Saturday, April 30, 2016

በጃዋር መሃመድ ሀሳቦች ላይ! – አስራት አብርሃም


የጃዋር ፖለቲካ ተራማጅ አይደለም የምልበት ዋና ምክንያት አሁንም ፖለቲካው ከሶስቱ ብሄሮች (አማራ፣ ኦሮሞና ትግራይ) ጠበኛ ልሂቃን እይታ ያልወጣ መሆኑ ነው። ለእኔ አሁን ባለችው ኢትዮጵያ ተራማጅ አስተሳሰብ የምለው የተለመደውን የብሄር ፖለቲካ ካርድ እንስቶ በተሻለ ሁኔታ መጫወት ሳይሆን በዜግነት መብት ላይ የሚያተኩር፤ ለሁሉም ኢትዮጵያውያን የሚመች ስርዓት ለማምጣት የሚታገል፤ ፍቅርና ወንድማማችነትን ሃገራዊነትን የሚሰብክ፤ እኩልነትና ዴሞክራሲ ለማምጣት በእምነትና በመርህ የሚገዝ ሰው፤ ወይም ተቋም ነው ወይም አስተሳሰብ ነው።
በዚህ በእኩል በሶሻል ሚዲያው ተፅዕኖ ፈጣሪ ከሆኑ ኢትዮጵያዊያን ውስጥ የዜግነት ብሄርተኝነት የሚያቀነቅን፤ ቅንነትና የአቋም ያለመዋዠቅ ያለው ሰው “ከጎሣ ይልቅ ሰብአዊነትን እናስቀድም” የሚለው ኦባንግ ሜቶ (Obang Metho) እና ድርጅቱ “ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ” (Solidarity Movement for a New Ethiopia) ብቻ ይመስለኛል። አለበዚያ ስለፖለቲካዊ ለውጥ፣ ዴሞክራሲና እኩልነት አስባለሁ እያሉ፣ በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠሩ የደቡብ ኢትዮጵያ፣ የሶማሌ፣ የትግራይ፣ የአፋር፣ የጋምቤላ፣ የቤንሻንጉል ወዘተ ህዝብ ያገለለ ፖለቲካዊ ትብብር ውጤታማ ይሆናል ብሎ አያስብም። ይሄ አካሄድ ስርዓቱን በአቋራጭ ለመጣል ይጠቅም እንደሆነ እንጂ ሰላም፣ ፍትህ፣ ሃገራዊ አንድነት፣ ዴሞክራሲና እኩልነት ግን በዚህ መንገድ ፈፅሞ ሊገኝ አይችልም፤ በሀገሪቱ ያሉትን ዜጎች ያገለለ ከመሆኑ አንፃር ሃገራዊ አስተሳሰብም አይደለም። ከዚህ አንፃር የጃዋር ሀሳብ ተራማጅ ያለመሆኑ ብቻ ሳይሆን ጠቃሚም አይደለም።
ሁለተኛው የጃዋር መሀመድ ችግር ዘላቂ (consistency) የሆነ የፖለቲካ አቋም ወይም እምነት ያለመኖር ነው። በፖለቲካ ትግል ውስጥ የማትደራደርባቸውና በቀላሉ የማትለውጣቸው መሰረታዊ የሆኑ ፖለቲካዊ አቋሞች ወይም እምነቶች ወይም ራስህን የምትገልፅበት ማንነቶች ይኖራሉ። አንድ ሰው ወይም ፖለቲካዊ ድርጅት አቋሙ ለወዳጅም ለጠላትም ግልፅ ሆኖ ሲታይ ወይ ሲታወቅ ነው ለመደራደርም ሰጥቶ ለመቀበልም የተመቸ የሚሆነው። ማንነቱና ፖለቲካዊ አቋሙ የሚታወቅ ከሆነ ከእነዚህ መሰረታዊ አቋሞች ውጭ ባሉት ጉዳዮች ላይ ለመደራደር አስቸጋሪ አይሆንም። ስለዚህ በፖለቲካ ትግል ውስጥ መተጣጠፍና መገለባበጥ የሚቻለው መሰረታዊ ባልሆኑ ፖለቲካዊ አቋሞችና የትግል ታክቲኮች ላይ ብቻ ነው። ከዚህ ያለፈ መገለባበጥና መለዋወጥ መርህ አልባነት ከመሆኑ ውጪ ፖለቲካዊ ጥበብ አይመስለኝም። ምክንያቱም የራሱ የሆነ ፅኑ ፖለቲካዊ አቋም ከሌለው አካል ጋር ሌላው ለመደራደርና በሙሉ ልብ አብሮ ለመጓዝና ለመስራት ያስቸግሯል።
