Friday, October 27, 2017

ትናንት በአምቦ የተገደሉት ሰዎች ቀብራቸው ዛሬ ይፈጸማል። ከሟቾቹ መካከል የ13 ዓመት ልጅ ይገኝበታል ተብሏል


By ሳተናውOctober 27, 2017 05:56

 
አምቦ ውስጥ ስኳር የጫኑ መኪናዎች እንዳያልፉ ተዝግቶ የነበረውን መንገድ ለማስከፈት የፀጥታ ኃይሎች በወሰዱት እርምጃ ሰዎች ሞተዋል።
ዛሬ ከአምቦ ሆሰፒታል የሜዲካል ዳይሬክተር ተወካይ የሆኑት ዶ/ር ቶኩማ ክፍሌ እንደነገሩን፤ ትላንት በነበረው ግጭት ስድስት ሰዎች ህይወታቸው አልፎ ሆሰፒታል እንደደረሱ እና ሌሎች ሁለት ሰዎች ደግሞ ሆስፒታል ከመጡ በኋላ ህይወታቸው እንዳለፈ አረጋግጠዋል።
ዶ/ር ቶኩማ እንዳሉት ህይወታቸው አልፎ ከመጡት እና በሆስፒታሉ ከሞቱት መካከል ሁለቱ ሴቶች ናቸው።
”የሁሉንም ሟቾች አስክሬን ማየት ባልችልም፤ ከተመለከትኳቸው አስክሬኖች እና ከባልደረቦቼ እንደሰማሁት ሁሉም የሞቱት በጥይት ተመትተው ነው። ከሟቾቹ መካከል ጭንቅላታቸውን የተመቱ ሲኖሩ፤ ሆዱን የተመታና ኦፕሬሽን ክፍል ደርሶ ብዙ ደም በመፍሰሱ የሞተም አለ” ብለዋል።
ዶክትር ቶኩማ ጨምረውም አብዛኛዎቹ ሟቾች እድሜያቸው በ20ዎቹ ውስጥ የሚገኙ ወጣቶች ናቸው። ሆስፒታል ደርሰው ከሞቱት መካከል አንደኛዋ ሴት ስትሆን እድሜዋ በግምት 16 ወይም 17 ሊሆን እነደሚችል ተናግረዋል።
ከትላንት ጀምሮ ህክምና ተደርጎላቸው እየተመለሱ ያሉ ሰዎች እንዳሉ የሚናገሩት ዶ/ር ቶኩማ አሁን በሆስፒታሉ ከአስር ያላነሱ ሰዎች የተለያየ ጉዳት ደርሶባቸው ህክምና እየተደረገላቸው እንደሆነ ገልፀዋል።
ከእነዚህም መካከል በጽኑ የተጎዱ እንዲሁም ለህይወት የማያሰጋ ከባድ የአካል ጉዳት የደረሰባቸውም እንዳሉ ዶክተር ቶኩማ ተናግረዋል።


የአምቦ ከተማ የኮሚኒኬሽን ቢሮ ሃላፊ የሆኑት አቶ ጋዲሳ ደሳለኝ በከተማዋ ብዙ እንቅስቃሴ ባይታይም ከትላንቱ አንፃር ከተማዋ ስላም እንደሆነች ገልፀዋል።
ትናንት የተገደሉት የአብዛኞቹ ሰዎች ቀብር ዛሬ ስለሚፈፀም፤ ከቀብር ጋር ተያይዞ የፀጥታ ችግር እንዳይፈጠር የሃገር ሽማግሌዎች ከቀብር በኋላ ወጣቱ ወደ ቤቱ እንዲመለስ እያሳሰቡ ናቸው ብለዋል።
የምዕራብ ሸዋ ዞን የፀጥታ እና አስተዳደር ቢሮ ሃላፊ የሆኑት አቶ ጌታቸው ኩምሳ ደግሞ፤ ”የሟቾችን ማንነት፣ በማን እና በምን አይነት ሁኔታ እንደተገደሉ እየተጣራ ነው። እሰካሁን ባለን መረጃ ግን ከሟቾቹ መካከል ሦስት ሴቶች እና የ13 ዓመት ልጅ ይገኙበታል” ብለዋል።
አቶ ጌታቸው እንደሚሉት በአምቦ ስኳር ከጫኑ መኪኖች ጋር ተያይዞ የነበረው ግጭት ከሦስት እና ከአራት ቀናት በላይ አስቆጥሯል።
”ይህን ችግር ለመፍታት የክልሉ ፖሊስ እና የሃገር ሽማግሌዎች ወጣቶችን ለማወያያት ጥረት እያደረጉ ነበር። በዚህም መልካም ለውጦችን እየተመለከትን ነበር። ትናንት ተጨማሪ ኃይል ወደዚህ ከመጣ በኋላ ግን ይህ ሁሉ ችግር ተፈጠረ” ሲሉ ያስረዳሉ።
የኮሚኒኬሽን ቢሮ ሃላፊው አቶ ጋዲሳ ደሳለኝ እንዳሉት እስካሁን ባላቸው የተጣራ መረጃ ስምንት ሰዎች በትናንቱ ግጭት ሞተዋል ብለዋል።

No comments:

Post a Comment