Tuesday, November 7, 2017

አላሙዲንን በሆቴሉ ወለል ፍራሽ ታድሏቸው በአንድ ቦታ መታሰራቸውን በምስል የተደገፉ ሪፖርቶች አመለከቱ።

(ኢሳት ዜና–ጥቅምት 28/2010)ሼህ መሀመድ አላሙዲንን ጨምሮ በቁጥጥር ስር የዋሉት የሳውዲ ባለሃብቶችና ባለስልጣናት የታሰሩበት ባለ አምስት ኮከብ ሆቴል መሆኑ ቢረጋገጥም በሆቴሉ ወለል ፍራሽ ታድሏቸው በአንድ ቦታ መታሰራቸውን በምስል የተደገፉ ሪፖርቶች አመለከቱ። የሼህ መሀመድ አላሙዲን በሙስና ተጠርጥሮ መታሰር በኢትዮጵያ ባላቸው ኢንቨስትመንት ላይ የሚኖረው አንድምታ አነጋጋሪ ሆኗል። የሼህ መሀመድ አላሙዲን ከሳውዲ ልኡላንና ነጋዴዎች ጋር መታሰር በአለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን በስፋት መዘገቡ ቢቀጥልም በኢትዮጵያ ውስጥ የመንግስትና የፓርቲ መገናኛ ብዙሃን በዝምታቸው ቀጥለዋል። የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በሳውዲ ከሙስና ጋር በተያያዘ እስራት መከተሉን ቢዘግብም የሼህ መሀመድ አላሙዲንን መታሰር ሳይጠቅሰው አልፏል። ዳሽን ባንክ ባለፈው ቅዳሜ በአዲስ አበባ ከተ...ማ ከአንድ ቢሊየን ብር በላይ በሆነ ወጪ ባስገነባው ግዙፍና ዘመናዊ ሕንጻ ምርቃት ላይ ይገኛሉ ተብለው የተጠበቁት ሺህ መሀመድ አላሙዲን በዕለቱ በሳውዲ አረቢያ ውስጥ በመታሰራቸው ሕንጻው እሳቸው በሌሉበት ተመርቋል። በኢትዮጵያ ሕግ በባንክና ኢንሹራንስ ዘርፍ ለመሰማራት የተፈቀደው ለኢትዮጵያ ዜጎች ብቻ በመሆኑ ሼህ መሀመድ አላሙዲን ዳሽን ባንክን በቤተሰቦቻቸው አማካኝነት ማቋቋማቸው ተመልክቷል። በኢትዮጵያ በዋናነት በሆቴልና በማዕድን እንዲሁም በእርሻና በሲሚንቶ ኢንቨስትመንት ላይ መሰማራታቸው የተገለጸው የ71 አመቱ ባለሃብት ሼህ መሀመድ አላሙዲን በተለይ ከ1997 ምርጫ ወዲህ ስልጣን ላይ ላለው ቡድን በግልጽ በሚያሳዩት ድጋፍ ተቃውሞ ይሰነዘርባቸዋል። በተለይ በማዕድን ዘርፍ በሚሰሩት ኢንቨስትመንት የሀገሪቱን የወርቅ ሀብት በከፍተኛ ደረጃ እየመዘበሩ ነው በሚል ትችቶች እየቀረበባቸው ይገኛል። ይህም ለስርአቱ ለሚያሳዩት አጋርነት ስልጣን ላይ ባለው ቡድን በሚደረግ ድጋፍ የሚከናወን መሆኑም ተመልክቷል። በሌላም በኩል ባለሃብቱ ለስርአቱ ከሚሰጡት ድጋፍ ባልተናነሰ የሚያደርጉት በጎ አድራጎት ለሀገር ይጠቅማል በሚል ባለሃብቱን በበጎ የሚያነሷቸውም አልጠፉም። በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ የመንግስትና የገዢው ፓርቲ መገናኛ ብዙሃን የሼህ መሀመድ አላሙዲንን መታሰር በተመለከተ በዝምታ መቀጠላቸው የባለሃብቱ መታሰር በስርአቱ ውስጥ ድንጋጤ ስለመፍጠሩ የተገለጸውን የሚያጠናክር ሆኖ ተገኝቷል። የኢትዮጵያ መንግስት በሀገሪቱ የሰፈነውን የፖለቲካ አፈናና የሰብአዊ መብት ረገጣ እንዲያሻሽል ያግዛል በሚል የአሜሪካ ኮንግረስ እንዲያጸድቀው የቀረበውን ረቂቅ ህግ ለማክሸፍ ከመንግስት ጋር ሎቢስት በመቅጠር ሲንቀሳቀሱ መቆየታቸውና በዚህ ረገድ የሚፈጠረው ክፍተት የመንግስት ባለስልጣናትን ሳያሳስብ እንዳልቀረ የሚገልጹ ወገኖች አሉ። በሌላም በኩል ብዙዎቹ ባለስልጣናት ገንዘብ የሚያሸሹት በርሳቸው አማካኝነት በመሆኑም ይህም ተጨማሪ ምናልባትም ዋና ስጋት እንደሆነባቸው ታውቋል። የሼህ አላሙዲን መታሰር በርሳቸው የሀገር ውስጥ ኩባንያዎች እንዲሁም በኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ላይ የሚኖረው አንድምታ በእስሩ ርዝመትና ውጤት እንደሚወሰንም ባለሙያዎች ይናገራሉ። ሼህ መሀመድ አላሙዲንን ጨምሮ ባለፈው ቅዳሜ የተያዙትና አሁንም በመያዝ ላይ የሚገኙት ባለሃብቶችና ባለስልጣናት በሪያድ እጅግ ውድ በተባለው ሪዝ ካርተን ሆቴል ወለል ላይ የነፍስ ወከፍ ፍራሽ ታድሏቸው መታሰራቸውን አለም አቀፍ የመገናኛ ብዙሃን በምስል አስደግፈው ይፋ አድርገዋል። የሆቴሉ የስልክና የኢንተርኔት አገልግሎት መቋረጡም ይፋ ሆኗል።

No comments:

Post a Comment