ለምሳሌ የአማራና የኦሮሞ ህዝብ በግጭትና በትብብር ለዘመናት አብሮ የኖረ ነው ያለው ከአሁን በፊት ይለው ከነበረው ጋር ፍፁም ተቃራኒ ነው። ከቀኝ ገዥና ተገዥ ትርክት ባንዴ ወደዚህ ጫፍ አትመጣም። አሁን መጨረሻ ላይ ይህን ሀቅ የተገጠለት ማድረግ የፈለገውን ማድረግ ስላልቻለ እንጂ ከልቡ ስለሚያምንበት ነው ለማለትም እቸገራለሁ። ይህ እውነት በኦሮሞውና በአማራው ብቻ ሳይሆን በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉት ልዩ ልዩ ህዝቦች ሁሉ ተመሳሳይ የግጭትና የትብብር ረጅም ታሪክ እንዳላቸው እርግጥ ነው። በትግራይና በአማራ፣ በኦሮሞውና በደቡቡ እንደዚህ ዓይነት ግንኝነቶች ነበሩ፤ አሁንም አሉ። ስለዚህ ይህን እውነት በተሸራረፈ መንገድ ሳይሆን እንዲህ በተሟላ ሁኔታ መገንዘብ ያስፈልግ ነበር፤ ነገር ግን ጃዋር ለጊዜው የአማራው ልሂቅ የታክቲክ ትብብር ስለሆነ የፈለገው የሁለቱን ህዝቦች ግንኙነት ብቻ ነጥሎ በማውጣት ሊጠቀምበት ፈልጓል ማለት ነው። እንደዚያም ሆነ በእነዚህ ሁለት ልሂቃን መካከል የሚኖርን ትብብር በምን ላይ የተመሰረተ እንደሆነ ያስቀመጠው ነገር የለም። “ፖለቲካ ማለት ማን ምን አገኘ?” የሚል ጥያቄ የያዘ በመሆኑ ሰጥቶ የመቀበል ጉዳይ ነው።
ጃዋር የኦሮሞ ፖለቲካ ወኪል አድርገን እናስበውና ለአማራ ልሂቃን የእንተባበር ጥያቄ ሲያቀርብ ከእርሱ በእኩል ምን ለመስጠት ነው የፈለገው? የሚለውን ስናይ ምንም ሆኖ ነው ያኘሁት። ህወሀትን በጋራ አስወግደን እኛ የኦሮምያን ለም መሬት ባለቤት እንሆናለን፤ እናንተ ደግሞ የመተማ፤ የጠገዴና የወልቃይት ለም መሬት ባለቤት ትሆናላችሁ ዓይነት ነገር እንጂ ኢትዮጵያ በጋራ እንጠቀማለን፣ አብረን በሰላም እንዳአንድ ሃገር እንኖራለን፤ የኢትዮጵያ የግዛት አንድነት ሳይሸራረፍ ይቀጥላል የሚል ምንም ነገር አላየሁበትም። ከእነዚህ ሁለት ክልሎች ውጨ ያለውን ህዝብና መሬት ምን እንደሚሆን የተቀመጠ ነገር የለም። ይሄ በጣም አስፈሪው ገፅታው ነው። ሁሉት ብሄሮች በዚህ ጉዳይ ሊስማሙ የሚችሉት ሁለቱም ከዋናው ሃገር ለመገንጠል በአንድ ላይ ለመዋጋት ሲስማሙ ነው ልክ እንደ ህወሀትና ሻዕቢያ። ለምሳሌ ይሄ በኦነግና በኦጋዴን ነፃ አውጪ ግንባር ማካከል የነበረው ትብብር በዚህ ዓይነቱ ስሜት የተቃኘ ነበር።
