Sunday, July 24, 2016

‹‹ለአገሪቱ ሰላምና መረጋጋት ብሔራዊ ዕርቅ ወሳኝ ነው›› በጎንደር በደረሰው ጉዳትም መንግሥትን ተጠያቂ ነው



–  መአሕድ በሰሜን ጎንደር ለደረሰው ጉዳት መንግሥትን ተጠያቂ አድርጓል
የኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያ ፓርቲ (ኢዴፓ) ሰሞኑን በጎንደር የታየውና  በአገሪቱ የሚነሱ አብዛኞቹ ግጭቶች መነሻ ምክንያታቸው፣ አገሪቱ የምትከተለው ቋንቋና ብሔረሰባዊ ማንነት መሠረት ያደረገው የፌዴራላዊ አደረጃጀት ነው ብሎ እንደሚያምን ገለጸ፡፡ በመሆኑም ኢትዮጵያን ለመሰለች የራሷ አብሮ የመኖርና የመቻቻል ባህል ያላትና ሉዓላዊነቷ ተጠብቆ ለኖረች አገር፣ የሚመጥንና የሚገባ ይዞታ ያለው ፌዴራላዊ አደረጃጀት ያስፈልጋታል አለ፡፡
‹‹ለአገሪቱ ሰላምና መረጋጋት ብሔራዊ ዕርቅ ወሳኝ ነው›› በሚል ርዕስ ሐምሌ 14 ቀን 2008 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ ቋንቋና ብሔራዊ ማንነትን ዋነኛ መሠረት ያደረገው የፌዴራሊዝም አደረጃጀት ባለፉት 25 ዓመታት ተፈትሾ ግጭቶችን፣ ልዩነቶችንና አለመግባባቶች እንዲበረክቱ ያደረገ በመሆኑ ሊስተካከል ይገባል ብሏል፡፡
በኢዴፓ እምነት መሠረትም አገሪቱ ልትከተል የሚገባው የፌዴራሊዝም ሥርዓት ቋንቋን፣ የመሬት አቀማመጥን፣ የሕዝብ ብዛትን፣ የኅብረተሰቡ አብሮ የመኖር ታሪካዊ ትስስርን፣ አስተዳደራዊ አመቺነትንና የኢኮኖሚ ጥቅም የአከላለል መመዘኛዎች ሊሆኑ እንደሚገባ ገልጿል፡፡ በመሆኑም መንግሥት አሁንም አገሪቱ ወደለየለት ግጭት ውስጥ ከመግባቷና ጊዜው ሳይረፍድ የፌዴራሊዝም አደረጃጀት ሥርዓቱን እንዲፈትሽ ጠይቋል፡፡
በገዥው ፓርቲ ተቀርጾ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፀደቀው የኢትዮጵያ ሕገ መንግሥት ‹‹ብሔር ብሔረሰብና ሕዝብ ማለት ሰፋ ያለ የጋራ ፀባይ የሚያንፀባርቅ ባህል ወይም ተመሳሳይ ልምዶች ያላቸው፣ ሊግባቡበት የሚችሉበት የጋራ ቋንቋ ያላቸው የጋራ ወይም የተዛመደ ሕልውና አለን ብለው የሚያምኑ፣ የሥነ ልቦና አንድነት ያላቸው በአብዛኛው በተያያዘ መልክዓ ምድር የሚኖሩ ናቸው፤›› በማለት መደንገጉ ይታወቃል፡፡
ኢዴፓ በመግለጫው ለሕዝብ ተቃውሞና ጥያቄዎች መንግሥት ከኃይል ዕርምጃ እንዲቆጠብ፣ የወልቃይት ጠገዴ ሕዝብን የማንነት ጥያቄ በሕገ መንግሥቱ መሠረት እንዲፈታ፣ የደረሰውን የአካልና የሕይወት ጉዳት የሚያጣራ ኮሚቴ እንዲቋቋም ጠይቋል፡፡
በተጨማሪም ከግጭቱ ጋር በተያያዘ የታረሱ ዜጎች ሰብዓዊ መብታቸው እንዲጠበቅና የመጎብኘት መብታቸው ተጠብቆ ግልጽ በሆነ ፍትሕ እንዲዳኙ፣ ሕዝብ ሕገ መንግሥታዊ ጥያቄ የማቅረብ መብቱ እንደተጠበቀ ሆኖ የአገሪቱን አንድነትና የሕዝቡን አብሮነት የሚጎዱ ተግባራት ከመፈጸም እንዲቆጠብ፣ የአገርና የሕዝብ ሀብት ንብረቶችን የሚጎዱ ድርጊቶችን እንዳይፈጽም፣ በአገር ውስጥና በውጭ አገር የሚተላለፉ የመንግሥትና የግል ሚዲያ ለሰላም ሙያዊ ግዴታቸውን እንዲወጡ ጥሪ አቅርቧል፡፡ ለአገሪቱ ሰላምና መረጋጋት ብሔራዊ ዕርቅ ወሳኝ ነው ብሏል፡፡
በሌላ በኩል የመላው አማራ ሕዝብ ድርጅት (መአሕድ) በበኩሉ መንግሥት ለወልቃይት ጠገዴ ሕዝብ ጥያቄ ወቅታዊ ምላሽ ባለመስጠቱ፣ በሕዝብና በመንግሥት መካከል አለመተማመን መፈጠሩን ገልጿል፡፡ ከወልቃይት ጥያቄ ጋር ተያይዞ ሰሞኑን በጎንደር በደረሰው ጉዳትም መንግሥትን ተጠያቂ አድርጓል፡፡

No comments:

Post a Comment