Thursday, April 28, 2016

በጋምቤላ ውጥረቱ እየተባባሰ መሆኑ ተገለጸ (የፍኖተ ዴሞክራሲ ራድዮ አጫጭር ዜናዎች)




ሚያዚያ 18 ቀን 2008 ዓ.ም.ዜና (April 26, 2016 NEWS)
# በጋምቤላ ውጥረቱ እየተባባሰ መሆኑ ተገለጸ
# ለጥጥ ልማት በማለት ብድር ወስደውና ደን መንጥረው የነበሩ ግለሰቦች ጠፉ ተባለ
# የትንሣዔ በዓልን አስታኮ ወያኔ የሸማቾች ማህበራት ሱቆች እያቋቋመ ነው
# የጄኔራሉን ገዳዮች ባስቸኳይ እንዲይዙ የብሩንዲው ፕሬዚዳንት ለጦር ኃይሉ መመሪያ ሰጡ
# አልሸባብ በባይደዋ የአፍሪካ ህብረት ሰላም አስከባሪ ጦር ሰፈርን ወርሮ ጉዳት አደረሰ
# የእርዳታ ሰጭ ድርጅቶች በሱማሊያ የገባውን ድርቅና ረሃብ ለመቋቋም የምግብ እርዳታ ያስፈልጋል አሉ
#ሬክ ማቻር ጁባ ገቡ
ሚያዚያ 18 ቀን 2008 ዓ.ም.
Ø ጋምቤላ 18 ኪሎሜትር ርቀት ላይ ባለው የደቡብ ሱዳን የጀዊ ስደተኞች ሰፈር የፈነዳው ግጭትና ግድያ ትላንትም ቀጥሎ እንደነበር በቦታው ያሉ ምስክሮች ገልጸዋል ። በቦታው የሰፈሩት ስደተኞች መቶ በመቶ የደቡብ ሱዳን አማጽያን መሪ የሪያክ ማሻር ተከታዮችና የኑዌር ተወላጆች ሲሆኑ የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ኮሚሽን ሾፌር የነበረው ኢትዮጵያው ሁለት ስደተኛ ህጻናትን በመኪና ገጭቶና ገድሎ በመሰወሩ ኑዌሮቹ በሰፈሩ ያሉትን ኢትዮጵያውያን ለመግደል ተነስተው ብዙዎችን እንደገደሉ ይታወቃል ። ከተገደሉት ውስጥ የስደተኛው ኮሚሽን ኢትዮጵያዊ ሰራተኞችም እንዳሉበት ታውቋል። ጀዊ የአንዋኮች አካባቢ ስትሆን ወያኔ ኑዌሮችን በዚያ ያሰፈረው ለተንኮል ነው ተብሎም ተጋልጧል። ወያኔ ከግድያው በኋላ ዜጎችን ለመከላከል ምንም እርምጃ ባለመውሰዱ ኢትዮጵያውያኑ ተደራጅተው የስደተኛውን ሰፈር ማጥቃታቸው ታውቋል። የሟቹ ቁጥርም ቀላል አልሆነም ። የተባበሩት መንግስታት የስድተኛ ኮሚሽን ሰራተኞቹን ከጀዊ አካባቢ አሽሽቷል። ግጭቱ ገና አልበረደም ሲል ዛሬም የደረስ ዜና ያረጋግጣል ።
Gambela
Ø ወያኔ ለዘረፋና ለስርቆት እንዲያመቸው ከ 100 ሺ ሄክታር በላይ የጋምቤላ መሬትን ለጥጥ እርሻ በማለት ለንግድ ሸሪኮቹ በመስጠትና ለልማትም በማለት 3 ቢሊዮን ብድር በመፍቀድ የጥጥ ምርትን እናሳድጋለን በማለት ፕሮፓጋንዳውን ካሰራጨ ወዲህ የጥጥ ምርቱም ሳይኖር ልማቱም ሳይካሄድ ደን ተጨፍጭፎ ከቆየ በኋላ በብድር የተሰጠው ገንዘብ ለምን ተግባር እንደዋለ እንኳ ለማወቅ አለምቻሉ ተገልጿል። ለጥጥ ልማት በማለት መሬት ወስደው ደን መንጥረው ገንዘብ ተበድረው ጠፉ የተባሉ ሰዎችና ኢንቬስተሮች እነማን እንደሆኑ ባይገለጽም ወያኔ ምርመራና ማጣራት ጀምሬያለሁ ብሏል። ጉዳዩን የተከታተሉ ወገኖች ግን ዘረፋውና የተፈጥሮ ወድመቱ በወያኔ አባላትና በንግድ ሸሪኮቻቸው መፈጸሙን ይናገራሉ።
