Friday, July 29, 2016

ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ፤


በሰመረ አለሙ
በምንኖርበት በምእራቡ አለም ዜጎች ከምርጫ በፊት መሪዎቻቸዉን ይገመግማሉ፤ያለፈ ታሪካቸዉን፤ልምዳቸዉን፤ማህበራዊ ተሳትፎዋቸዉን በተለይም ሀገር ወዳድነታቸዉን ከግምት ከተዉ ከሌሎች ተወዳዳሪዎች አንጻር ለቦታዉ ብቁ መሆናቸዉነ መርምረዉ መዝነዉ ይመርጣሉ። በዚህ ሁኔታ የተመረጠ መሪ መልካም ስነምግባር ይኖረዋል; ለአላማዉ የጸና ይሆናል;አድልዎን ይጠየፋል፤መልካም አስተዳደርን ያሰፍናል፤ ለአገር ዘላቂ ጥቅም ለማስገኘት በርትቶ ይሰራል ፤ሃላፊነቱንም በብቃት ይወጣል። የዚህ ጽሁፍ አንባበዎችም ይህ አሰራር ከማይተገበርበት ከምስራቁ፤ ከአረቡ አለምና ከአፍሪቃ ሀገሮች ኮብልለን ይህን በሚያራምዱ በምእራብ አገሮች ተጠልለን በምንፈልገዉ ምርጫ የምንፈልገዉን ተወዳዳሪ እየመረጥን ያለንበት ሀገር የሰጠንን መብት እያጣጣምን እንደምንኖር በእርግጠኝነት መናገር ከማስቻሉም በላይ ይህ አሰራር ወደ አገራችን የሚደርስበትን ሁኔታም በአይነ ህሊና እያየን እንገኛለን እንጥራለንም።
ታዲያ የጽሁፌ መንደርደሪያ ይሄ ሁኖ ዛሬ በፖለቲካዉ ምህዳር ከሀገር ቤት ዉጭ ድርጅት መስርተዉ ጦር ሰብቀዉ የተነሱትን የድርጅት፤የፖለቲካ፤እና የጦር መሪ የሆኑትን ዶር ብርሀኑን ከዚህ በፊት ባልተለመደ መልኩ ዜጎች በልባቸዉ ያለዉን ወደ ዉጭ እንዲያወጡ ለመጋበዝ በይዘቱ ልዩ ሊሆን ይችላል ብዬ ያሰብኩትን ጽሁፌን ለአንባቢ አቅርቢያለሁ። በእርግጥ ይህ ሙከራ አዲስ አይደለም ቀደም ባለዉ ጊዜ ዶ/ር በየነ ጴጥሮስን ግርማ ካሳ በተባ ብእሩ ሲጎበኛቸዉ አሰፋ ጫቦም ተደርቦ ዶክተሩን ከዉስጥ ወደ ዉጭና ከዉጭ ወደ ዉስጥ እንድናይ ረድቶናል ክፋቱ አቶ አሰፋ ጫቦም ከዚሁ ፍላጻ አላመለጠም።
የጽሁፉ ዋና አላማ በመሪነት ስም የሚመጡትን ግለሰቦች ለመተናኮል ሳይሆን ለመሪነት ከመብቃታቸዉ በፊት በሚገባ ይገምገሙ ለማለት ነዉ። እንደ ልማድ ሁኖ በህይወት የሌሉትን ብቻ ከማብጠልጠል በህይወት ስላሉ የድርጅት መሪዎች ስብእና፤ብቃት፤ችሎታ ተመሪዉ ህዝብ በቂ ዘገባ ያስፈልገዋል ብዬ አምናለሁ። ገብሩ አስራት፤ሌንጮ ለታ፤አረጋዊ በርሄ፤አንዳርጋቸዉ ጽጌ፤ብርሀኑ ነጋ፤ሰየ አብረሀ፤ኢያሱ አለማየሁ፤አሰፋ ጫቦ፤ኤርምያስ ዋቅጂራ የመሳሰሉ ግለሰቦች ድርጅት መስርተዋል ወይም