ ላይ ነበር፡፡ ደርግ ይሄንን ያህል ግዙፍ ባጀት (የገንዘብ መደብ) በእነኝህ ሁለት ክፍላተ ሀገራት በሠፈረው ሠራዊቱ ላይ ሲያንቀሳቅስ ሁለቱ ክፍላተ ሀገራት በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ተጠቃሚ መሆናቸውን ለመረዳት የሚከብድ አይመስለኝም፡፡ ሌላኛው ምክንያት ደግሞ ደርግ ያባበለ እየመሰለው እህልን እንኳን ሳይቀር ከተቀረው የሀገሪቱ ክፍል እያራቆተ ዕድሜ ልኩን ኤርትራና ትግራይ ላይ ያፈስ የነበረ በመሆኑ ነው፡፡
በተጨማሪም ሀገሪቱ ከነበሯት ፋብሪካዎች (መምረቶች) እና ኢንዱስትሪዎች (ምግንባቦች) የሚበዛው በዚሁ ቀጠና የነበረና ከዚህም አንፃር ከሀገሪቱ ኢኮኖሚያዊ (ጥሪታዊ) እንቅስቃሴ የአንበሳውን ድርሻ የያዘው ይሄው ተጎዳ የተባለው ቀጠና ነበር፡፡
ወያኔ “ትግራይ የጦርነት ቀጠና በመሆኑ ከተቀረው የሀገሪቱ ክፍል በትምህርትና የጤና ሽፋን፣ በመሠረተ ልማት ዝርጋታ ወዘተረፈ. ከሌሎቹ የሀገሪቱ ክፍላተ ሀገራት በዚህን ያህል ደረጃ ወደኋላ ቀርታለች ወይም ተጎድታለች! ብለህ አኃዛዊ መረጃ አቅርብ?” ተብሎ ቢጠየቅ ውጤቱ የሚያሳየው ቅጥፈቱን በመሆኑ ፈጽሞ ሊያደርገው አይችልም፡፡ በመሆኑም ነው እንዲያው በደፈናው ምክንያት በመመክነት ብቻ አሳቦ ዝርፊያ ሲፈጽምብን የኖረውና ያለው፡፡
እርግጥ ነው ጦርነት መገዳደያ መጠፋፊያ እንጅ መሸላለሚያ አይደለምና በዚህ ቀጠና በርካታ ወገናችንን አጥተንበታል፣ ጉዳት ደርሶብናል፡፡ ልብ ሊባል የሚገባው ነገር ግን በዚህ የጦርነት ቀጠና ያለቀው ዜጋ የትግራይና የኤርትራ ተወላጅ ብቻ ሳይሆን ከሁሉም የሀገሪቱ ክፍል በብሔራዊ ውትድርና በግዳጅ ተመልምሎ ይወሰድ የነበረውና ምንም የማያውቀው ለጋ ወይም ገና ታዳጊ ወጣት ወገን ጭምርም ነው ያለቀውና የአካል ጉዳተኛም ሆኖ የቀረው፡፡
እናውራው ከተባለስ እንዲያውም ከሕወሓት መሥራች ታጋዮች አንደበትና ከሌሎች ምንጮችም እንደሰማነው በደርግ ከተገደሉ የትግራይና የኤርትራ ተወላጆች ይልቅ ራሳቸው ወያኔና ሸአብያ የትግራይና የኤርትራ ተወላጆች በእነሱ አስተሳሰብ ብቻ አምኖ የሚንቀሳቀስ ለማድረግ፣ ከእነሱ የተለየ አስተሳሰብ እንዳይይዝ እንዳያንጸባርቅ ለማድረግ የገደሉት እንደሚበዛ መረጋገጡን እዚህ ላይ ማንሣቱ ተገቢ ነው፡፡ በወያኔና ሸአቢያ በትግራይና ኤርትራ ተወላጆች ላይ ለተፈጸመው ጭፍጨፋና ወያኔና ሸአቢያ በአካባቢው ሆን ብለው ያደርሱት ለነበረው የመሠረተ ልማት፣ የትምህርት ቤት፣ የጤና ጣቢያ የመሳሰሉት ውድመቶች የኢትዮጵያ ሕዝብ ዕዳ ከፋይ ወይም ባለዕዳ ሊሆን የሚችልበት አንድም ዓይነት አግባብ የለምና ወያኔ ትግራይን ለመጥቀም የፈጠረው ሰበብ አሳማኝ፣ ትክክልና ፍትሐዊ ሊሆን አይችልም፡፡
