Thursday, April 27, 2017

የፖለቲካ አመራር ብቃት ማነስ በአሜሪካ ስህተት፣ በኢትዮጲያ ውድቀት ያስከትላል



ከስዩም ተሾመ
የበለፀገ ኢኮኖሚ እና የዳበረ ዴሞክራሲ ያላቸው ሀገራት አንዴ ጦረኛ፥ ሌላ ግዜ ምሁር፣ ከዛ ደግሞ ዘረኛ የሆነ መሪ ሊኖራቸው ይችላል። ለምሳሌ አሜሪካ እንደ ጆርጅ ቡሽ በሚሊዮን የሚቆጠሩ የአፍጋኒስታን፣ ኢራቅ፣ ፓኪስታን፣…ወዘተ ዜጎችን ለሞት፥ ሥቃይና ስደት የዳረገ ጦረኛ ፕረዜዳንት ነበራት። ከእሱ ቀጥሎ ደግሞ ገና ለፕረዜዳንትነት በተመረጠ ማግስት የዓለም የሰላም ኖቬል ሽልማትን የተሸለመው ባራክ ኦባማ መርቷታል። በአሜሪካ የመጀመሪያው ጥቁር ፕረዜዳንት የተተካው ግን የመጨረሻ የነጭ አካራሪና ዘረኛ በሆነው ዶናልድ ትራምፕ ነው።
ስዩም ተሾመ
በዚህ መልኩ ፕ/ት ጆርጅ ቡሽ ያበላሸውን ገፅታ ባራክ ኦባማ ሲገነባ፣ ፕ/ት ባራክ ኦባማ የገነባውን ገፅታ ዶናልድ ትራምፕ መልሶ ያፈርሳል። ያም ሆኖ ግን፣ የአሜሪካ ፕረዜዳንቶች የፖለቲካ አመራር ብቃት በሀገሪቱ የወደፊት ዕጣ-ፋንታ እና በሕዝቡ ሕይወት ላይ የሚፈጥረው ተፅዕኖ በጣም ውስን ነው። እንደ ኢትዮጲያ ባሉ የበለፀገ ኢኮኖሚ እና የዳበረ ፖለቲካዊ ሥርዓት በሌላቸው ሀገራት ግን የመሪዎች የአመራር ብቃት የሕልውና ጉዳይ ነው። ምክንያቱም፣ የደሃ ሀገራት መሪዎች የፖለቲካ አመራር ብቃት በሀገሪቱ ሰላም፥ ልማትና ዴሞክራሲ ከማረጋገጥ ጋር ቀጥተኛ የሆነ ተያያዥነት አለው።
ደቡብ አፍሪካዊው ፀኃፊ “William Gumede” ስለ ጉዳዩ በሰጠው ትንታኔ መሰረት፣ የፖለቲካ አመራር ብቃት ከበለፀጉ ሀገራት ይልቅ በደሃና ታዳጊ ሀገራት ዘንድ እጅግ ወሳኝ የሆነ ሚና አለው። ምክንያቱም፣ የበለፀጉ ሀገራት በተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎች ዘንድ ከፍተኛ የዕውቀትና የልምድ ክምችት አለ። ከዚህ በተጨማሪ፣ አስፈላጊው የፖለቲካ አመራር ብቃት የሌለውን መሪ በዴሞክራሲያዊ ምርጫ አማካኝነት በቀላሉ ከስልጣን ማውረድና በሌላ መተካት ይችላሉ።
እንደ ኢትዮጲያ ባሉ የአፍርካ ሀገራት ግን የፖለቲካ መሪዎች ብቃት የሀገራቱን ሰላም፣ ልማትና ዴሞክራሲ ወደፊት ሊያስቀጥል ወይም ወደኋላ ሊቀለብስ ይችላል። እንደ ፀኃፊው አገላለፅ፣ እንደ ኢትዮጲያ ባሉ ሀገራት የሕዝቡ ሰላምና ደህንነት፥ የሀገሪቱ ልማትና ዴሞክራሲ በዋናነት የተመሰረተው በፖለቲካ መሪዎች የአመራር ብቃት ላይ እንደሆነ እንደሚከተለው ገልፆታል፡-
“In poor countries, competent political leadership is a scarce skill that matters even more than in industrial nations. Industrial nations, where power is dispersed across the society, can tolerate bad leaders better. Better still, bad leaders can generally be outvoted. The right kind of leader in fractious, ethnical diverse and underdeveloped African countries, can be a rallying force that helps binds them together, and helps unleash the country’s productive energies. A bad leader, in the context of fragile democratic institutions, ethnic diversity, and underdevelopment, can be terribly destructive – holding back democracy, growth and nation-building. Worse, in African countries bad leaders are difficult to rid of, and remain a drain on the system long after they are eventually gone.” William Gumede, Pambazuka News, Nov 26, 2009

