Saturday, September 23, 2017

ጎሳን መሰረት ያደረገው ፌዴራሊዝም በኢትዮጵያ እልቂት እያባባሰ ነው ተባለ – በወንድወሰን ተክሉ


By ሳተናውSeptember 23, 2017 08:49



በኢትዮጵያ ያለው ፌዴራሊዝም በዘር/ጎሳ/ ላይ የተመሰረተ በመሆኑ በህዝቦች መካከል እልቂት እየፈጠረና ሀገሪታንም ወደ አላስፈለገ የእርሰ በርስ ጦርነት እየወሳዳት ነው ሲሉ ሁለት የኢትዮጵያ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በጋራ የአቃም መግለጫ የሰጡ ሲሆን በምስራቁ የሀገሪቱ ክፍል ለተፈጠረው እልቂት የመንግስት ቸልተኝነት፣ዳተኝነትና ግድየለሽነት ውጤት ነው ሲሉም ተጠያቂው መንግስት ነው ሲሉ ገልጸዋል።
የመላ ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት[መኢአድ]እና የሰማያዊ ፓርቲ ድርጅት በጋራ ባወጡት መግለጫ በምስራቁ የኢትዮጵያ ክፍል በኦሮሚያና ሶማሌ ክልሎች መካከል በተፈጠረ የወሰን ግጭት በመቶዎች ለሚቆጠሩ ንጹሃን ህይወት መጥፋትና በአስር ሺህዎች ለሚቆጠሩ ዜጎች መፈናቀል ምክንያት የሆነው የስርዓቱ ጎሳን/ዘርን መሰረት ያደረገው ፌዴራሊዝም መሆኑን ጠቅሰው ለደረሰው ውድመትና እልቂት ተጠያቂው በስልጣን ላይ ያለው መንግስት በጉዳዩ ላይ አግባብ የሆነ ፈጣን እርምጃ ባለመውሰዱ ምክንያት የተፈጠረ በመሆኑ ተጠያቂ ነው ሲሉ ገልጸዋል።
እንደ ሁለቱ ድርጅቶች እምነት በአዋጅ ስልጣን የተሰጠው የመከላከያ ሰራዊት መንግስታዊ ትእዛዝ ሳይጠብቅ ግጭቱን ማስቆም ይቻለው ነበር ካሉ በሃላ የመንግስት ዳተኝነትና ቸልተኝነት በሁለቱም በኩል ለጠፋው የሰው ህይወትና በአስር ሺህ ለሚቆጠሩት መፈናቀል ምክንያት ሆናል በማለት መንግስትን ሃላፊነቱን ባለመወጣት ተጠያቂ አድርገዋል።
ለሁለት ሳምንታት በዘለቀው የኦሮሚያና የሶማሊያ ክልሎች ግጭት ከሁለቱም ወገን ከመቶ በላይ ንጹሃን መገደላቸው እና ከ75ሺህ በላይ መፈናቀላቸው ቢታወቅም በመንግስት በኩል የማቾቹን ቁጥር እስከዛሬ የማወቅ ችግር እንዳለ በመግለጽ የማይገልጸው ሲሆን ስለተፈናቃዩቹም የፌዴራሉ መንግስት ወደ 10ሺህ የሚደርሱ ሲል የኦሮሚያ ክልላዊ መስተዳድር ደግሞ ከ60ሺህ በላይ እያለ መግለጹ ይታወቃል፡፣
ጎሳን መሰረት ያደረገው ፌዴራሊዝም ለተከሰተው የጎሳ ግጭት መንስኤ መሆኑን የሚገልጹት ሁለቱ ድርጅቶች ኢትዮጵያ ዛሬ ወንድማማቾች እርሰበርስ የሚገዳደሉባት ሀገር ሆናለች በማለት ፖሊሲውን ሲያወግዙ መንግስት ደግሞ ችግሩ ከፌዴራሊዝም ሳይሆን በስሩ በታቀፉት ጠባብና ትምክህተኛ አመለካከት ባላቸው ያለፈ ስርዓት አቀንቃኞች ምክንያት ነው ሲል ይናገራል።
በኢትዮጵያ ውስጥ የማንነት ጥያቄንም ሆነ የመልካም አስተዳደር ጥያቄን የሚያነሱትን መንግስት “ጠባብ፣ትምክህተኞች፣ያለፈ ስርዓት አራማጆች፣አሸባሪና የግብጽና ሻእቢያ ተላላኪዎች”በሚል ስያሜ እየፈረጀ በጉዳዩ ላይ አባባሽ ድርጊቶችን ከማድረግ ይልቅ የቀረበለትን ህዝባዊ ጥያቄን በአግባቡ በመመለስ ግጭቶችን ሲከላከል አይታይም።
የመኢአድና የሰማያዊ ፓርቲ ድርጅቶች ከሶማሌ ክልል ተፈናቅለው በሐረር እስታዲየም የተጠለሉትን ወገኖች በተለይም ሴቶችን እና ህጻናትን ለመርዳት ድጋፍ አሰባሳቢ ግብረ ሃይል ማቃቃማቸውን ገልጸው መንግስት ለሞቱት ዜጎች ብሒራዊ የሀዘን ቀን ሊያውጅ ይገባል ሲሉ ገልጸዋል።

No comments:

Post a Comment