Thursday, July 28, 2016

የሕወሓት የሃሰት ክስ ቀጥሏል:: ኦሮሚያን ለመገንጠል በሚንቀሳቀስ አዲስ ድርጅት ውስጥ በመሳተፍ የተጠረጠሩ ተከሰሱ


የኢትዮጵያን አንድነት የማፈራረስና ኦሮሚያን ከፌዴሬሽኑ የመገንጠል ዓላማ ይዞ በህቡዕ ሲንቀሳቀስ እንደነበር በተገለጸው የኦሮሞ አንድነት ግንባር (ዩኤልኤፍኦ) በሚል ስያሜ አዲስ በተቋቋመ ድርጅት፣ የሽብር ወንጀል ለመፈጸም አባል በመሆን ሲንቀሳቀሱ ተደርሶባቸዋል የተባሉ 17 ተጠርጣሪዎች ላይ ክስ ተመሠረተባቸው፡፡
የፌዴራል ዓቃቤ ሕግ ማክሰኞ ሐምሌ 19 ቀን 2008 ዓ.ም. ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት በተጠርጣሪዎቹ ላይ ያቀረበው ክስ እንደሚያስረዳው፣ አዲስ የተቋቋመው የኦሮሞ አንድነት ግንባር ድርጅት በኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በአሸባሪነት የተፈረጀውን የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) ዓላማና ተልዕኮ ለማጠናከር መሆኑን ገልጿል፡፡
ተከሳሾቹ ከአዲስ አበባ፣ ከኦሮሚያ፣ ከድሬዳዋ፣ ከምሥራቅና ምዕራብ ሐረርጌ በመውጣጣት ከአዲስ አበባና ከኦሮሚያ የተቀናጀ ማስተር ፕላን ጋር በተያያዘ ተነስቶ የነበረውን አመፅ እንዲቀጣጠል፣ በተለይ በምሥራቅ ሐረርጌ በጋራ ሙለታና በበዳኖ ቡድን እያደራጁ በመላክ የመንግሥትን ታጣቂዎች ትጥቅ እንዲያስፈቱና በየትምህርት ቤቱ የተሰቀለውን የኢፌዴሪ ሰንደቅ ዓላማ በማውረድ፣ የኦነግን ባንዲራ እንዲውለበለብ ያስተባብሩ እንደነበር የዓቃቤ ሕግ ክስ ያስረዳል፡፡
ተከሳሾቹ የኦነግን የፖለቲካ ፕሮግራምና ዓላማ ሳይቀይሩና ባንዲራውም ከኮከቡ በስተቀር አንድ ሆኖ፣ የኦሮሞ አንድነት ግንባር በሚል ስያሜ እስከ መጨረሻው የኢትዮጵያን መንግሥት በትጥቅ ትግል ታግለው ለመጣል፣ መቀመጫውን እንግሊዝ አገር ካደረገው የኦነግ ከፍተኛ አመራር ጋር መስማማታቸውን የዓቃቤ ሕግ ክስ ይገልጻል፡፡
የኦነግ ከፍተኛ አመራር መሆኑ የተገለጸው አብደላ መሐመድ መኖሪያው አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ መሆኑ በክስ ከተገለጸው አንደኛ ተከሳሽ አሚን ዩዬ ሙሐመድ (ነገዎ ቢሎ) ጋር በስልክ ተነጋግረው በተስማሙት መሠረት፣ 1,100 የአሜሪካን ዶላር ልኮለት ለሽብር ተግባር ማስፈጸሚያና አባላትን ለመመልመል መስማማታቸውንና ተግባራዊ ማድረጋቸውንም ክሱ ያብራራል፡፡
የኦነግ አመራሮች የኦሮሞ አንድነት ግንባርን በአዲስ መልክ ማደራጀት በዋናነት የፈለጉት፣ በጫካና በከተማ ሽብር በመፍጠር ኅብረተሰቡ የኢትዮጵያ መንግሥትን ጠልቶ ከሥልጣኑ እንዲወገድ ለማድረግ መሆኑንም ክሱ ይጠቁማል፡፡
ኦሮሚያን ከፌዴሬሽኑ የመገንጠል ዓላማ የነበረውን የኦነግን ተልዕኮ ለማስፈጸም በመንግሥት ላይ ተፅዕኖ በማሳደርና ኅብረተሰቡን በማስፈራራት፣ የአገሪቱን መሠረታዊ የፖለቲካ፣ ኢኮኖሚና ማኅበራዊ ተቋማትን ለማናጋትና ለማፈራረስ የኦሮሞ አንድነት ግንባር ከ2004 ዓ.ም. ጀምሮ ሲንቀሳቀስ እንደነበርም በክሱ ተገልጿል፡፡ ተከሳሾቹ በአሜሪካ፣ በእንግሊዝ፣ በሳዑዲ ዓረቢያና በሌሎችም አገሮች ከሚገኙ የኦነግ አመራሮች ተልዕኮ በመቀበል፣ በኤርትራና በሶማሊያ ወታደራዊ ሥልጠና በመውሰድ ኢትዮጵያ ከመጡ በኋላ፣ ሐረርና ሌሎች አካባቢዎች በመሄድ በህቡዕ ተደራጅቶ በኢትዮጵያ ውስጥ በሚንቀሳቀሰው የኦሮሞ አንድነት ግንባር ውስጥ አባል መሆናቸውንም ክሱ ያስረዳል፡፡
ሁሉም ተከሳሾች የኦነግን ዓላማና ተግባር በተጠናከረ ሁኔታ ለማስቀጠል የኦሮሞ አንድነት ግንባር በሚል ስያሜ በተቋቋመው የሽብር ቡድን ውስጥ አባል በመሆን በአዲስ አበባ የካቲት 21 ቀን 2008 ዓ.ም. በዲአፍሪክ ሆቴል የሽብር ቡድኑ በጠራው ስብሰባ ላይ መሳተፋቸውን ክሱ ይገልጻል፡፡ በስብሰባውም ላይ እንደተስማሙት በኦሮሚያ ክልል የተጀመረው አመፅ እንዲቀጥል በየአካባቢያቸው የማስተባበር ሥራ እንዲሠሩ ሎጂስቲክስ፣ ስንቅና የጦር መሣሪያ እንደተዘጋጀ ሁሉም ወደ ጫካ በመግባት መንግሥትን በትጥቅ ትግል ለመለወጥ መታገል እንዳለባቸው መስማማታቸውን ክሱ ያብራራል፡፡ የተከሳሾቹን የቅድመ ክስ መቃወሚያ ለመስማት ፍርድ ቤቱ ለሐምሌ 27 ቀን 2008 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

No comments:

Post a Comment