Ø በአባይ ወንዝ ግድብና አጠቃቀም ዙሪያ ወያኔና ግብጽ የገቡበትን የፖሊቲካና የዲፕሎማሲ ውዝግብ ለማብረድ በወያኔ ፓርላማ አፈጉባዔ የሚመራ አንድ የልኡካን ቡድን ግብጽንና ሱዳንን መጎብኘቱ ይታወሳል። የጉብኝቱ ዓላማ የታሰበለትን ግብ ይምታ አይምታ ባይታወቅም በወቅቱ የነበረውን የዲፕሎማሲ ውጥረት ግን ሳያለዝበው እንዳልቀረ ተገምቷል፡፤ ወያኔ ከሱዳን ጋር መልካም ወዳጀነት ፈጥሮ በድንበር አካባቢ ለም መሬቶችን አሳልፎ ከሰጠና ሱዳንም በአገሩ የሚገኙ የወያኔ ተቃዋሚዎችን እያፈነ ለወያኔ ለመስጠት ጥረት በሚያደርግበትና በሁለቱ አገሮች መካከል የድንበር ጥበቃ ውል ተፈርሞ ባለበት በአሁኑ ሰዓት የሱዳን ሕዝብ ዲፕሎማሲ የተባለ ቡድን የወያኔን ባለስልጣኖችን እንደሚያነጋግር ተገልጿል። ጉብኝቱ ግንቦት 1 ቀን 2008 ዓም የሚጀመር ሲሆን የዲፕሎማሲው ቡድን ከወያኔው ጠቅላይ ሚኒስትር ተብየው ጀምሮ ከሌሎች የወያኔ ባለስልጣኖችን ያናገጋራል ተብሏል፡፤
Ø መጭውን የትንሳዔ በዓል አስታኮ የወያኔ አገዛዝ ሱቆችን በማደራጀት አባ ወራዎችን በቡድን እየመደበ እንደሚያሰማራ ታውቋል። ከአስራ አምስት እስከ ሃያ የሚደርሱ አባወራዎች በአንድና በሁለት ሱቆች ሸቀጦች እንዲሸጡ በማደራጀትና በማስገደድ ነዋሪዎንና የነጋዴው ህብረተሰብን ለማጋጨት እየተሞከረ መሆኑ ተገልጿል። ሱቆቹ በዋናነት ስኳርና ዘይት የሚያቀርቡ ሲሆን ሌሎች ሸቀጦችንም ሊጨምሩ እንደሚችሉ ተነግሯል። የወያኔ አገዛዝ በመላ ኢትዮጵያ ላንሳራፋው የኑሮ ውድነት ተጠያቂ መሆኑ የሚታወቅ ቢሆንም የችግሩ መነሻና ምንጭ የነጋዴው ህብረተሰብ እንደሆነ አድርጎ በማቅረብ ነጋዴዎችን ከሕዝብ ጋር ለማጋጨት የሸማቾች ማህበራትን ማቋቋሙ ይታወቃል። የፋሲካ በዓልን ተንተርሶ እንደ ቅቤ እንቁላል ዶሮ በግና በሬዎች የመሳሰሉ የምግብ አቅርቦቶች ዋጋ ጭማሪ እያሳየ መሆኑ ታውቋል።
Ø ኢትዮጵያውያን ስደተኞችን ለወያኔ ማስረከብ የለመደበት የኬንያ መንግስት የታይዋን ተወላጅ ሆነው በህገወጥነት የወነጀላቸውን የታይዋን ተወላጆች አስሮ ለሀገራቸው ሳይሆን ለቻይና ማስረከቡ ተጋለጠ። ቻይና ታይዋን ግዛቴ ናት ብትልም ቻይናና ታይዋን ሁለት የተለያዩ ሀገሮች ሆነው እንድሉ ይታወቃል። ወያኔ በበኩል ኬንያ እንደ የመን የሚመጡ ተቃዋሚዎችን አግታ እንድታስረክብ ዝርዝር ስሞችን ሰጧል ተብሎም መረጃ አለ ።
Ø ከጥቂት ቀናት በፊት በብሩንዲ አንድ የጄኔራል ማእርግ ያላቸው ከፍተኛ ባለስልጣን ከነባለቤታቸው ባልታወቁ ሰዎች መገደላቸው የሚታወስ ሲሆን ገዳዮችን አፈላልገው እንድይዙ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ለወታደሮቻቸው የአንድ ሳምንት የጊዜ ገደብ ያለበት ጥብቅ መመሪያ የሰጡ መሆናቸው ታውቋል። ፕሬዚዳንቱ ለሟቾቹ ቤተሰቦች ሀዘናቸውን የገለጹ ሲሆን የአገሪቱ የጦር ኃይልም አንድነቱን አጠናክሮ ሁኔታውን በቁጥጥር ስር እንዲያደርግ ተማጽነዋል። የፕሬዚዳንቱ ትእዛዝ በብሩንዲ እየተካሄደ ያለውን ግድያ ያፋፍማል የሚል ስጋት ፈጥሯል። የብሩንዲ የእርስ በርስ ግጭት ከጀመረ ወዲህ የመንግስት ባለስልጣኖች ማንነታቸው ባልታወቀ ሰዎች ሲገደሉ የመንግስት የጸጥታ ኃይሎች ደግሞ በሰላማዊ ሰዎች ላይ የጅምላ ግድያ እያካሄዱ ከመሆናቸውም በላይ በርካታ ሰዎችን አስረው ሰቆቃዊ ድርጊት እየፈጸሙባቸው መሆኑ ይነገራል።
