Sunday, September 17, 2017

በዛሬ ህዝብ ዉሳኔ በሁሉም ቀበሌዎች ህዝቡ ከጎንደር ጋር መቀጠሉን ወሰነ #ግርማ_ካሳ

   



የቅማንት ማህበረሰብ አብዝኛው አማርኛ ተናጋሪ ነው። ከሌላው ማህበረሰብ ጋር ለዘመናት ተዋልዶ፣ ተፋቅሮ የኖረ፣ ራሱን ጎንደሬ ብሎ የሚጠራ በምንም መስፍርትና ሚዛን አማራው ከሚባለው ማህበረሰብ ጋር የማይለያይ ማህበረሰብ ነው።
ሆኖም ወገን ከወገን፣ ሕዝብ ከህዝብ መከፋፈል ስራዉና ባህሪው የሆነው ህወሃት፣ በሚቆጣጠረው የፌዴራል መንግስት በኩልና እርሱ ባስቀመጣቸው ጥቂት የብአዴን አመራሮች አማካኝነት ፣ ከመቼውም ጊዜ በላይ እየጠነከረ የመጣውን የወልቃይት ጥያቄን ለማዘናጋት፣ ሕዝቡን ለማዳከምና እርስ በርስ እንዲጫረስ ለማድረግ በወጥነው ዉጥን መሰረት፣ ዛሬ በስምንት ቀበሌዎች ህዝብ ዉሳኔ ተደርጓል። በሰሜን ጎንደር ዞን ወይስ አዲስ በሚቃቀረው የቅምናት ዞን በሚል።
ከዛሬው ዉሎ አንዱና ትልቁ አስደሳች ጉዳይ ቢኖር ምንም አይነት ረብሻ፣ ችግርና ብጥብጥ አለመፈጠሩ ነው። ህዝቡ ቅማንት፣ አማራ ሳይባባል ኢትዮጵያዊ፣ የጎንደር ጨዋነቱን ያሳየበት ምርጫ ነበር። በስምንቱም ቀበሌዎች “ሕዝቡ ጎንደሬ ነን ፤የጎንደር አካል ሆነን ነው መቀጠል የምንፈልገው” የሚል ድምጽ እንደሰጠ ነው መረጃዎች የሚጠቁሙት። በስምንቱ ቀበሌዎች በጥቅል ብቻ ሳይሆን በሁሉም የምርጫ ጣቢያዎች የሕዝቡ ድምጽ ተመሳሳይ ነበር።፡ ሕዝቡ ቅማንት ፣አማራ ሳይባባል አንድ መሆኑን በመግለጽ ለሕወሃት “እኛ አንድ ነን፤ አትከፋፍሉን” የሚል መልእክት ነው ያስተላለፈው።
ምርጫውን ሲመራ የነበረው ምርጫ ቦርድ፣ በዛሬው ቀን የምርጫ ውጤቶችን መለጠፍ ሲገባው ለነገ ቀጠሮ ሰጥቷል። ሌሊቱን ሙሉ ኮሮጂ የሕዝብን ድምጽ ቀይሮ መግለጫ ሊያወጣ እንደሚችል  ብዙዎች ይናገራሉ። ሆኖም ግን ከዚህ በፊት የነበረውን የቅማንትና አማራ አንድ ናቸው አቋሙን በማለሳለስ ፣ ተገዶ ሕዝበ ዉሳኔ እንዲሰጥ የተገደደው የአቶ ገዱ አንዳራጋቸው የክልል አስተዳደር፣ ጣልቃ በመግባት የሕዝቡን ድምጽ ሊያስከበር ይችላል የሚል ተስፋም አለ።

No comments:

Post a Comment