Wednesday, September 6, 2017

ሀገር የታሰረችበት የዝቅታ ዘመን! – ጌታቸው ሺፈራው



By ሳተናውSeptember 6, 2017 07:17


የሀገር መሰረቱ ቤተሰብ ነው። የትውልድ ምሰሶው ቤተሰብ ነው። ይህ የማህበረሰብ መሰረት ጠንካራ ሲሆን ጠንካራ ሀገር መፍጠር ይቻላል። ይህ የማህበረሰብ መሰረት ሲናጋ የሀገር ህልውና አደጋ ውስጥ ይገባል። ይህ የማህበረሰብ መሰረት ሲታሰር ሀገር ይታሰራል። በዚህ ወቅት ጭቆና እና በደል ያላንኳኳው ቤት የለም። እስር ያልደረሰበት ጎጆ ጥቂት ነው። በተለይ ስልጣን ለማስጠበቅ የወጣው ማሰሪያ አዋጅ (ፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ) ማህበራዊ ግንኙነትን እንኳ መለየት አልቻለም። ምንም ይሁን ምን ግንኙነት ያለውን ሁሉ ይጠፍራል። ያስራል። ቤተሰብን!
በፀረ ሽብርተኝነት አዋጁ በርካታ ቤተሰቦች አንድ ላይ ታስረው ቤት ተፈትቷል። ልጆች አሳዳጊ አጥተው ጎዳና ላይ እንደወጡ ታሳሪዎች እንባ እየተናነቃቸው ለፍርድ ቤት ተናግረዋል። ሚስትለመኖር ስትል የታሰረ ባሏን፣ ባል ልጆቹን ለማሳደግ ሲል የታሰረች ሚስቱን ፈትቷል። ጧሪ የሌላቸው ሽማግሌዎች ባዶ ቤት ስለመቅረታቸው፣ በካድሬዎች “የአሸባሪ ቤተሰብ ነው” ተብለው ከሞቀ ቤታቸው ተፈናቅለው በረንዳ ላይ እንደወደቁ፣ ከማህበራዊ ግንኙነት እንደተገለሉ በዚህ አሳሪ አዋጅ ከቤተሰባቸው የተነጠሉት እስረኞች ጆሮ የማያገኘውን ድምፃቸውን ሲያሰሙ ቆይተዋል። አሁንም ግን ቤተሰብ እየታሰረ፣ ቤተሰብ እየፈረሰ ነው። ለማሳያ ያህል በፀረ ሽብርተኝነት አዋጁ የታሰሩ የቤተሰብ አባላት የሚከተሉት ናቸው።
1) በፍቃዱ አበበ፣ አየለች አበበ፣ ባንተወሰን አበበ ( እናት እና አባታቸውም ታስረው ነበር)
2) ቦኪ እሸቱ፣ ብርሃኑ ቦኪ ፣ ማሙሽ ቦኪ
3) አንዱዓለም አያሌው፣ አዲሱ አያሌው
4) መርጋ ደበሎ፣ ደረጀ መርጋ
5) ደረጀ አደመ፣ አወቀ አደመ
6) አየለ በየነ ( ህክምና ተከልክሎ የሞተ)፣ ቦንሳ በየነ
7) አበረ ፋንታሁን፣ ታፈረ ፋንታሁን
8) መብርህቱ ደምለው? ፣ መከተ መብርህቱ?
9)ደመቀ ነጋ፣ ቻሌ ነጋ
10) ቦረና ረጋሳ፣ ገመችስ ረጋሳ ( ታስሮ የተፈታ)
11) ተስፋዬ አያለው ከእነወንድሙ
12) ሸኽ ቡዲን ነስረዲን፣ ሀያት ነስረዲን ?( የተፈታች)
እነዚህ እንደማሳያ የቀረቡ ናቸው እንጅ በሽህ የሚቆጠር ህዝብ በታሰረበት ሀገር እጅግ በርካታ የቤተሰብ አባላት እስር ቤት ሊሆኑ እንደሚችሉ እሙን ነው። ይህ የማህበረሰብ መሰረት፣ የሀገር ዋልታ ሲታሰር ሀገርም ይታሰራል፣ ሲናጋ ሀገርም ይናጋል። ቤተሰብ ታስሮ፣ ፈርሶ ሀገር ዝቅ እንጅ ከፍ ሊል አይችልም።
አዎ! ቤተሰብ የተናጋበት፣ ማህበረሰብ የተናጋበት፣ ሀገር የተናጋበት፣ ዝቅ ያለበት ዘመን ላይ ነን!
(ጌታቸው ሺፈራው)

No comments:

Post a Comment