ደርግ ስላደረሰው ጥፋት ስናወራ ቀይ ሽብር አንዱና ዋናው ነው፡፡ በዚህ የቀይ ሽብር እርምጃ ከሀገሪቱ አካባቢዎች እጅግ በከፋ መልኩ እንደቅጠል የረገፈውና የተጎዳው የጎንደርና የጉራጌ የሀገሪቱ ክፍል ነው፡፡ ታዲያ እንግዲህ እውነታው ይሄ ከሆነ “ትግራይና ኤርትራ የጦርነት ቀጠና ስለነበሩና ከተቀሩት ክፍላተ ሀገራት በተለየ መልኩ የደርግ አገዛዝ ባደረሰው ጥቃት ተጎድተዋልና የመልሶ ማቋቋም ሥራ ሊሠራላቸው ይገባል!” ተብሎ ተጨባጩ ሀቅ ግን የተቀረው የሀገሪቱ ክፍል ከሁለቱ በከፋ መልኩ በደርግ ጥቃትና ከላይ እንዳነሣነው ሁለቱ ክፍላተ ሀገራት በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ተጠቃሚ የሆኑበትን “ለጦሩ!” በሚል ሁለንተናውን ተበዝብዞ በከፋ መልኩ የተጎዳ መሆኑን እያሳየ እያለ የተሰጠው ምክንያት የቱ ላይ ነው እውነትነቱ፣ ትክክለኛነቱና ፍትሐዊነቱ?
በመሆኑም ሐሰተኛ ወይም የማስመሰያ ምክንያት ተፈጥሮ የለየለት ፋሺስታዊ (አረመኔያዊ) ዝርፊያና ውንብድና ነው ሲፈጸምብን የኖረውና እየተፈጸመብንም ያለው፡፡ አረና ትግራይም ይሄንን ግፍ ማስቀጠል ነው የሚፈልገው፡፡ “ሥልጣን ብንይዝ!” ብለው የተናገሩት ነገር ፓርቲው በአንድነት ፓርቲ ጭምብል ተከልሎም ጠባብ ኢፍትሐዊ የጎሳ ጥቅሙን ለማስጠበቅ እንዳሰበ ማረጋገጫ ነው፡፡
አረና በዚሁ ጉባኤው ላይ ወልቃይትን በተመለከተ ያለውን አቋም ሲገልጽ የወልቃይት ጉዳይ በሕዝበ ውሳኔ እንዲፈታ እንደሚፈልግ አቋሙን አስታውቋል፡፡ ኃላፊዎቹ ግን በግል የሚያንፀባርቁት ከዚህ የተለየ ነው፡፡ ለምሳሌ በዚህ ጉባኤ የፓርቲው ሊቀመንበር ሆኖ የተመረጠው አብርሃ ደስታ የወልቃይት ሕዝብ “ጥያቄያችን የማንነት ጥያቄ ነው!” እያለ ባለበት ሁኔታ ይሄንን የሕዝብ ጥያቄና ጩኸት ኢዲሞክራሲያዊና ኢፍትሐዊ በሆነ አተያይ በማየትና ጥያቄያቸውን ለመቀበል ባለመፈለግ “የወልቃይት ሕዝብ ጉዳይ የአስተዳደር ችግር እንጅ የማንነት አይደለም!” በማለት “ወልቃይት የኛ ነው!” የሚል አንባገነናዊ አቋሙን ግልጽ ያደረገ ግለሰብ ነው፡፡