ደግሞ በተመሰረተ ድርጂት ዋና ተዋናይ ነበሩ ድርጅታቸዉም ዉስጥ ከፍተኛ ተሳትፎም አድርገዋል አንዳንዶቹም ድርጅታቸዉ በለስ ቢቀናዉ ኢትዮጵያን ይረከቡ ነበር። ከእነዚህ መሀልም ዛሬ ፍዳችንን የሚያበላንን የህወአትን መሰረት የጣሉ ወይም ደግሞ ቀደም ባለዉ ስርአት ተዋናይ የነበሩ መሆናቸዉን ከ30 እስከ 85 የእድሜ ቅንፍ ዉስጥ ያለን በሚገባ እናዉቃለን። በእንጻሩም እነዚህ ግለሰቦች ዛሬ መሰረቱን የጣሉለትን የህወአትን መንግስት በእነሱ ፊታዉራሪነት እንድንጥለዉ ያሳስቡናል። የዚህ ጽሁፍ መክፈቻ ዶ/ር ብርሀኑ ቢሆኑም ሌሎችንም እንዲሁ ቀሪዉ ኢትዮጵያዊ እንዲጎበኛቸዉ እያሳሰበኩ ዘገባዬን በሚከተለዉ መልኩ አቀርባለሁ።
ከ60ዎቹ (የምን እንቅስቃሴ ብየ እንደምጠራዉ ቸግሮኝ ነዉ) ባሉት እንቅስቃሴዎች ሁሉ የዶ/ር ብርሀኑ ስም በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ያልተጠቀሰበት እሳቸዉም በተለያየ ክብደት እጃቸዉን ያላስገቡበት እንቅስቃሴ ይኖራል ብሎ መገመት አስቸጋሪ ነዉ። ቀደም ባለዉ ጊዜ በኢህአፓ ቀጥሎ በቀስተ ዳመና ቀጥሎ በቅንጂት ቀጥሎ በጂ7 ጎልተዉ የታዩ ተዋናይ ናቸዉ። እዚህ ላይ የዶ/ር ብርሀኑ ስም መነሳት ያስፈለገበት ዋናዉ ምክንያት አንድን ድርጅት መርተዉ ኢትዮጵያን ነጻ አዉጥተዉ መሪ ለመሆን በእንቀስቃሴ ላይ በመሆናቸዉ ተመሪዉ ህዝብ ስለኝህ ሰዉ አንስቶ መጠየቅ ፤መተቸት ፤ መመርመር፤ሀሳብ መስጠት እንዲችል ለመጋበዝ ነዉ።
ዶር ብርሀኑም የምእራቡን አለም ዲሞክራሲ በሚገባ በማወቃቸዉ ተመሪዉ ህዝብ መሪዉን ለመተቸት ሀሳብ ለመስጠት ሙሉ መብት እንዳለዉ በሚገባ እንደሚረዱም እገምታለሁ። እዚህ ላይ እያንዳንዳችን ወደ ስራ ስንቀጠር ስለ ግል ህይወታችን፤ ችሎታችን፤ለስራዉ ብቁ መሆናችንን ቀጣሪዎቻችን እንደሚገመግሙን ማለት ነዉ። አንድ ቁማርተኛ በክፉ ሱስ የተጠመደ፤ የቤተሰብን ዋጋ ክብር የማይሰጥ ወይም ሌላ አስነዋሪና አስከፊ ጸባዮችና ልምዶች ያሉበት ይህ ጸባዩ በተለያየ መልኩ ስራዉ ላይ ስለሚንጸባረቅ እንዲህ ያለ ግለሰብ ለትልቅ ስራ ቢታጭ ከልማቱ ይልቅ ጥፋቱ ስለሚያመዝን መሪዉን የሚመረጥ ዜጋ ያለፈ ታሪኩን የመመርመር ግዴታ ይኖርበታል ተብሎ ስለሚታመን ነዉ። (ለፍርድ የምትቸኩሉ አንባቢዎቼ እሳቸዉን ማለቴ አይደለም ምሳሌዉን ነዉ)።
