Monday, April 24, 2017

በሳኡዲ የጋዝ ፍንዳታ 2 ኢትዮጵያውያንን ገድሎ 1 አቁስሏል


በሳኡዲ የጋዝ ፍንዳታ 2 ኢትዮጵያውያንን ገድሎ 1 አቁስሏል – በሳኡዲ አረቢያ አጅማን ተብሎ በሚጠራ አካባቢ በሚገኝ የመኖሪያ ቤት ማብሰያ ክፍል ውስጥ የተከሰተ የጋዝ ሲሊንደር ፍንዳታ፣ ሁለት ኢትዮጵያውያን ሴቶችን ለህልፈተ ህይወት ሲዳርግ፣ አንዲት ሌላ ኢትዮጵያዊትንና አንዲት ኢንዶኔዢያዊትን በከፍተኛ ሁኔታ ማቁሰሉን ዘ ገልፍ ኒውስ ዘግቧል፡፡
ባለፈው ረቡዕ የተከሰተው ፍንዳታ ስሟ ያልተጠቀሰውን የ47 ዓመት ኢትዮጵያዊት ወዲያውኑ የገደለ ሲሆን፣ ሌላኛዋ ኢትዮጵያዊት ሆስፒታል ከደረሰች በኋላ ሞታለች፤ የተረፈቺው ኢትዮጵያዊትና ኢንዶኔዢያዊት ደግሞ ከፍተኛ የቃጠሎና የመቁሰል አደጋ እንደደረሰባቸውና በሼክ ካሊፋ ሆስፒታል የህክምና እርዳታ እየተደረገላቸው እንደሚገኙ ዘገባው ጠቆሟል፡፡
የሞቱት ኢትዮጵያውያን ሴቶች አስከሬን ምርምራ እየተደረገበት እንደሚገኝ የጠቆመው ዘገባው፤ ምርምራው መጠናቀቁንና አስፈላጊ ህጋዊ ጉዳዮች መሟላታቸውን ተከትሎ፣ አስከሬኖቹ ወደ ኢትዮጵያ እንደሚላኩ ፖሊስ ማስታወቁን አመልክቷል፡፡
ፍንዳታው ከማብሰያ ቤቱ በተጨማሪ ከጎኑ የሚገኝን ሌላ ክፍል ግድግዳዎችና መስኮቶች እንዳፈራረሰ የዘገበው ዘ ገልፍ ኒውስ፤ ከሶስት ወራት በፊትም ራስ አል ካይማህ በተባለ አካባቢ በተከሰተ ተመሳሳይ የጋዝ ሲሊንደር ፍንዳታ አደጋ፣ ምግብ ስታበስል የነበረች አንዲት ኢትዮጵያዊት የቤት ሰራተኛ ለሞት  መዳረጓን አስታውሷል

No comments:

Post a Comment