Wednesday, February 15, 2017

አስቸኳያ ተሃድሶ እና ጥለቅ ገደል! | ጋዜጠኛ አናንያ ሶሪ ከእስር ቤት የላከው አዲስ ጽሑፍ




 የመጀመሪያ ክፍል ፩
“አለባብሰው ቢያርሱ በአረም ይመለሱ!” ይላል ሀበሻ ሲተርት፤ “የእነ ቶሎ ቶሎ ቤት ግድግዳው ሰንቤሌጥ”ም  ይባላል፡፡ ስለ ጥድፊያ ያላማረ መጨረን ለመግለጥ “የሀገራችን ኣሳዛኝ ወቅታዊ ሁኔታም ይህን አባባል በተግባር እያስተዋልን እንደሆነ ያስገነዝባል- ልብ ብሎ ላስተዋለ!
በእስር ላይ የሚገኘው ጋዜጠኛ አናንያ ሶሪ
እጅግ ብዙ ነገሮች ባለፉት 4 ወራት እየተግተ፤ተ፤ ተፈፅመዋል፤ ከእነዚህም ውስጥ፡-
  1. የእሬቻ በዓል የጅምላ ሞት
  2. የኢህአዴግ “ጥልቅ ተሃድሶ” ነጋሪት
  3. የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ልፈፋ
  4. የዜጎች የጅምላ እስራት
  5. የ“ሙሰኛ የሥራ ኃላፊዎች” የሥራ ስንብትና ክስ
  6. የህዝቦች የመኖር ስጋት እና የወጣት ስደት
  7. የሀገሪቱ አለመረጋጋትና ፖለቲካዊ ውጥረት……. ተጠቃሽ ናቸው
እነዚህ እጅግ በጣም በአጭር ጊዜ ውስጥ እንዲፋጠን ናዳ የወረዱ ክስተቶች፤ ሀገራችን ወዴት አቅጣጫ እየሄደች እንደሆነ ቆም ብለን እንድንመረምር ያስገድዱናል፡፡ ቀድሞውኑ እዚህ እንዴት ደረስን? ከእዚህስ እንዴት እንወጣለን?
ያለፉትን 25 ረጅም ዓመታት በጥልቅ ለመገምገም አልሞክርም፣ ነገር ግን አንኳር የሆኑትን ቁም- ነገሮች ልጠቃቅስና ላሁኑ ሁኔታ ያላቸውን ፋይዳ ና አስተዋፅዖ ላመላክት፡-
ከህገ-መንግሥቱ መርቀቅ ጀምሮ እጅግ በርካታ ቃልኪዳን የተገባላቸው ወሳኝ ፍሬ ነገሮች ነበሩ፤ ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት ወይንም ያለአንዳች ገደብ ሃሳብን በተለያዩ የግልሚዲያዎች አማካኝነት ማስተላለፍ እንዲሁም የመድብለ-ፓርቲ ሥርዓት ወይንም ነፃ የምርጫ ፉክክር ባለበት የሥልጣን ሽግግር ማካሄድ! ከእነዚህ ሁለት ቁም ነገሮች ጋር ደግሞ ተነጣጥሎ ሊታዩ የማይችለውና የማይገባው የሰብዓዊ መብቶች ዕውቅና ማግኘት ጉዳይ ነው፡፡ በእዚህም መሠረት- ከደርግ መገርሰስ በኃላ የ“ኢፌድሪ” (የኢትዮጵያ ፌዴራሊያዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ) ተመስርቶ፤ መንግሥታዊ መዋቅር ተዘረጋ፡፡
በኢትዮጵያ ልዩ ታሪካዊ ሁኔታም የተነሳ የ“መሬት” እና “ብሔር” ጉዳዮች በልዩ መንገድ ታይተው ልዩ ስፍራ ያዙ-ሉዓላዊ የሥልጣን ባለቤቶችም “ብሔርና ብሔረሰቦችን እንዲሁም ህዝቦች” ናቸው፡፡ ተባለ! መሬትም “የህዝብና የመንግሥት” ንብረት እንዲሆን ተወሰነ፡፡ “የነፃ- ገበያ ኢኮኖሚ”  ምስረታም ከ“ዴሞክራሲያዊ ስርዓት” ግንባታ ቢሮ ጋር እጅና ጓንት ሆኖ እንደሚቀላጠፍ በሰፊው ታተተ፡፡
