Friday, April 22, 2016

የወያኔ አቅጣጫ የማስቀየር ፖለቲካ በዳላስ (የዳላስ ፎርትወርዝ ኢትዮጵያውያን ፎረም)



ከዳላስ የፖለቲካ እና ውይይት አዘጋጅ ስብስብ:
d24af016-c583-4552-bd62-6ade75040889መከራ ከማይደርቅባት አገራችን ኢትዮጵያ የሚጎርፈው ዘግናኝ ለአይን እና ለጆሮ የሚሰቀጥት ዜናን ያላየ ወይንም ያላዳመጠ የአለም ህብረተሰብ አለ ለማለት ያስቸግራል። ለአለፉት ስድስት እና ከዚያ በላይ ለሆኑ ወራት በኦሮሞ ወገኖቻችን የተጀመረው የሰላማዊ አመጽ እንደቀጠለ ነው። ለዚህ ሰላማዊ ጥያቄ በወያኔ እየተመለሰ ያለውም ግድያና ጭፍጨፋ መሆኑን አይተናል እያየንም ነው። በሰሜን ኢትዮጵያ በወልቃይት፣ በጸገዴ፣ በጸለምት እና በሰሜናዊ የወሎ ክፍለ ሀገር የትግራይ አዋሳኝ በነበሩ ቀበሌወች ያለፈቃድ ወደትግራይ ከተከለሉ በኋላ የነበረው የህዝብ ማጉረምረም ወደ አደባባይ ወጥቶ የማንነት ጥያቄ የተጀመረበት ጊዜ ነው። ወያኔ እራሷ በፈጠረችው የዘር እና የማንነት ፖለቲካ ስትያዝ ወደአመጽ በመውሰድ ሕዝብን ማሰር መግደል እና ዳብዛ ማጥፋቱን ቀጥላበታለች።፡የወልቃይት እና የጸገዴ ሕዝብ ለአለፉት 25 እና ከዚያም በላይ ለሆኑ አመታት ሕዝብን በጥይት ጨርሶ መሬቱን ወደ ትግራይ ለመቀላቀል በጠባቧ ጎጠኛ ቡድን የተዘየደው እና በግድ የተከለለው ሕዝብ የማንነት ጥያቄ ከመቸውም በላይ ገዝፎ የወጣበት እና ከዚህችው ጠባብ ብሄርተኛ ድርጅት ጋር ግብግቡ የፋመበት፣ ጥያቄውን ያነሳው ሕዝብ ሰላሙን አጥቶ የሚሰቃይበት ወቅት ላይ ነው።
ከሁሉም በላይ የአለምን ሕዝብ አይንና ጀሮ የሳበው አሳዛኝ ርሐብ ወያኔ ልትደብቀው በማትሽልበት ግዝፈት አይኑን አፍጦ የወጣበት እና 14 ሚሊዮን ህዝባችን ዳግም ለምጽዋት ሰጭ ደላሎች የተዳረገበት፣ በአንጻሩም ቁጥረ ብዙ ወገን ዙሪያ ገባው ጨልሞበት መድረሻ አጦ በማለቅ ላይ ያለበት ጊዜ ነው። ይህ ሁሉ ግፍ ሳያንስ በሰሞኑ በጋንቤላ ወገኖቻችን የደረሰው ፍጅት መልስ ከማንም በላይ ይፈልጋል። ለመሆኑ ጭፍጨፋው በውጭ ሰርጎ ገብ ተፈጸመ ማለቱስ የቱን ያክል እውነትነት ሊኖረው ይችላል? ቢሆንም እንኳን የዜጎችን ደም ለማፍሰስ ከጥይት የቀደመ ፍጠት ያለው የአጋዚ ጦር እና መንግስት ነኝ ባዩ ወያኔ መራሹ ምን እየሰራ ነበር? ቢያንስ አንድ Liaison Officer ጁባ ያስቀመጠ መንግስት፣ የአየርና የምድር ጦር በቅርብ በራሪ ድንበር ጠባቂ ሄሊኮፍተሮች ጋር የታጠቀ እንዴት ለቀናት የተጓዙ የውጭ ሰርጎ ገቦች ዜጎችን ሲጨፈጭፉ ምን ያክል ስውርነት ቢኖራቸው ነው ወዘተ። የሚሉት ጥያቄወች ሁነኛ መልስ ቢሹም መልስ ሰጭ እንደማይኖር ግን የኢትዮጵያ ሕዝብ ጠንቅቆ የተረዳው ጉዳይ ሆኗል።