በመሰረቱ የአማራ ልሂቃን አሁን በኢህአዴግ የተሰጣቸውን ክልል ብቻ ይዘው ለመኖር የጃዋርን ትብብር የሚያስፈልጋው አይመስለኝም። ሌላው የአማራ ልሂቃን ኦሮሚያ እንድትገነጠል የሚፈልጉ አይመስለኝም፤ ስለዚህ ጃዋር ከእነዚህ ጋር ለመስራት ከፈለገ አቋሙን ነው በትክክል መቀየር ያለበት። አንደኛ በኢትዮጵያ የግዛት አንድነት ማመን አለበት፤ ሁለተኛ ህዝቦቿ የተሳሰረ የጋራ እድል እንዳላቸው፤ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ለማምጣት የሁሉም ተሳትፎ እንደሚያስፈልግ መቀበል ይኖርበታል። እንደዚሁም በኢትዮጵያ ጨቋኝ ስርዓቶች እንጂ በቀኝ ግዛት መልክ የገዥና የተገዥ ግንኙነት እንዳልነበረ ከልብ መረዳት ያስፈልጋል።
በሌላ በእኩል ኦፌኮ የኦሮሞ ህዝብ ወኪል እንደሆነ ገልፀዋል፤ እንደዚያ ከሆነ ደግሞ የኦፌኮ ፕሮግራም ማየት ይኖርብናል ማለት ነው። ኦፌኮ በኢትዮጵያ ትክክለኛ ፌደራሊዝምና ዴሞክራሲያዊ ስርዓት እንዲኖር ይፈልጋል፤ አሁን ያለውን የኦሮሚያ ክልል ካርታ ያለመሸራረፍ እንዲከበር ይፈልጋል፤ አዲስ አበባ በኦሮሚያ ግዛት ውስጥ የሚገኝ በመሆኑ ኦሮሚያ ከአዲስ አበባ ልዩ ጥቅም እንድታኝ ይፈልጋል፤ ኦሮምኛ ልክ እንደአማርኛ የፌደራል መንግስት የስራ ቋንቋ እንዲሆን ይፈልጋል። ስለዚህ የአማራ ልሂቃን ቢያንስ በእነዚህ ከመገንጠል በመለስ ያሉትን የኦሮሞ ፖለቲካ ጥያቄዎች ለመቀበል ይችሉ ይሆናል፤ ይህን ሲቀበሉ ግን የሚያገኙት ነገር ሊኖር ይገባል። ይሄ ሲሆን ሌላው ደቡብ ትግራዩ አፋሩ ጋምቤላው ቤንሻንጉሉ ምንድነው የሚያደርገው ዝም ብሎ ያያል። ሀሳቡ ራሱ ገና ከመነሻው የከሸፈ መሆኑ የሚያሳየው እዚህ ላይ ነው።
ኦፌኮ ይህን ፍላጎቱን በተወሰነም ቢሆን በመድረክ ውስጥ ያሉትን ፓርቲዎች ለማሳመን ሙከራ ያደርጋል፤ ለምሳሌ ሁለተኛ ቋንቋ ይኑር በሚለው ጉዳይ ላይ አረና፣ የያኔው አንድነት፤ የበየነ ፓርቲዎች ተቀብለውት ነበር። ከዚህ ውጪ ከአንድ ወገን ብቻ የሚደረግ ትብብር ኢህአዴግ እስከሚወድቅ ድረስ ብቻ የሚቆይ እንጂ ዘላቂ አይሆንም። ሌላው ጃዋር እንደሚያስበው ህዝብ ዝም ብሎ ተባበር ስላልከው ብቻ አይተባበርም፤ አንድላይ ሁን ስላልከው ብቻ ተነድቶ አንድ ላይ አይሆንም፤ ሰው የከብት መንጋ አይደለምና። ይሄ ህዝብን መናቅ ነው፤ ህወሀትም እስከዛሬ ሲያደርገው የኖረውን ነገር ነው።
ሶስተኛው ነገር የትግራይ ልሂቃን ተራማጅ ለመሆን አልቻሉም ያለበት ነገር ነው። አንደኛ እውነትነት ያለው አይደለም፤ ሁለተኛ ደግሞ የእርሱ የተራማጅነት መለኪያ ምን እንደሆነ ግልፅ አይደለም፤ እሱ ሜኒሶታ ሆኖ አቧራ ባስነሳ ቁጥር ለምን ድጋፍ አልሰጡኝም ከሆነ ብዙ የሚያስኬድ አይደለም። እንደ ትግራይ ልሂቅነታቸው የራሳቸው የሆነ ክልላዊና ሃገራዊ አጀንዳዎች ይኖራቸዋል። ከዚህ ፍላጎቻቸው ተቃራኒ የሆኑ እንቅስቃሴዎች ሲደረጉ ድጋፍ ላይሰጡ ይችላሉ። ለምሳሌ እኔ በኢትዮጵያዊ ብሄርተኝነት አምናለሁ፤ ህወሀት ለኢትዮጵያ ጥሩ ስርዓት እንዳልሆነም አውቃለሁ። በዚህ ምክንያትም በተቻለኝ አቅም ሁሉ ስታገለው ኖሬያለሁ፤ ነገር ግን “የትግራይን ህዝብ ከህወሀት ጋራ ደርበን እንመታለን” የሚሉትን አንዳንድ ፅንፍ የረገጡ ኃይሎች አልቀበላቸውም።
አስር ሺህ የማይሞላ ትግርኛ ተናጋሪ በስርዓቱ ተጠቃሚ ስለሆኑ “የትግራይ ህዝብ ሁሉ ተጠቃሚ ነው” የሚለኝም አልቀበልም፤ ምክንያቱም እኔ ትግራይ ውስጥ ኖሬ ነው እውነታውን የማይቀው። ስለዚህ እኔ በትክክል ስለማውቀው ነገር አሜሪካ ወይም አውሮፓ ወይም አዲስ አበባ ሆኖ ተቃራኒው እንዲነግረኝ አልፈልግም። ሌላው የጃዋር መከራከሪያ ደካማ የሚያደርገው ምክንያት ደግሞ “አራት መቶ ሰው ሲጨፈጨፍ አንድም የትግራይ ልሂቅ ወጥቶ “አረ ይኼ ግድያ ትክክል አይደለም” አለማለቱ እንደሆነ አስቀምጠዋል።
እርሱ አልሰማም ይሆናል እንጂ ቢያንስ እራሱ “የኦሮሞ ህዝብ ወኪል ነው” ካለው ኦፌኮ ጋር አብሮ በመድረክ ጥላ ስር ያለው አረና በስራ አስፈፃሚ ደረጃ ተወክሎ አብሮ መግለጫ ሲሰጥ ተመክቻለሁ። እነ አረጋዊ በርሄ፣ ግደይ ዘርዓፅዮንና የመሳሰሉት አንጋፋ የትግራይ ፖለቲከኞች አሉበት የሚባለው ሸንጎ የተባለ በውጭ የሚኖሩ ፓርቲዎች ስብስብም ግድያውን አውግዘዋል። እንግዲህ አሁን ባለው ነባራዊ ሁኔታ ኦፌኮ የኦሮሞ ህዝብ ወኪል ነው ካለ አረናም የትግራይ ህዝብ ወኪል የማይሆንበት ምንም ምክንያት የለም። ስለዚህ የትግራይ ልሂቃን ወገናቸው በሆነው የኦሮሞ ህዝብ ላይ ስለደረሰው ነገር ለጃዋር ስልክ እየደወሉ ወይም በፌስቡኩ ስር ተስልፈው አቋማቸውን ማሳወቅ የነበረባቸው አይመስለኝም። እንዲያውም እኔ አልፎ አልፎ ከትግራይ ልጆች ጋር ስንወያይ የኦሮሞ ፖለቲካ በኢትዮጵያ ባለው የኃይል አሰላለፍ እንደተፈጥሯዊ አጋር የማየት ሁኔታ ነው የማየው። ይሄ ህወሀት የፈጠረው ትፅዕኖ ሊሆን ይችላል። እንደእኔ እምነት ግን አንድ ህዝብ በአንድ ሃገር ውስጥ ከሌላው ነጥሉ አጋር አንዱን ደግሞ ጠላት ወይም ስጋት የማድረግ አካሄድ አላምንበትም።
ስለተራማጅነት ከተነሳ አረና በነበርኩበት ወቅት ኦሮምኛ ሁለተኛ ብሄራዊ ቋንቋ እንዲሆን በመድረክ መለስተኛ ፕሮግራም ላይ ተወያይቶ በሙሉ ድምፅ ነበር ያፀደቀው፤ ለእኔ ከዚህ በላይ ተራማጅነት የለም። ከአቶ ገብሩ አስራት በስተቀር ያለበት ጉዳይ ራሱ በጣም አስቂኝ ነው፤ አቶ ገብሩ አስራት በአረና ውስጥ ካሉት ወይም ከአረና ውጪ ካሉት የህወሀት ተቃዋሚዎች በኦሮሞ ጉዳይ ላይ የተለየ አቋም ያለው አይመስለኝም፤ “ከገብሩ በስተቀር ዓረና ውስጥ ያሉትን ወጣቶች “የአንድነት ኃይል” ተፅዕኖ አለባቸው” እየተባለ በመድረክ ኮሪደር አከባቢ የሚወራውን ነው የደገመው፤ ምንም አዲስ ነገር የለውም። መድረክን እንደ አንድ ኃይል አለመስወዱ ግን መድረክ ከሚያደርገው እንቅስቃሴ ደካማነት አንፃር ተገቢ ሊሆን ይችላል።