ከላይ በጥቅሱ እንደተገለፀው፣ የተጠናከሩ ዴሞክራሲያዊ ተቋማት፣ የተለያዩ ብሄሮች፥ ብሄረሰቦችና ሕዝቦች፣ እና ዝቅተኛ ልማት ባለበት ሀገር ብቃት የሌለው የፖለቲካ መሪ ለሀገሪቱ እድገት፣ ዴሞክራሲ እና አንድነት ዋና እንቅፋት ነው። ነገር ግን፣ የችግሩ መሰረታዊ መንስዔ ከብሄር ልዩነት ወይም ከሀገሪቱ የልማት ደረጃ ጋር ይልቅ የተጠናከሩ ዴሞክራሲያዊ ተቋማት ካለመኖራቸው ጋር በቀጥታ የተያያዘ ነው።
በመሰረቱ፣ ውሳኔ መስጠት (Decision making) ከተለያዩ አማራጭ የውሳኔ ሃሳቦች ውስጥ አንዱን መምረጥ ነው። በዚህ መሰረት፣ ጠንካራ ዴሞክራሲያዊ ተቋማት ባላቸው ሀገራት የፖለቲካ ውሳኔና አመራር መስጠት በጣም ቀላል ነው። በዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ውስጥ አማራጭ የውሳኔ ሃሳቦች የሚቀርበው ከአራት የተለያዩ አቅጣጫዎች ነው።
ለምሳሌ፣ አዲሱ የአሜሪካ ፕረዜዳንት ገና ወደ ስልጣን እንደመጡ በተወሰኑ ሀገሮች ላይ የጉዞ እገዳ መጣላቸው ይታወሳል። በመጀመሪያ ይህ የውሳኔ ሃሳብ የቀረበው ከራሳቸው ከፕረዜዳንቱ፣ ከካቢኔያቸው ወይም ከአማካሪዎቻቸው ሊሆን ይችላል። ይሁን እንጂ፣ አንድ የውሳኔ ሃሳብ ለፕረዜዳንቱ መቅረቡ እንደታወቀ በዋናነት የተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅቶች፣ የሚዲያ ተቋማትና የሙያና ሲቭል ማህበራት የእያንዳንዱን አማራጭ የውሳኔ ሃሳብ አዎንታዊ እና አሉታዊ ጎኖች በዝርዝር እየተነተኑ ማቅረብ ይጀምራሉ። ስለዚህ፣ የፖለቲካ መሪው የውሳኔ ሃሳቡን ያሻሽላል። በዚህም ከሁሉም አማራጮች የተሻለው የውሳኔ ሃሳብ ተቀብሎ ያፀድቃል። ልክ ፕ/ት ዶናልድ ትራምፕ የእነዚህን አካላት ሃሳብና አስተያያት ችላ ብሎ ተቀባይነት የሌለው ውሳኔ የሚያሳልፍ ከሆነ በፍርድ ቤት ትዕዛዝ ውድቅ ይደረጋል።
በኢትዮጲያ ሰፊ የሆነ የብሄር ልዩነት እና ዝቅተኛ ልማት መኖሩ እርግጥ ነው። ከዚህ በተጨማሪ፣ በፖለቲካዊና ታሪካዊ ጉዳዮች ላይ ብሔራዊ መግባባት የለም። ከሁሉም በለይ ግን በሀገሪቱ ጠንካራ የዴሞክራሲ ተቋማት የሉም። የኢህአዴግ መንግስት ባለፉት አስር አመታት ውስጥ በፀረ-ሽብር ሕጉ፣ በሚዲያ ሕጉ፣ እንዲሁም የበጎ-አድራጎት ተቋማት ማቋቋሚያ አዋጅን ተግባራዊ በማድረጉ በሀገሪቱ የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት መዋቅር ሙሉ-በሙሉ ፈርሷል። በዚህ ምክንያት፣ ኢትዮጲያ ውስጥ ጠንካራ የዴሞክራሲ ተቋማት የሚባሉት፤ ነፃና ገለልተኛ የሚዲያ ተቋማት፣ የተደራጁ የተቃዋሚ ፖለቲካ ድርጅቶች እና የሲቪል ማህበራት ከነጭራሹ የሉም ማለት ይቻላል።