ከላይ ለመግለጽ እንደሞከረኩት በያለንበት በምእራቡ አለም እንደምናዉቀዉ አንድ መሪ ለመሪነት ሲቀርብ ዜጎች የመምራት ብቃቱን በአስጨናቂ ጥያቄ ይገመግማሉ። ይህ መሪ ለኢኮኖሚ እድገት፤ የስራ አጥነትን ችግር ለማቃለል ፤ለልማት፤ ለማህበራዊ ፍትህ ምን መልስ አለዉ የሚለዉን ለመገምገም ሲሆን ከዚህ አለፍ ብሎም ድፍረቱና ሀገር አደጋ ላይ በወደቀችበት ጊዜ የጦር አዝማች ሁኖ ጦሩን ለድል ማብቃቱንም አብረዉ ይመለከታሉ። ይህንና ይህን የመሳሰለዉ ጥያቄ ለመሪዉ ቀርቦ መሪዉም ብቃቱን በሚሰጠዉ መልስ ባሳለፈባቸዉ ስራዎቹ ለህብረተሰቡ ባደረገዉ አስተዋጽኦ ተለክቶ መራጩ ህዝብ ድምጹን ይሰጠዋል።
እዚህ ላይ ከነገሬ ሳልወጣ ከጥንት ክፍለ ሀገራችን (ኤርትራ) ጋረ በተደረገዉ ጦርነት የጦሩ የበላይ አዛዥ መለስ ዘራዊ ጦሩን ለዉጊያ ልኮ ምንም ሳይረበሺ የተልእኮ ትምህርቱን ፈተና ለመቀበል በእርጋታ ያጠና እንደነበር የጊዜዉ አንጋቾቹ በሗላም ተወርዉረዉ የተጣሉት እነ አለምሰገድ በለቀቁት ጽሁፍ ላይ አንበበናል። በተመሳሳይ ሁኔታ ስታሊንግራድ መያዟ ነዉ ምን እናድርግ ብለዉ ለስታሊን ቴሌግራም ሲያደርጉለት እዛዉ በቆምክበት ምድር ለሀገርህ ሀዉልትህ ሁነህ ሙት እኔም ከአንተዉ ጋር አብሬ እሞታለሁ ብሎ ነበር ለጄነራሉ የመለሰለት። የሁለቱንም ዉጤት አንዱን ከታሪክ አንዱን በአይን ምስክርነት ታዝበናል። ለዚህ ነዉ ለመሪነት የሚመጡ ግለሰቦች የመሪነት ችሎታቸዉ ወደ ወምበሩ ከመድረሳቸዉ በፊት ይገምገም የሚባለዉ። ይህ ብቻ አይደለም በፖላንድ አምድ የስታሊን ልጅ እንደ ማንኛዉም ራሺያዊ ዜጋ በዛ ቀዉጢ ሰአት በመቶ አለቃ ማእረግነት ሀገሩን ለመከላከል የዜግነት ግዴታዉን ሲወጣ በጠላት እጅ ወድቆ ወታደራዊ ምዝገባ ሲካሄድ የስታሊን ልጅ መሆኑን ባለስፈላጊ ሁኔታ ከምረኮኞቹ አንዱ በመናገሩ ጀርመኖች እጃቸዉ የገባዉን አዱኛ በመደራደሪያነት በታሰሩት ጄነራሎች ሊለዉጡ ለስታሊን ከመደወል አልፈዉ ልጁንም በስልክ አገናኝተዉት ነበር። በቀዉጢ ሰአት የማዋጋትና የመምራት ብቃት ያለዉ ስታሊን ግን ደዋይ ጀርመኑ ጀነራል ላይ ስቆ ልጁን ግን ብትሞትም ለሀገርህ ነዉ የሞትከዉ ስምህ ግን አብሮህ አይሞትም ብሎ ነበር የመለሰለት። በዚህ ድርድር እንዳልሆነላቸዉ የተረዱት ጀርመኖች ግን የዚህን መሪ ልጂ ገደሉት ስታሊንም እምባዉን ወደ ዉስጥ ዉጦ ሀገሩን ከጀርመን ወራሪ አዳነ በስታሊንግራድ ዉጊያ የተገኘ ጀርመናዊም