Ø በሱማሊያ ከዋናዋ ከተማ ከሞጋዲሾ ሰሜን ምዕራብ 250 ኪሎሜትር ርቀት ላይ ከምትገኘው ከባይደዋ ከተማ አጠገብ በሚገኘው የአፍሪካ ህብረት እና የሱማሊያ መንግስት የጦር ካምፕ ላይ አልሸባብ ጥቃት ሰንስዝሮ ቢያንስ 20 ወታደሮችን የገደለ መሆኑ ከስፍራው የተገኘው ዜና ይገልጻል። ከተወሰነ የተኩስ ልውውጥ በኋላም የአፍሪካ ህብረት የሰላም አሰከባሪ ሃይሎች እና የሱማሊያ ወታደሮች የጦር ሰፍሩን መልሰው መቆጣጠራቸው ተነግሯል። የአልሸባብ አጥቂዎችም ከባድ ጉዳት እንደደረሰባቸው የአፍሪካ ህብረት የሰላም አስከባሪ ኃይል ቢገልጽም ከአልሸባብ በኩል የተሰማ ዜና የለም።
Ø መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችና የሰብአዊ እርዳታ ሰጭ ድርጅቶች በጋራ ባወጡት መግለጫ በሱማሊያ የገባውን ከፍተኛ ድርቅና ረሃብ ለመቋቋም አስቸኳይ እርዳታ እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል። ድርጅቶቹ በጋራ መግለጫቸው ላለፉት አራት አመታት በሱማሊያ ዝናም በመጥፋቱ ምክንያት ከ5 ሚሊዮን በላይ የሚሆን ሕዝብ መሰደዱን ገልጸው ሁኔታው በዚህ ከቀጠለ ከፍተኛ እልቂት ሊኖር እንደሚችል ተናግረዋል። ከስድስት ዓመት በፊት በሱማሊያ በገባው ድርቅ ምክንያት ከ250 ሺ ሰው በላይ የሞተ መሆኑን አስታውሰው ተመሳሳይ የሕዝብ እልቂት እንዳይደርስ ከፍተኛ እርዳታ መሰብሰብ አለበት ብለዋል።
Ø ከጥቂት ቀናት በፊት ከአንድ የቱርክ የንግድ መርከብ ላይ በባህር ላይ አፋኞች ተጠልፈው ተወስደው የነበሩ ስድስት የመርከቡ ሰራተኞች የተለቀቁ መሆናቸውን የንግድ መርከቡ ባለስልጣኖች ገልጸዋል። ሚያዚያ 3 ቀን 2008 ዓም. ማንነታቸው ያለታወቀ የባህር ላይ አፋኞች መርከቧ ላይ በመውጣቱ ካፕቴኑ የሚገኝበትን ስድስት ሰዎች በቁጥጥር ስር ማድረጋቸው የታወቀ ሲሆን ማክሰኞ ሚያዚያ 18 ቀን 2008 ለቀዋቸዋል ተብሏል። የተለቀቁት የመርከቧ ሰራተኞች በጥሩ የጤና ሁኔታ ላይ መሆናቸው ቢነገርም ለመለቀቃቸው ካሳ መከፈሉ እና አለመከፈሉ የተገለጸ ነገር የለም። በዚህ ዓመት ብቻ በናይጄሪያ ወደብ አካባቢ ከ32 በላይ የመርከብ ጠለፋዎች የተካሄዱ መሆናቸው ከተባበሩት መንግስታ ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት አካባቢ የተገኙ ዜናዎች ይጠቁማሉ።
Ø የደቡብ ሱዳን አማጽያን መሪ ሪክ ማቻር ለአንድ ሳምንት ያህል ጉዟቸው ካዘገዩ በኋላ በዛሬው ቀን ጁባ ገብተዋል። የአማጽያኑ ድርጅት ቀደም ብሎ ባወጣው መግለጫ ሚስተር ማቻር ዛሬ ሚያዚያ 18 ቀን ከቀኑ ስምንት ሰዓት ላይ ጁባ የሚገቡ መሆናቸውን ገልጾ የነበረ ሲሆን በታቀደው መሰረት ለምክትል ፕሬዚዳንቱ ቦታ ለመያዝ ቃለ መሃላ ፈጽመዋል ተብሏል። ሚስተር ማቻር ጁባ ይገባሉ ተብሎ ታቅዶ የነበረው ሚያዚያ 10 ቀን የነበረ ሲሆን ከዚያ በኋላ በተደጋጋሚ በታቀዱት ቀናት ወደ ጃባ ባለመለሳቸው በዓለም አቅፉ ህብረተሰብ በሌሎች ላይ ከፍተኛ ስጋት ፈጥሮ እንድነበር አይዘነጋም።

No comments:

Post a Comment