Wednesday, September 20, 2017

የመለስ እርኩስ መንፈስ

ኃይሉ ማሞ


  
By ሳተናውSeptember 20, 2017 15:39


 

አቶ መለስ ዜናዊ የሞተበት 5ኛ ዓመትን አስመልክቶ ደጋፊዎቹ ውርሱን እንዘክራለን በሚል ባገኙት መገናኛ መንገድ ሁሉ ቅዱስነቱን ሲሰብኩ እየታዘብን ከርመናል። ይህን ጊዜም በትዝብት አለፍ ስንል ሁሌም የመለስ ምናምን ከማለት ወጥተው በራሳቸው እንደሰው መቆም የማይችሉት ስንኩላን የስርዐቱ ስብስቦች ልክ መለስ ዜናዊ ባንዲራ ጨርቅ ነው ባለበት አፉ የባንዲራ ቀን የሚል ከበሮ እንደደለቀው ሁሉ፣ በህገመንግስቱ ሳይቀር የኢትዮጵያ መሰረት ኢትዮጵያዊ ዜግነት ሳይሆን የብሄር ጥርቅም ነው እንዳላሉ የ2010 ዓ/ም ዘመን መለወጫን አስመልክቶ የከፍታ ቀን፣ የሀገር ፍቅር ቀን ወዘተ የሚሉ የካድሬ ጥሩንባዎችን እየሰማን አዲስ ዓመቱን ተቀበልን። ከካድሬው ጥሩንባ ባሻገር ያለው እውነት ግን የስርዓቱ የአፈና ተግባር ተባብሶ እንደሚቀጥል የተረጋገጠበት፣ የሀገር ፍቅሩ ቀርቶ ኢትዮጵያ ተብሎ ስሟ ሲጠራ ዘረኞቹ እስከስረኛው አንጀታቸው የሚታመሙ መሆኑን የቴዲ አፍሮ ኮንሰርትና አልበም ምረቃ ዝግጅቶች መታገድ ቀጣዩንም የጨለማ ጊዜ ነጭና ጥቀር በሆነ መልኩ ቁልጭ አድርጎ ያሳየ ነበር። የኢትዮጵያ 2010 መባቻ ከመቸውም ጊዜ በበለጠ የመለስ እርኩስ መንፈስ ግዘፍ ነስቶ የታየበትም ነው። ህወሀት በሰሜን አማራና ቅማንት በማለት በህዝቦች መካከል የጥላቻና የመነጣጠል ዘር ለመዝራት ሲዳክር በደቡብ ምስራቁ የሀገራችን ክፍል ደግሞ የዘር ካባን በለበሰ ሽፋን ልዩ ኃይል በተሰኘ የህወሀት ልዩ የግድያ ቡድን አማካይነት የኦሮሞን ህዝብ ሲጨፈጭፉ ከርመዋል። በደቡብም በአማሮ ኬሌ፣ በጉጂና በቡርጂ ህዝቦች መካከል የተለኮሰው እሳት አካባቢውን ሲያጋይና የህዝቡ ውሎ አዳር የፍርሀትና የስጋት ደመና ያንዣበበት እንደሆነ እስካሁንም ቀጥሏል። የመሀል ሀገሩ ህዝብም በገቢ ትመና ሰበብ ለዘረፋ ተዳርጎ ድኃው የእለት ጉርሱን ቃርሞ ማደር ያልቻለበት፣ አቤት የሚልበት ያጣበት የሰቆቃ ድምጾች ከየቦታው የሚሰሙበት ወቅት እንደሆነ 2010 ተንደረደረ። እናም የተቀበልነው አዲስ ዓመት ካድሬው የወደቀ ፕሮፓጋንዳውን ሲያንቋርር የህዝቡ ለቅሶ ደግሞ ህዋውን አልፎ ሰማየ ሰማያት የዘለቀበት ነው።
በርካታ ስብሰባዎች በሚደረጉበት ወቅት የሀገሪቱ መጪ ጊዜ ከልብ የሚያስፈራቸው ሙሁራን የሚያነሱት ግን እንደዋዛ እየተሰማ የሚታለፍ ነጥብ አለ። ኢትዮጵያ በህወሀት እጅ ውስጥ በቆየች ቁጥር የሚገጥመን አደጋ የከፋ ከመሆን አልፎ እስከወዲያኛው ሀገር ሊያሳጣን እንደሚችል ተደጋግሞ ተወስቷል። የኢትዮጵያን ውሎ አዳር በቅርበት የተከታተለና የህወሀትን አመጣጥ ብሎም ስልጣን ላይ ለመቆየት የተመሰረተባቸውን ምሶሶዎች ለተገነዘበ ይህ ስርዓት የሀገራችን መጥፊያ መሆኑን ለመረዳት ደቂቃዎችን የሚፈጅ ጊዜም አይፈጅበትም። ህወሀትና የህወሀት ቅልቦች የመለስን እርኩስ መንፈስ ተሸክመው በዚሁ እርኩስ መንፈስ ሀገሪቱን እያመሷት ዛሬ ላይ ደርሰዋል። ኢትዮጵያም በዚህ እርኩስ መንፈስ የምትቃትት ሀገር፣ ህዝቧም በእርኩስ መንፈሱ የሚሸበር ሆኖ እየመሸ ይነጋል፥ እየነጋ ይመሻል።
ሁሉንም የመለስ የእርኩስ መንፈስ ውርሶች ዘርዝሮ መጨረስ ባይቻልም አንኳር የሆኑት መጠቃቀሱ ግን ከላይ ለተንደረደርንበት ሀሳብ አጋዥ ይሆናልና ጥቂት እንጠቃቅስ።

No comments:

Post a Comment