ሌላው የሕወሓት አወዳደቅ የትግራይ ሕዝብን ይዞ እንዳይወድቅ መጥንቀቅ አስፈላጊ ነው፤ …. ማንም ይኹን ምን ኢትዮጵያ ውስጥ የአንድ ብሔረሰብ መጎዳት ለኢትዮጵያም ኾነ ለአጠቃላዩ የምሥራቅ አፍሪካ መልካም አይደለም።” ያለው ተገቢ የሆነ ግንዛቤ ነው። ቢያንስ ምንም ምንም በማይደርስበት የውጭ ዓለም ተቀምጠው፤ በርገራቸውን እየገመጡ “የእኛ ትግል የትግራይ ህዝብ ካልደገፈ እኛ ወደ ስልጣን ስንመጣ ወዮውለት” ከሚሉት አንዳንድ የዲያስፖራ ፖለቲከኞች የተሻለ አቋም ነው።
በመሰረቱ ህወሀትንና የትግራይን ህዝብ ለይቶ የማያይ የፖለቲካ አስተሳስብም ሆነ እንቅስቃሴ መጨረሻው ውድቀትና መከራ ለሁላችን ያመጣ እንደሆነ እንጂ ለድል የሚበቃ አስተሳሰብ አይደለም። የትግራይ ህዝብ ከህወሀት የተለየ ምን ሊያደርጉለት እንደሚችሉ ማሳመን ያለባቸው እነርሱ ናቸው፤ ይህን ማድረግ ካልቻሉ የራሳቸው ችግር ነው። ገና ለገና መንግስት ሲሆኑ ሊያጠቁኝ ይችላሉ ብሎ ፈርቶ የትግራይ ህዝብ ማንምም ሊደግፍ አይችልም፤ እንደዚያ ዓይነት ታሪክም የለውም። ስለዚህ ሊማርከው ያልቻለን ፖለቲካ ያለመደገፍ መብቱ ነው፤ ህወሀት መጥፎ ስለሆነ ሌለው ሁሉ ጥሩ ነው ማለት አይደለም። እኔ የሚያሳስበኝ ነፃ ያለመሆኑ ነው እንጂ ነፃ ሆኖ ህወሀትም ቢደግፍ ህዝብ እንደህዝብ ተሳስቷል የምልበት ሞራል አይኖረኝም ነበር። እንዲያውም እንደህዝብ በህወሀት ታግቶ እየኖረ ያለ በመሆኑ ሊታሰብለት ነው የሚገባው።
ተራማጅ የሆነ ፖለቲካዊ አስተሳሰብ ያለው ማንኛውም ሃይል የትግራይ ህዝብ ነፃ ሆኖ የፈለገውን እንዲደግፍ ነው እድል ማመቻቸት ያለበት እንጂ በልዩ ልዩ ተፅዕኖና በፍራቻ ውስጥ ሆኖ እየኖረ ለህወሀት ይደግፋል ማለት እጅግ በጣም ፍርደ ገምድልነት ነው። በድንብ መሰመር ያለበት ጉዳይ እንዲህ ከሚያስቡ ኃይሎችና ግለሰቦች ጋር የትግራይ ልሂቅ ትብብር ሊኖረው አይችልም።
ለሁሉም ነገር አስታራቂው ሀሳብ የሚመስለኝ፤ በዜግነታዊ ብሄርተኝነት (Civic Nationalism) ሁላችንንም እኩል የምንሆንበትን ስርዓት ለማምጣት እንታገል የሚል ነው። ሁሉም ኢትዮጵያዊ ተጠቃሚ የሚያርግ፤ በህግ የበላይነት የሚመራ፤ አድልዎ የሌለበት ስርዓት ታግለን እንትከል የሚል ጥሩ ሀሳብ ነው። ይሄ ሀገር እዚህ እንዲገኝ ሁሉም አስተዋፅኡ አድርጎበታል፤ ችግር እየሆነ ያለው ሁሉም ተጠቃሚ ያለመሆኑ ነው። ይሄ ነው ማስተካከል ያለብን። ሁለተኛ ደግሞ መገንጠል መፍትሄ ያለመሆኑ ነው። ከዚያ አከባቢ ነቅለህ አይደለም የምትሄደው፤ አሳባዊ የሆነ መሬት ላይ የሌለ ድንበር አበጅተህ ነው ጎን ለጎን ተፋጥጠህ የምትኖረው። ስለዚህ እንዲህ ተፋጥጠህ ከምትኖር በሰላም ተግባብቶ መኖር አማራጭ የሌለው መፍትሄ ስለሆነ ነው

No comments:

Post a Comment