የፖለቲካ መሪዎች ውሳኔና አመራር የሚሰጡት ከተለያዩ አማራጮች ውስጥ የተሻለውን የውሳኔ ሃሳብን በመምረጥ ነው። እንደ አሜሪካ ጠንካራ የዴሞክራሲ ተቋማት ካላቸው ሀገራት አንፃር ሲታይ በኢትዮጲያ የፖለቲካ ውሳኔና አመራር መስጠት በጣም ከባድ ነው። ቀደም ሲል ለመግለፅ እንደተሞከረው፣ የዳበረ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ባላቸው ሀገራት አማራጭ የውሳኔ ሃሳቦች የሚቀርቡት ከአራት የተለያዩ አቅጣጫዎች ነው። ነገር ግን፣ እንደ ኢትዮጲያ ነፃና ገለልተኛ የሚዲያ ተቋማት፣ የተደራጁ የተቃዋሚ ፖለቲካ ድርጅቶች እና የሲቪል ማህበራት በሌሉበት አማራጭ የውሳኔ ሃሳቦች የሚቀርቡት ከአንድ ወገን ብቻ ነው።
ለምሳሌ፣ ከአሜሪካው ፕሬዜዳንት ወይም ደግሞ ከእንግሊዝ ጠ/ሚኒስትር አንፃር ሲታይ የኢትዮጲያው ጠ/ሚኒስትር ውሳኔና መመሪያ የሚሰጡት ልክ በድቅድቅ ጭለማ ውስጥ እንዳለ ሰው ነው። በራሳቸው ከሚያውቁት፣ ከፓርቲያቸው ወይም ከአማካሪዎቻቸው ከተሰጣቸው ውጪ፤ የውሳኔያቸውን አግባብነት ለመፈተሸ የሚያስችሉ አስተያየቶች፣ ሌሎች አማራጭ የውሳኔ ሃሳቦች ስለመኖራቸው፣ ወይም ውሳኔያቸው ስለሚያስከትለው አሉታዊና አዎንታዊ ጎን ተጨማሪ ሃሳብና አስተያየት የሚያገኙበት መንገድ የለም። ስለዚህ፣ ጠ/ሚ ኃይለማሪያም ልክ በድቅድቅ ጭለማ ክፍል ውስጥ እንዳለ ሰው በራሳቸው በሚያውቁትና በመሰላቸው መንገድ የፖለቲካ ውሳኔና መመሪ ይሰጣሉ።
“William Gumede” እንዳለው፣ በአብዛኞቹ የአፍሪካ ሀገራት የሕዝቡ ሰላምና ደህንነት፥ የሀገሪቱ ልማትና ዴሞክራሲ በዋናነት በመሪዎቹ የአመራር ብቃት ላይ የተመሰረተ ነው። ለዚህ ዋናው ምክንያት ከላይ የተጠቀሰው ጭለማ ነው። የፖለቲካ መሪዎቹ፣ ከገዢው ፓርቲ አባላትና አመራሮች በተጨማሪ፣ ከተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎች የተለያዩ ሃሳቦችና አስተያየቶችን የሚቀበሉ ከሆነ፣ በዚህም በትክክለኛ መረጃና ዕውቀት ላይ የተመሰረተ ውሳኔ፣ እንዲሁም በተግባር የተደገፈ መመሪያ የሚሰጡ ከሆነ የሕዝቡ ሰላምና ደህንነት፣ የሀገሪቱ ልማትና ዴሞክራሲ ማረጋገጥ ይችላሉ።
ነገር ግን፣ ጠንካራ የዴሞክራሲ ተቋማት በሌለበት ሁኔታ የሀገሪቱ መሪዎች በራሳቸው ተነሳሸነት የሕዝቡን ጥያቄና ፍላጎት ለማወቅ ጥረት ካላደረጉ፣ ከአንድ ወገን በመጣ መረጃ ላይ ብቻ ተመስርተው ውሳኔና መመሪያ የሚሰጡ ከሆነ የፖለቲካ አመራር ብቃት የላቸውም። እነዚህ መሪዎች የተረጋጋ ፖለቲካዊ ሥርዓት ለመዘርጋት አስፈላጊ የሆነውን የአመራርነት ሚና መወጣት አይችሉም። የተረጋጋ ፖለቲካዊ ሥርዓትና ቁርጠኛ አመራር በሌለበት ሁኔታ የሀገሪቱን ሰላምና ልማት በዘላቂነት ማረጋገጥ አይቻልም። በመሆኑም፣ እንዲህ ያሉ የፖለቲካ አመራር ብቃት የሌላቸው መሪዎች ለሀገር ሰላም፥ ልማትና ዴሞክራሲ እንቅፋት ናቸው።
በዚህ መሰረት፣ “የሀገራችን መሪዎች የፖለቲካ አመራር ብቃት እንዴት ይታያል?” የሚለውን በሌላ ፅሁፍ እመለስበታለሁ። እንደው በጥቅሉ ሲታይ ግን፣ አሁን በሀገራችን የሚስተዋለው መሰረታዊ ችግር የመልካም አስተዳደር እጦት ወይም የኪራይ ሰብሳቢነት አመለካከት አይደለም። ከዚያ ይልቅ፣ የሀገሪቱ መሰረታዊ ችግር የመሪዎቿ የፖለቲካ አመራር ብቃት ማነስ ነው።

No comments:

Post a Comment