አሁን ፓርቲው “የወልቃይት ጉዳይ በሕዝበ ውሳኔ እንዲፈታ ይፈልጋል!” ብሎ ሲል ኃላፊዎቹ በግል ከያዙት አቋም የተለየ ወይም የተሻለ አቋም ማንጸባረቁ ሳይሆን የወያኔ ሕገመንግሥት “መኖሪያውን በቦታው ካደረገ 5 ዓመታትና ከዛ በላይ የሆነ ሰው ሁሉ በሕዝበ ውሳኔ የመሳተፍ መብት አለው!” ስለሚልና ወያኔ ከትግራይ እያጋዘ ያሠፈረው ሕዝብ እያፈናቀለ፣ እያሳደደ፣ እየገደለ በእጅጉ ካመናመነው ከነባሩ የወልቃይት ሕዝብ ቁጥር በእጅጉ የሚበዛ መሆኑን ስለሚያውቁ ሕዝበ ውሳኔው እነሱኑ ተጠቃሚ እንደሚያደርግ በመተማመን የያዙት አቋም ነው፡፡ በመሆኑም የፓርቲው አቋም እነ አብርሃ ደስታ በግል ከያዙት አንባገነናዊና ፋሺስታዊ (አረመኔያዊ) አቋም የተለየ አይደለም፡፡
በወልቃይት ጉዳይ ላይ ታች አምና በቅሊንጦ እስር ቤት እያለሁ ከአብርሃ ደስታ ጋር በተነጋገርንበት ጊዜ አንድ ያነሣልኝ ነጥብ ነበረ፡፡ ምን አለ መሰላቹህ “የጎሳ ፌዴራሊዝም (ራስ ገዝ) ወይም ይሄ የአማራ ክልል ነው፣ ይሄ የትግሬ ክልል ነው፣ ይሄ የኦሮሞ ክልል ነው… የሚባለው ነገር የሚቀር ከሆነና ዜጎች በፈለጉት የሀገሪቱ ክፍል የመኖር ሙሉ መብት ካላቸው ወልቃይት የአማራ ነው! የሚለውን ነገር ምን አመጣው?” ብሎኝ ነበር፡፡
እኔም ስመልስለት “የትግሬ ነው የሚለውንስ ምን አመጣው? ነገር ግን እኔ እያልኩ ያለሁት የጎሳ ፌዴራሊዝም (የራስ ገዝ ሥርዓት) እንዳይኖር እንዲጠፋ እንፈልጋለንና የአማራ፣ የኦሮሞ፣ የትግሬ… የሚባል ነገርም አይኖርምና ወልቃይት የአማራ ነው ወደአማራ መመለስ አለበት ሳይሆን እያልኩ ያለሁት ወልቃይት የጎንደር ነውና ወደ ጎንደር መመለስ አለበት! ነው እያልኩ ያለሁለት! በግፍ ተፈናቅለው፣ ተነጥቀው እንዲሰደዱ እንዲጠፉ ተደርገው መሬታቸው፣ ቤት ንብረታቸው ለሠፋሪ ትግሮች የተሰጠባቸው ወገኖች ንብረታቸው ከካሳ ጋር ሊመለስላቸው ይገባል! ይሄንን የፍትሕ ጥያቄ ሳንመልስ መቸም ቢሆን ፍትሐዊና ዲሞክራሲያዊ (መስፍነ ሕዝባዊ) ሥርዓትን መሠረትን ልንል አንችልም!” ብየ ነበር የመለስኩለት፡፡ በወቅቱም አብርሃ ባልኩት ነገር ተስማምቶ ነበር አሁን ላይ ቢያፈርሰውም፡፡
እናም በእነኝህ ምክንያቶች አረና ትግራይ ኢትዮጵያንና ሕዝቧን የሚያስቀድም የማንነትና የብስለት ደረጃ ላይ ሊደርስ የማይችል ድውይ ጠባብ ጎሰኛ ፓርቲ በመሆኑ ሌሎች ወገኖች ተታላቹህ “ከሱ ጋር አብረን ሀገር አቀፍ የአንድነት ፓርቲ እንመሠርታለን!” ብላቹህ እንዳትጃጃሉና መጠቀሚያ እንዳትሆኑ ከወዲሁ አጥብቄ ማሳሰብና ማስጠንቀቅ እወዳለሁ!
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!! ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር!!!
ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው
amsalugkidan@gmail.com

No comments:

Post a Comment