ሀገሩን በድጋሚ ሳያይ ቀረ። ይህን ምሳሌ ወደ ሀገራችን ገልብጠን ስናየዉ በዉን የህወአት መሪዎች ከዚህ የተቀራረበ ገድል ለኢትዮጵያ አይደለም ለትግራይ ይሰራሉ? ከተግባራቸዉ አንጻር ግን አይመስልም። ለዚህ ነዉ ለሀገር ዘላቂ ጥቅም የሚሰሩ ሀገር የሚወዱ መሪዎች ይመረጡ የሚባለዉ መሪነት የመድረክ ተዋናይነት ስላልሆነ።
ለጊዜዉ ከሞላ ጎደል የራዲዮ የድህረ ገጽ የቴሌቨዥን አገልግሎት የሚሰጠዉ ኢሳት የተባለዉ የሚዲያ ተቋም ሲሆን ዶር ብርሀኑም እዛ መድረክ ላይ ሲወጡ ጠያቂ እንጂ ተጠያቂ አይመስሉም። ሲሳይ አጌናና ሌሎች ኢሳቶች እንደ አቶ ተክሌ የሻዉ ፕሮፌሰር ጌታቸዉ ሐይሌን አይነቱንና ዶር ብርሀኑን የሚያዩበት አይን አንድ አይደለም ምንም እንኳን ሁሉም ኢትዮጵያዉያን ቢሆኑም። አርካይቭ ዉስጥ ስላለ የአባባሉን ተአማኒነት ጎልጉሎ ማየት ይቻላል። በእርግጥ ኢሳት ሙሉ በሙሉ በዶር ብርሀኑ ድርጅት ቁጥጥር ስር ቢሆንም ገንዘቡን የሚያዋጡት ግን የድርጅታቸዉ አባሎች ብቻ ሳይሆኑ ሌሎች ኢትዮጵያዉያንም በመሆናቸዉ ሚዛኑን የጠበቀ የሚዲያ አገልገሎት ሊሰጥ በተገባዉ ነበር።
ፕሮፌሰር ብርሀኑ ተጽፎ ካልተሰጣቸዉ በስተቀር ብዙ ጊዜ ንግግራቸዉ ለተች አጋልጦ ይሰጣቸዋል። አንባቢ እንደሚያስታዉሰዉ ከህወአት መጻፎች ዉጭ ለመጀመሪያ ጊዜ የተቆረጠች ኢትዮጵያን ያየነዉ በዶ/ር ብርሀኑ መጽሀፍ ነዉ ። አለፍ ሲሉ በስብሰባ ላይ በረከት ሰሞን ወዳጄ ነዉ፤ መለስ ዜናዊ የቅርቤ ሰዉ ነዉ ሲሉ ለአቶ ሰየ አብረሀና ወንድማቸዉ ደግሞ በጣም የሳሳ ልብ ያላቸዉ ከመሆኑም በላይ በጽሁፋቸዉም ላይ ደጋግመዉ የእነዚህን ሰዎች ስም ያነሱ ነበር። ሰየ አብረሀ ግን አዉቀዋለሁ ከማለት የዘለለ ነገር አለማለቱንና በረከት ሰምኦንም ባልተወለደ አንጀቱ በመጽሀፉ ላይ በክብረ ነክ አገላለጽ በሳቸዉ ላይ ከማላገጥ በስተቀር ብድራቸዉን ሳይከፍላቸዉ ቀርቷል።
የአማራን ጨቋኝ አባርሬ የትግሬን ጨቋኝ ላነግስ አልፈልግም ያሉት ዶር ብርሀኑ በድምሩ 40 ሚሊዮን ህዝብ ከማስቀየማቸዉም በላይ ማንን ይዘዉ ኢትዮጵያዊ ድርጅት እንደሚመሩም ለማወቅ አዳጋች ሁኗል። እዚህ ላይ አንባቢ እንደሚገነዘበዉ የኦሮሞ ብሄረተኞች የኦሮሞ ህዝብ በእጃችን ነዉ በሚሉበት ጊዜ ከአፋር፤ ጋሙጎፋ፤ባሌ፤ሱማሌ ጋር የቅርብ ግንኙነት የሌላቸዉ ዶር ብርሀኑ ማንን ይዘዉ የኢትዮጵያ መሪ ሊሆኑ እንደሚችሉ ለመረዳት አስቸጋሪ ነዉ። እንግዲህ እነዚህ የተገለጡት ብሄረሰቦች ሲቀነሱ ለዶ/ር ብርሀኑ የሚቀሯቸዉ አነድ 4 ሚሊዮን ህዝብ ቢሆን ነዉ እነሱም ሙሉ በሙሉ እሳቸዉን ይደግፋሉ ብዬ አልገምተም ምክንያቱም እሳቸዉ ያነጣጠሩበት ነገድ በኢትዮጵያ አንድነት ከማንም በላይ ተጠቃሚ እነደሆነ በሚገባ ስለሚታወቅ ነዉ። እንደ እዉነቱ ከሆነ አማራ ገዛ በሚሉበት ዘመን ተመችቷቸዉ የኖሩት ዶር ብርሀኑ በትግሬዉም ዘመን ከላይ በፎቶግራፉ እንደሚመለከተዉ ደስታ በደስታ ሁነዉ ለስልጣን ቀርበዉ በምከርም በምንም ሟቹ መለስ ዘራዊን ያገለገሉ ነበሩ። አንባቢ ከዛ ፈቶ ጀርባ ያለዉን ምስጢር መፍታት ግዴታዉ ነዉ እኔ ግን አባባሌን ይደግፋል ብዬ ለጥፌዋለሁ።
እንግዲህ ለኢሳት ስራ ማስኬጃ ግብጽ ይሄን ያህል ረዳ ሻቢያ ይህን ያህል ረዳ የሚለዉን የጂ7ን የዉስጥ አሰራር ትተን በዚህ ዶር ብርሀኑ አዛዥና ናዛዥ በሆኑበት ኢሳት ከአንድነት ይልቅ ልዩነት፤ ከጥንቱ ከሚያኮራ ታሪካችን ይልቅ አዲስ ታሪክ ፍለጋ የምንኳትንበት፤ ኢትዮጵያዊነትን የሚያቀነቅኑ እንደ ጠላት የሚታዩበት፤ ኢትዮጵያዉያን አይደለንም የሚሉ የኢትዮጵያ ጠላቶች ትልቅ መድረክ ተሰጧቸዉ በትልቅ ክብር ኢትዮጵያንና አንድነቷን የሚያራክሱበት፤ የሚያዋርዱበት መድረክ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ በዶር ብርሀኑ/ነአምን ዘለቀ እንደሚመራ አንባቢ በሚገባ ይረዳዋል ብዬ እገምታለሁ። በዚህ ኢሳት በተባለዉ መድረክ በስህተት ኢትዮጵያዊ መንፈስ ያላቸዉ ወገኖች ሲጋበዙ ጥያቄዉ የፖሊስ ምርመራ አይነት ሲሆን ወከባዉና ክብረ ነክ አቀራረቡ መሀከለኛ እድሜን ላለፈ ኢትዮጵያዊ የሚመች አይሆንም። ሆኖም ዶር ብርሀኑ ይህንን እያዩ እርምት ሊወስዱ ባለመሞከራቸዉ እኝህ ሰዉ ወዴት እየሄዱ ነዉ ምንስ አስበዉ ነዉ ብሉ መጠየቅ ግድ ይላል።
ኢሳትና በቀጣይነት ከረንት አፌየርስ የተባለዉ የፓልቶክ (የኮምፒተር) መወያያ መድረክ የዶር ብርሀኑ ድርጂት አቀንቃኞች፤ሻቢያኖች በስድብ ሰናይፐር የሰለጠኑ አባሎቻቸዉን በማሰማራት ኢትዮጵያዊነትን የሚያንሸራሸሩ ወገኖችን ባልተወለደ አንጀት የሚያዋርዱበት መድረክ ሁኖ ሳለ ዶር ብርሀኑ ጊዜ ሲኖራቸዉ እየገቡ የሚስቁበት መድረክ ነዉ ብዬም እገምታለሁ። በዚህ መጠነ ሰፊ ዘለፋ በዚህ ኢትዮጵያዊ ባልሆነ የዉይይት ስልት ዘለፋዉ በእጅጉ የበዛባቸዉ የቀድሞ የቅንጂት አንጋፋዎች ስድቡን አስቁሙሉን ብለዉ በእንባ ቀረሺ ልመና ቢማጠኑም ሰሚ ጠፍቶ ክፍሉ እራሱ በራሱ መክኖ ዛሬ ተሳዳቢዎችም አደብ ገዝተዉ በስራቸዉ አፍረዉ ጥግ ጥግ ይዘዉ ቁመዋል። መቼም ጽናጽል ከጽናጽል ዉጭ ምንም ሊሆን አይችልምና፡፤
