Monday, April 18, 2016

ከዚህ በላይ ቁስል ከዚህ በላይ እንባ ( ሄኖክ የሺጥላ )


በላ
ደረትህን ድቃ
ዐይንህ ዶቃ እምባ ዛጎል ልቅሶ ያንባ
ዱብ ይበል ስቃይህ የጨው ውሃ ለብሶ
የፊትህን ሰማይ ፥ ገፅታህን ገምሶ!
በላ እናልቅሳ ፥ እሪ ኡኡ እንበል
ደም ሲፈስ እያየን ፥ ሲፈልቅ እንደ ጠበል !
ባንድ ጥያት እናት ፥ ባንድ ጥይት ኣራስ
ባንድ ጥይት ሲሞት ፥ ሲጣመር ሁለት ነብስ
ባገራችን ባህል
በደም ባጥንታችን
ኡኡ እንበል በቃ
ሲፈርስ ቤታችን !
እንደ ኣንበጣ ሲሞት ፥ ጎርፍ እንደጣለው ትል
ከእንባ ጅረት ሌላ ፥ በምን ቃል ምን ልትል ?
ከናቱ ትከሻ ፥ ጀርባ ላይ ተጣብቆ
በጥይት ሲነጠቅ ፥ በእንቅልፍ ኣለም ወድቆ
ምን ቃል ኣለህና
በምን ልትናገር
ዝም ብለህ ኡኡ በል ፥
ኡኡ በል ኣንት ሃገር !
እንባህን እርጭ እና ፥ ወደ ጥልቁ ሰማይ
ምልክት ተቀበል ፥ ከሁሉም የበላይ!
ኡኡ በል እሪ በል
ስፈር ሃዘንህን
እንደ እዮብ ጠጉር ንጭ
በል ጉዳው ገላህን !
«ንገረኝ እንግዲህ ኣንተም ተናገረኝ
ምድርን ስመሰርት ነበርክ መስለኝ»
ብሎ እስኪቆጣህ ኣምላክ እስኪቀየም
እሪ በል ኡኡ በል ፥ መኖሩ ኣልታየም !
መፈጠርህን እርገም ሰው መሆንህን ጥላ
ለምን ብለህ ጠይቅ ፥ እውነት እንዳትፈራ!
ለምን እኔን በለው ፥ ለምን ካለም ሁሉ
ለምን ሆነ በለው ፥ ለምን ሆነ ቃሉ !
ባምሳሉ ፥ በገፁ የፈጠረው ሲሞት
ለምን ብለህ በለው ፥ ለምን በለው በእውነት !
ኣትፍራ ጠይቀው ፥ ለምን ሙሴ እንዳጣን
ምን ሲል በምን ምክንያት እንዲህ የሚቀጣን !
ኡኡ በል እሪ በል ኣምላክም ይታወክ
ባያድነን እንኳ መኖሩን እንወቅ!
ኣታልቅሱ ብሎ ፥ ሊቆጣን ሲመጣ
እንጠይቀዋለን ፥ መቼ እንደሚፈርድ ፥
ፀሃይ እንደሚወጣ !
ድረስ ብለን ያልነው
ለዘመን ኣርፍዶ
እራሴን ስጠላ ከተቆጣ ወርዶ
እኔ ምን ቸገረኝ ፥ እሱ ያናግረኝ እንጂ
እራሴን መጥላቴ ኣይከፋም ከመሞት ፥ ከመጥፋት በፈንጂ !
ስለዚህ እሪ በል
ኣምላክ የለም ወይ በል
ድንገት ኣለሁ ካለ ፥ ካፈለቀ ጠበል
ሙሴን ከፈጠረ ከከፈለ ባህር
ድንገት ተበሳጭቶ
ድንገት ተቆጥቶ
መኖሩን ካሳየ ፥ ባሳቤ ተከፍቶ
የለም ብለህ ኣስቆጣው
የለም ብለህ ጥራው
በነገሩን ባነበበነው በክታቡ እንዳየነው
ኣምላክም ቢሆኑ ራሱ ፍፁም ቀናተኛ ነው ።
ድረስ ብለን ካልሰማን ፥ ካልደረሰ እንደ ዛሬ
የለህም ንብለህ ጥራው ፥ እሪ ብለህ በቀብሬ 

No comments:

Post a Comment