Tuesday, July 11, 2017

ቴዲ አፍሮ በሚሊኒየም አዳራሽ ለሚያዘጋጀው ኮንሰርት የመንግሥትን ይሁንታ እየጠበቀ ነው – ውድነህ ዘነበ



ታዋቂው ድምፃዊ ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) ‹‹ኢትዮጵያ›› የተሰኘውን አልበም ካወጣ በኋላ፣ በአዲስ አበባ ከተማ ሚሊኒየም አዳራሽ የመጀመርያውን ኮንሰርት ለማቅረብ የመንግሥትን ይሁንታ እየጠበቀ ነው፡፡
ድምፃዊው ጳጉሜን 5 ቀን 2009 ዓ.ም. ለአዲስ ዓመት ዋዜማ የሙዚቃ ዝግጅቱን ለማቅረብ መዘጋጀቱን፣ ማኔጀሩ አቶ ጌታቸው ማንጉዳይ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
ኮንሰርቱን አልበሙን ያከፋፈለው ኩባንያ ጆይ ኤቨንትና ፕሮሞሽን ኩባንያ ከኤፕላስ ኤቨንትና ፕሮሞሽን ኩባንያ ጋር በጥምረት የሚያዘጋጁት መሆኑን፣ ጆይ ኤቨንት የሚሊኒየም አዳራሽን ከሚያስተዳድረው አዲስ ፓርክ ጋር ስምምነት ላይ መድረሱን ለማወቅ ተችሏል፡፡
ጆይ ኤቨንት ኮንሰርቱን ለማዘጋጀት የሚያስችል ዕውቅና ለማግኘት ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጽሕፈት ቤት ለሰላማዊ ሠልፍና ስብሰባ ፈቃድ ማሳወቂያ ክፍል ጥያቄ ማቅረቡም ታውቋል፡፡
የአዲስ ፓርክ ዴቨሎፕመንትና ማኔጅመንት ኩባንያ የማርኬቲንግና የሰው ኃይል መምርያ ኃላፊ አቶ ስለሺ ለማ፣ ሰኔ 2 ቀን 2009 ዓ.ም. ለከንቲባ ጽሕፈት ቤት በጻፉት ደብዳቤ ለአዲስ ዓመት ዋዜማ የሙዚቃ ኮንሰርት በሚሊኒየም አዳራሽ ለማካሄድ ፕሮግራም መያዙን ገልጿል፡፡ ‹‹ለፕሮግራሙ ተገቢው ትብብር ይደረግለት ዘንድ እንጠይቃለን፤›› በማለት አቶ ስለሺ በጻፉት ደብዳቤ ጠይቀዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጽሕፈት ቤትና የካቢኔ ጉዳዮች ኃላፊ አቶ አሰግድ ጌታቸው የኮንሰርት ጥያቄ መቅረቡን ለሪፖርተር አረጋግጠው፣ ነገር ግን ከሚመለከተው አካል ጋር ንግግር ከተደረገ በኋላ ምላሽ እንደሚሰጡ አስታውቀዋል፡፡
ለዚህ ኮንሰርት ቴዲ አፍሮ 1.8 ሚሊዮን ብር እንደሚከፈለው፣ ለሚሊኒየም አዳራሽ የዕለቱ ዝግጅት ኪራይ 1.2 ሚሊዮን ብር ክፍያ ለመፈጸም ስምምነት ላይ መደረሱን ምንጮች ተናግረዋል፡፡
ቴዲ አፍሮ የአዲስ አበባውን ኮንሰርት ካካሄደ በኋላ በሐዋሳ፣ በጎንደርና በመቀሌ ተጨማሪ ኮንሰርቶችን እንደሚያካሂድ ከስምምነት ላይ መድረሱን ለማወቅ ተችሏል፡፡
‹‹ኢትዮጵያ›› የተሰኘውን አልበም ጨምሮ አራት አልበሞቹን ለአድማጮች አቅርቧል፡፡ ከአልበም በተጨማሪ በርካታ ነጠላ ዜማዎችን በተለያዩ ጊዜያት ያቀረበ ሲሆን፣ ሥራዎቹ በአድናቂዎቹ ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነት እንደነበራቸው ይታወቃል፡

No comments:

Post a Comment