እንግዲህ ከዚህ በላይ ያለቸዉን በዚህ መልኩ ካስቀመጥኩ በሗላ ፓርቲያቸዉ በለስ ቀንቶት የወደፊት የኢትዮጵያ ጠ/ሚኒስተር ዶ/ር ብርሀኑ አዲሱ እምነታቸዉ ኢትዮጵያን ከሻቢያ ጋር በመሆን ነጻ እናወጣለን የሚል መሆኑ ከማንም የተሰወረ ካለመሆኑም በላይ አንጋቾቻዉም ደረታቸዉን ሰጥተዉ በአጽንኦት ያለ እፍረት ይህንን ሀሳባቸዉን ያጠናክራሉ። ብዙ ወገኖች አረ ይህን ነገር ቆም ብለን እናስብበት እኛም ያገባናል በሻቢያና በህወአት መሀከል ልዩነት የለም ቢባሉም በከረንት አፌየርስና ኢሳትን በመሳሰሉት የዶር ብርሀኑን እምነት በሚያራግቡ የሚዲያ ተቋማት ሀሳብ ለመስጠት ሲሞከር በረቀቀ የዘለፋ ስልታቸዉ አንተ ወያኔ ነህ በሚል ማስደንገጫ ኢትዮጵያዉያኑን ጥግ ሊያስይዙ ይሞክራሉ። እንደዉም በኢሳትም ሆነ በነዚህ የፓልቶክ መወያያዎች ሻቢያኖቹ የጎላ ቦታ ተሰጥቷቸዉ የአንድነት ሐይሉን ያንገላታሉ።
በኢትዮጵያዉያኑ አካባቢ እየተለመደ የመጣዉ በዳይን ከወዳጂ በተሻለ መልኩ የመንከባከብ ባህል ማዳበር ነዉ። ዶ/ር ብርሀኑ ፤አንዳርጋቸዉ ጽጌ፤ ኤርምያሰ ዋቅጂራ ፤ ተስፋዬ ገ/አብ ፤ሰየ አብረሃ፤አረጋዊ በርሄ፤ገብሩ አስራት…….ከህወአት ጋር በጣም የቀረበ ትሰስር ያላቸዉና አንጋፋዎቹም ምስረታዉ ላይ የመሰረት ድንጋይ የተከሉ መሆናቸዉ እየታወቀ ዛሬም አዋቂ እንደጠፋ ሁሉ ወደ ኢትዮጵያን መንደር ብቅ ብለዉ ነገርን ያሳክራሉ ትግሉም ኢትዮጵያዊ መልክ እንዳይዝ በረቀቀ ልምዳቸዉ ያወነባብዳሉ ። የመጣዉን መንግስትም በአማካሪነት ያገለገሉ በቃችሁ ሳይባሉ ቀርተዉ ዛሬም ነገር ያደፈርሳሉ። ለዚህ ነዉ መሪዎችን የፖለቲካ ሰዎችን ከማምለካችን በፊት የቀድሞ ህይወታቸዉን በትኖ ማወቅ ያስፈለገበት ምክንያት ። ዉሳኔያቸዉ የቤተሰብ ዉሳኔ ሳይሆን ህዝባዊ ነዉ የሚያደርሱት ጥፋት የብዙ ሚሊዮን ህዝቦችን ህይወት ይነካል። በጫት እና በመጠጥ የነበዘ መለሰ ዜናዊ እና ለመሪነት ብቃት የሌላቸዉ የህወአት መሪዎች ወደብን ያህል ነገር አሳልፈዉ ሲሰጡ ምን እንደሆነ እንኳን በቅጡ አልመረመሩትም ዛሬ የኢትዮጵያ ገበሬና ነጋዴ አርሶና ነግዶ ጥረቱን ለጂቡቲ ይሰጣል። ኢትዮጵያን የሚያክል ትልቅ አገር ዛሬ ለጂቡት ማጎብደድ ግዴታ ሁኖበታል አንዴ ዉሀ ላቅርብ አንዴ ለም መሬት ዉሰዱ እየተባሉ ይስተናገዳሉ። እንግዲህ ለዚህ ነዉ መሪዎቻችንን ማንነታቸዉን መርምረን መረዳት የሚያስፈልገን። ህወአት በስብሰባዉ አፈጮሌ ቀጣፊ ባይመረጥ ኑሮ ዛሬ ቢያንስ አሰብ እና 70000 ኢትዮጵያዊ የተቀጠፋባቸዉ መሬቶች ለኢትዮጵያ ሁነዉ ይቀሩ ነበር። ዶ/ር ብርሀኑንም ከዚህ ማእዘን ማየት እንደፈለግሁ አንባቢ ይረዳልኝ።
እንግዲህ ከላይ የተመለከተዉን ብዙ የሚናገረዉን የዶር ብርሀኑን ፎቶ አንባቢ ዉስጣዊ ሰሜታቸዉንና ይፋ ባልሆነ በስልጣን ተዋረድ ከታምራት ላይኔ በላይ ለመለስ ዘራዊ ቀረቤታም እንደላቸዉ ታሳብቃለች ብዬ እገምታለሁ። የዩኒቨርስቲ መምህራኖችም የሕወአት ስራ አገር ማጥፋት መሆኑን ተረድተዉ ስራ ሲያቆሙም ዶር ብርሀኑ ክፍተቱን ሞልተዉ መስራታቸዉ የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነዉ ለዚህ ነዉ የመሪዎች ያለፈ ታሪካቸዉ በሚገባ መገምገም ያስፈለገበት።
ዛሬ ኢትዮጵያ በሻቢያ አማካይነት ነጻ ትሆናለች በሚል በከፍተኛ ፖለቲካዊ ክንድ ጠምዝዝ ቅስቀሳ ወገኖች ወደ ኤርትራ እየሄዱ ደብዛቸዉ ጠፍቶብናል። ቀደም ባለዉ ጊዜ ጋዜጠኛ ደምስ ከብዙ በጥቂቱ ሁኔታዉ ተጋልጦ እርምት እንዲወሰድበት ቢጠይቅ የእሩምታ ተኩሰ ከየአቅጣጫዉ ተከፍቶበት መድረክም ተከልክሎ ሳይወድ በግድ የወያኔን እምነት አራማጂ ለሆነዉ ለብርሀኑ ዳምጤ ቀርቦ ተከታይ ሀሳቡን ማሰማቱን የኢትዮጵያን ጉዳይ የሚከታተል ወገኔ አስደምጦኛል ኢሳት በሩን ክፍት ቢያደርግለት ስንት ጉድ እንሰማ ነበር።
ወይ ዉርደት 100 ሚሊዮን ህዝብ ያላት ኢተዮጵያ ሀገርነቷ ባልተረጋገጠዉ ክፍለ ሀገራችን መጫወቻ ትሁን? ዉርደት ከዚህ በላይ የታለ? ደጃዝማች አፈወርቅ፤ጸሐፊ ትእዛዝ አክሊሉ ሐብተወልድ/አብዲሳ አጋ/ገበየሁ ባልቻ/በላይ ዘለቀ /በላይ ቃለ አብ፤ኡመር ሰመታን፤ዘርአይ ደረስ ይህን ሳታዩ ሞታችሁ እድለኞች ናችሁ። የኢትዮጵያ ወታደር በሱማሌ ሲገደል ከረንት አፌርስ ና ኢሳት ርችት ይተኩሱ ነበር አይ ዜጋ አይ ትምህርት። በዉን ተራ ወታደሩ የኢትዮጵያ ህዝብ ትግሬ ነዉ?፡በዉን ተራ ወታደሩ ወያኔን ሊጠብቅ ነዉ የተቀጠረዉ? እናንተ ምንም ሳታጡ ባንዳ ሁናችሗል እሱ ግን የሚበላዉ አጥቶ ባንዳ ቢሆን ምኑ ይገርማል?