ከላይ የተዘረዘሩትን ግዙፍ ብሄራው ቀውሶች ምንም እንኳን መደበቅ የሚቻል ባይሆንም ወያኔው የፖለቲካ ጨዋታውን ወደ ውጭው ዜጋ በማዞር በሰሞኑ በብዙ የአውሮፓ እና የሰሜን አሜሪካ ከተሞች በመንቀሳቀስ ላይ መሆኑን ዜናው ለዳላሶችም ደረሰን። ከዚህ በፊት ወደዚሁ በመምጣት አፍሮ የተመለሰው ደመቀ መኮነን የተባለ የወያኔው ምክትል ምናምን በኤፕሪል 24/2016 እነድሚመጣም የወያኔው ደጅ ጸኝወችና ተጠቃሚወች በማሰራጨት ላይ ባሉት ወረቀት ለማወቅ ችለናል። ይህ ግለሰብ የአገራችንን ምእራባዊ ክፍል ለሱዳን ፈርሞ እንደሰጠም የተነገረለት ጉደኛ ተላላኪ ነው። በዚህ አያበቃም። እርሱ ከቤተሰቡ ጋር ከወሎ ክፍለ ሀገር ወደ መተከል ጎጃም ተዛውሮ ያደገበትን ቀበሌ እያወቀ ዜጎች ወደክልላችሁ ተብለው ፍዳ ሲቀበሉ፣ በአገራቸው ስደተኞች ሆነው ሲንጓለሉ በስራቱ ባለው ውክልና እና ስልጣን እንኳን የት ወደቃችሁ ያላለ ግለሰብ እንደሆነ አገር ያወቀው ጸሀይ የሞቀው ታሪኩ ነው። እናም ወደ ዳላስ የሚመጣበትም የፖለቲካ ጨዋታ የአማራ ልማት በሚል ፌዝ የተጃጃለ ከተገኘም ጨው ለማላስ አለያም ያው የአገሪቱን የገዘፉ እና አደባባይ የወጡ ችግሮችን አስቀይሮ አጀንዳ ለመስጠት እንደሆነ አይዘነጋም።
ማሳሰቢያ በዳላስ እና ፎርትወርዝ ለምትኖሩ ኢትዮጵያውያን በሙሉ
ይህን የወያኔ አቅጣጫ አስቀያሪ አጀንዳ ባለማወቅ ወደዚህ ስብሰባ ለመሄድ የተጠራችሁ (የተጋበዛችሁ) የአገራችንን ሁኔታ እና በህዝባችን ላይ እየደረሰ ያለውን በደል በጥሞና እንድትመረምሩ እናሳስባለን። የዳላስ ኢትዮጵያውያን በኢትዮጵያ ኮሚውኒቲ ማህበር በተጠራ ለወገን ደራሽ ድጋፍ World Vision ለተባለ አለማቀፍ የእርዳታ አሰባሳቢ እና አድራሽ ድርጅት $62,000.00 አሰባስበው ባለፈው እሁድ ገንዘቡን ለተጠቀሰው ድርጅት በኮሚውኒቲው ሊቀመንበር እንዳስረከቡ አይተናል። ይህ በጎ ለወገን ደራሽ ተግባር በተሰራበት ከተማ እና ሳምንት ለወገኖቻችን እልቂት ምክንያት የሆነው የስርአቱ ተላላኪ በጠራው ስብሰባ መገኘት ህሊና ላለው እና አዙሮ ለሚያይ የሚመጥን ተግባር እንዳይደለ ሁሉም እንዲረዳልን እናሳስባለን።
በዳላስ እና ፎርት ወርዝ ለምትኖሩ አክቲቪስቶች እና አገር ወዳድ ወገኖች ሁሉ በምንኖርበት ከተማ የታቀደው የወያኔ ስብሰባ አንድም ዘረኝነትን ያስቀደመ መደለያ ሲሆን። ሌላም ወገን ከወገኑ የሚለያይ ብሎም በውስጥ በወገኖቻችን ላይ እየደረሰ ያለውን በደል ለመሸፈን የታቀደ የወያኔ መላ ወይንም ፌዝ ስለሆነ ሁሉም እንዲያወግዘው ቅስቀሳ እንድታደርጉ በትህትና እናሳስባለን። በቦታውም ተገኝቶ የወያኔውን ተልእኮ አሳፍሮ መመለስ ይጠበቅብናል።
ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር !!!
የዳላስ ፎርትወርዝ ኢትዮጵያውያን ፎረም

No comments:

Post a Comment