Monday, May 23, 2016

በርካታ የኢትዮጵያ ቡና ደጋፊዎች በጎንደር ጉዳት ደረሰባቸው

በዳዊት ፀሀዬ |ግንቦት 15 ፣ 2008
በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ከተካሄዱ ጨዋታዎች መካከል አንዱ በጎንደሩ አፄ ፋሲለደስ ስታዲየም የወራጅነት ስጋት የተጋረጠበትን ዳሽን ቢራን በሁለተኛው ዙር ጥሩ ግስጋሴ እያደረገ ከሚገኘው ኢትዮጲያ ቡና ያገናኘው እና ሁለት አቻ የተጠናቀቀው ጨዋታ ይጠቀሳል፡፡
ከጨዋታ በፌት ቅዳሜ ክለቡ ባመቻቸው 3 አውቶብሶች እና በግላቸው በርከት ያለ ደጋፊዎች ወደ ስፍራው ማቅናታቸው ይታወሳል፤ በስፍራው ሲደርሱም በጎንደር ተቀማጭነቱን ባደረገው እና ከኢትዮጵያ ቡና ጋር በቅርበት የሚሰራው እና የዳሽን ቢራ ዋንኛ የከተማ ተቀናቃኙ  የፋሲል ከተማ ደጋፊዎች አድካሚ ጉዞ ለተጓዙት የቡና ደጋፊዎች አቀባበል ማድረጋቸውም እንዲሁ፡፡
ጨዋታው በተያዘለት መርሃግብር መሠረት በተሟሟቀ የተመልካች ድጋፍ መካሄዱን ጀመረ የመጀመሪያው አጋማሽ  ኦዶም ሆሶሮቪ እና ሳዲቅ ሴቾ ለክለቦቻቸው ባስቆጠሯቸው ግቦች የመጀመሪያ አጋማሽ አንድ አቻ በሆነ ውጤት ሊጠናቀቅ ቻለ፡፡
በሁለተኛው አጋማሽ ጅማሮ በ49ኛው ደቂቃ ይተሻ ግዛው ባለሜዳዎቹን ቀዳሚ አደረገ በዚህች ግብ መነቃቃት የተሰማቸው የዳሽን ደጋፊዎች በከፍተኛ ሞራል ቡድናቸውን ማበረታታ ጀምሩ፡፡
ከዚህ በኃላ ነበር ኢትዮጲያ ቡና የአቻነቷን ግብ ለማግኘት በአንፃሩ ዳሽኖች ደግሞ ውጤቱን ለማስጠበቅ እልህ አስጨራሽ ትግል ማድረግ የጀመሩት፡፡
በ62ተኛው ደቂቃ ላይ ግን የጨዋታውን መንፈስ የቀየረ አጋጣሚ ተከሰተ የኢትዮ አዲስ ስፖርት ምንጮች ስለሆኒታው ሲያስረዱ ሳዲቅ ሴቾ ኳስዋን ሲያስቆጥር ከጨዋታ ውጪ የነበረ አቋቋም ውስጥ ነበር በሚል የዳሽን ተጫዋቾች በተለይም በ39 ኛው ደቂቃ ላይ አስራት መገርሳን ተክቶ የገባው ሳሙኤል አለባቸው(ግቻው) የመስመር ዳኛውን ማዋከብ ጀመሮ ፤ ጨዋታውን በመሀል ዳኝነት ሲመራ የነበረው አልቢትር ዘካሪያስ ጉዳዮን ለማረጋጋት ወደ ስፍራው ባቀኑበት ወቅት በሆኒታው በተበሳጩ የዳሽን ደጋፊዎች በተወረወረ ቁሳቁስ ጭንቅላታቸውን የተመቱት፡፡
በዚህም የመሀል ዳኛው በህክምና ባለሙያዎች ህክምና ከተደረገላቸው በኃላ በደም የተለወሰውን መለያቸውን በሌላ ቀይረው ጨዋታው ጭንቅላታቸውን በፋሻ ተቅልለው ለመጨረስ ተገደው ነበር፡፡
ከጨዋታው መጠናቀቅ በኃላ ነበር ከፋሲል ከነማ ደጋፊዎች ጋር ተቀላቅለው ሲጨፍሩ የነበሩ የኢትዮጵያ ቡና  ደጋፊዎች ላይ የዳሽን ቢራ ደጋፊዎች ድንጋይ መወርወር የጀመሩት በዚህም የኢትዮጵያ ቡና ደጋፊዎች አጥር ንደው ወደ መጫወቻ ሜዳ በመግባት ለማምለጥ ጥረት አድርገዋል ሆኖም ጥቂት የማይባሉ የተቃራኒ ደጋፊዎች በተቃራኒ ያለውን ጥሰው ጥቃት ለማድረስ ሞክረዋል፡፡
በዚህም መሠረት ጥቂት የማይባሉ የኢትዮጵያ ቡና ደጋፊዎች ከከፍተኛ እስከ ቀላል ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡
ማምሻውንም በርካታ ቁጥር ያለው የኢትዮጵያ ቡና ደጋፊ ጎንደርን ለቆ ማደርያውን በባህርዳር ማድረጉን ማረጋገጥ ችለናል፡፡
በመጨረሻም ገና እንደ ህፃን ልጅ እየዳኸ በሚገኘው እግርኳሳችን ላይ ጭራሽ የዚህ አይነቱ አሳፋሪ እና አስነዋሪ ድርጊት ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በስፋት እየተስተዋለ መምጣቱ ለእግርኳሳችን እድገት አይበጅም እና ሁላችንም ባለድርሻ አካላት ተረባርበን መፍትሔ ልናበጅለት ይገባል መልእክታችን ነው፡፡

No comments:

Post a Comment