ዶ/ር ብርሀኑ ከኤርትራዉ አስተደደር ያላቸዉ ግንኙነት የበታችና የበላይ ካልሆነና የወዳጂ መንግስት ከሆነ እንደሳቸዉ ቀደም ባለዉ ጊዜ በሀይል ከኤርትራ በመወንጨፍ ኢትዮጵያን ነጻ እናወጣለን ብለዉ ኤርትራ የተጠለሉ ብዙ ወገኖቻችን በእስር በእንግልት ላይ የሚገኙ መሆናቸዉን አምነስቲ ኢንተርኛሽናልና ወጣ ገባ የሚሉ ወገኖች ነግረዉናል። ከነዚህም መሀል ስመ ጥሩዉ ኮለኔል ታደሰና ወጣቱ የቢቢሲ ጋዜጠኛ ዮሴፍ ይገኙበታል። እንግዲህ ፕሮፌሰር ብርሀኑና ነአምን ዘለቀ የኤርትራ መንግስት ወዳጃቸዉ ከሆነ የኤርትራ መንግስተ በፍቃዳቸዉ ወደ ሀገሩ የገቡትን ዜጎቻችን አስፈትተዉ ነጻነታቸዉን ወደሚያገኙበት ሀገር እንዲያሰናብቱልን በኢትዮጵያዉያን ስም ጥያቄዬን አቀርባለሁ።
ቀደም ባለዉ ጊዜ አቶ ሌንጮ ይመስለኛል የጠላት አገር ወደሚለዉ ኢትዮጵያ የድርጅቱ አባል ታስሮበት ሰተት ብሎ ገብቶ አስለቅቆ እንደተመለሰ አንድ ጽሁፍ ላይ ተጽፎ አይቻለሁ። እንግዲህ ሌንጮ ከጠላት መንግስት ይህን ካደረገ ለዶር ብርሀኑ ከወዳጂ መንግስት በችግር ላይ የወደቁ ወገኖቻችንን ማስለቀቅ ይከብዳቸዋል ብዬ አልገምትም። ፖለቲካ ተለዋዋጭ ነዉ አቶ አንዳርጋቸዉ የህወአት ባትሪ አብሪ ነበሩ ነገር ተለዉጦ ዛሬ በሚያስሩበት እስር ቤት ታስረዋል፡ ነገር ግን ባለንበት አገር አቶ አንዳርጋቸዉ ይፈቱ በማለት የምንችለዉን ሁሉ ያለእረፍት በማድረግ ላይ ነን። ይህ ስህተት ካልሆነ እርሶም በዛ የታሰሩብንን ወገኖች የማስፋታት የዜግነትና የመሪነት ግዴታ ይኖርቦታል ብዬ እገምታለሁ። እዚህ ላይ ቀደም ብዬ እንደገለጽኩት ትላንት ኮለኔል ታደሰና መሰሎቹ ላይ የደረሰዉ በእርሶም ላይ የማይደርስበት ሁኔታ አይኖርም ብዬ እገምታለሁ። ዛሬ ለነሱ የተጨነቅን ሰዎች ለደረሰቦት ችግር ልንደርስ የምንችለዉ እርሶ ለኮለኔል ታደሰና በኤርትራ በእንግልት ላይ ለሚኖሩ ወገኖቻችነን በሚያደረጉት አስተዋጽኦ ልክ መሆኑን በአጽንኦት ማስገንዘብ እንወዳለን። ወደ ኤርትራ ምቾታቸዉን ትተዉ የሄዱ ወገኖች በሙሉ በሀገር ፍቅር ስሜት ተንገብግበዉ ኢትዮጵያን ኢትዮጵያ ለማድረግ በመሆኑ ዛሬ እኛ ባለንበት ሀገር ባንታሰርም ልባችን ከነሱ ጋር መታሰሩን ሊያዉቁልን ይገባል ብዬ እገምታለሁ። በዚያ በእንግልት የሚገኙ ወገኖቾን እያዩ እንዳላዩ አልፈዉ ኢትዮጵያን ነጻ አወጣለሁ የሚል አባባል ዉሀ ስለማይቋጥር ካሁን በሗላ ወደ መድረክ ሲቀርቡልን ይዣቸዉ መጣሁ የሚለዉን መልካም ዜና እንጂ ሌላዉን መስማት እንደማንፈልግ እንዲረዱልን እንጠይቃለን።
ለዚህ ጥያቄዎ የኤርትራ መንግስት መልስ ሊሰጥ የማይችል ከሆነ ዉሳኔዎን እንደገና በጥንቃቄ ይመርምሩ እላለሁ። ነገር ባላሰብኩት መንገድ ሂዶ ልዩ ትርጉም ከተሰጠዉ ይቅርታ ከማለት ሌላ ምን ይበላል ቢያንስ ሰዉ አልሞተም ሀሳብ ተንሻፍፎ ሊሆን ይችላል ይሰተካከላል። ለአስተያየት በዚህ ድረሱኝ semere.alemu@yahoo.com
በቸር ይግጠመን
ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር

No comments:

Post a Comment