ብዙ ማራኪ ተስፋዎች ተዘሩ፤ እጅግ የበዙ እምነቶች ታመኑ፤ የታጨደው ግን ጉም ሆነ፡፡ ፍየል ወዲያ ቅዝምዝም ወዲህ ሆነና ዴሞክራሲያዊ ፣ ገበያው መንግስታዊ (ፓርታዊ፣ ሚዲያዊ፣ ወገናዊ፣ ሰብአዊ መብቱ ወረቀታዊ መድብለ ፓርቲ (አዊራዊ፣ ፈድራሊዝሙ ኢስሙላዊ ፖለቲከኛነትና ጋዜጠኝነት የአፍ ልማታዊ የተግባር ልማዳዊ ሆነው ሆነው፤ ደርግ በሄደብት ኢህአዴግ ተመላለሰብት!
የኢትዮጵያ የጉልቻ መለዋወጥን እንጂ የወጥ ማጣፈጥን ሳያይ “አዲሱን ንጉሡን” ተሸክሞ፤ ትናንት የባህር መደብ ያስረካባትን ሀገር ሊወጋ የተነሣው ፈርኦኑ አሽከርነት ገብቶ ለባድማ መሬት በመቶ ሺዎች ረገፈ ባልገባው ገብቶ ተማገደ፤ በተማገደበት ግን አንዳችም አላተረፈም! የቅርፅ እንጂ የይዘት ለውጥ ስላልመጣም “መንግሥት” የበጎ-ለውጥ ኃይል ከመሆን ይልቅ፤ የመሻሻል ተስፋ ደንቃራ ሆኖ ተገደገደ፡፡ የተገቡ ቃልኪዳኖችም በሙሉ ፈረሱ፤ በህገ-መንግሥት ዕውቅና የተቸራቸው አብይ ጉዳዮችም ተቀለበሱ-1997 ምርጫ እና የተከተለው መዘዝም ተስፋዎቹ በርም መከርቸምም በግልጽ አመላከተ፡፡
በተከረቸሙ በሮች ላይ የተለያዩ አፋኝ አዋጆች ችንካር ሆነው ተመቱ- የመ.ያ.ዶዎች አዋጅ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች አዋጅ፣ የሚዲያ አዋጅ የፀረ-ሽብር አዋጅ፣…. የአፈና ስልቶች ጋጋታ!
ከእነዚህ ጎን ለጎን ደግሞ፡- እጅግ ብዙ ወጣቶችን፣ ሴቶችን ፣ አለፍም ሲል ባልቶቶችን ወደ ‹‹ አውራ-ፓርቲ›› ኮርስ ለመክተት ሌት ተቀን ተደከመ፡፡ እነ ሬድዋን ሁሴን ይህንን ታሪካዊ ግዳጃቸውን ፈፅመው ያሰራቸውን ደሞዝ ከሰበሰቡ በኋላ ይኸው ዛሬ የግዳጅ ጡረታ ወጥተዋል፡፡
እነሆ በ2009 ዓ.ም ደግሞ ኢህአዴግ፡- (ማነህ ባለ ሳምንት? ማነህ ባለተራ?) እያለ በደጃፍህ ቆሞ ሊያንኳኳ ጉዞውን ጀምሯል- ባለ ሦስት ፈርጅ የአፈና ስልቱን በአንተ ትኩስ ደም ታድሶ ቆዳውን እየቀያየረ እባብ ለመሆን ሸኮናህን ፍለጋ በማለዳ ወጥቷል! (ሥልጣን) ቋሚና የማይቀያር ፅኑ-ዓላማው የሆነው የህወሓት /ኢህአዴግ ፤ የብዙ ተቀያያሪና ተፈራራቂ ሰዎችን ዕውቀት እንደሸንኮራ እየመጠጠ በመጠቀም ብዙ ርቀት ለመድረስ ያልማል! ይህም ፡- ስር-ሰደድ ‹‹የስልጣን ጥም›› (deep-hooted lust for power) ኣባዜው እዚህና ለዚህ ያደረሰን!
የገባቸው ዕጹብ ቃል ኪዳኖች ሁሉ ቀርጥፎ የበላው (የሥልጣን ስስታም) እና (የቁስ- ሰቀቀናም) ስለሆነ ነው፡፡  ስለ ሥልጣን ሲልም አገርን አርገው ሊያቆሙ የሚችሉ ምሰሶና ማገሮችን በህገ መንግሥቱ ለይስሙላ ተቀብለው፤ በተግባር ግን ውስጥ ውስጡን ሲቦረቡራቸውና ሲደረማምሳቸው ይታያል!

ይቀጥላል…..
ጋዜጠኛ አናንያ ሶሪ

No comments:

Post a Comment