Wednesday, November 8, 2017

ሼህ መሀመድ አላሙዲንን ጨምሮ ለአደጋ የተጋለጠው የባለሀብቶቹ ንብረት 33 ቢሊየን ዶላር መሆኑ ተመልክቷል።

(ኢሳት ዜና–ጥቅምት 29/2010)የሳውዲ አረቢያ መንግስት ባለፈው ቅዳሜ በቁጥጥር ስር ያዋላቸው ትውልደ ኢትዮጵያዊው ሼህ መሀመድ አላሙዲንን ጨምሮ የሌሎች ታሳሪዎችን የባንክ ተቀማጭ ሒሳብ አገደ። ከእስሩ ጋር በተያያዘ በአጠቃላይ ለአደጋ የተጋለጠው የባለሀብቶቹ ንብረት 33 ቢሊየን ዶላር እንደሚገመትም ከብሉምበርግ ዘገባ መረዳት ተችሏል። የሼህ መሀመድ አላሙዲን ቃል አቀባይ ከብሉምበርግ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ርምጃው በሳውዲ አረቢያ ውስጥ የተገደበና በሌሎች ሀገራት ያላቸውን ንብረት የማይመለከት መሆኑን ገልጸዋል። ቋሚ መኖሪያቸውን በሳውዳረቢያ ጅዳ ያደረጉት ሼህ መሀመድ አላሙዲን እስካለፈው ሳምንት መጨረሻ በሳውዳረቢያ ሪያድ በተካሄደው ግሎባል ኢንቨስትመንት ፎረም ላይ ከተገኙ በኋላ መያዛቸውና መታሰራቸውም ተመልክቷል። ከሳውዲ ባሻገር በሞሮኮ፣በሲውዲን...ና በኢትዮጵያ ከፍተኛ ኢንቨስትመትን ያላቸው ሼህ መሀመድ አላሙዲን የሳውዲው እስራትና እገዳ በሌሎች ሀገራት ኢንቨስትመንታቸው ላይ ተጽእኖ አይኖረውም ሲሉ ቃል አቀባያቸው ቲም ፓንደር ተናግረዋል። በሳውዲ የተፈጠረውም ሁኔታ የንጉሳውያን ቤተሰቦች የውስጥ ችግር ነው ሲሉ ለብሩምበርግ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል። የ10 ነጥብ 3 ቢሊየን ዶላር ሀብት ባለጸጋ በሆኑት በሼህ መሀመድ አላሙዲንና በሌሎች ታሳሪዎች ላይ የተጣለው እገዳ የግል ተቀማጭ ሂሳባቸውን ብቻ የሚመለከት መሆኑንም የሳውዳረቢያው ብሔራዊ ባንክ አስታውቋል። የታሳሪዎቹ ኩባንያ ተቀማጭ ሒሳብ አለመታገዱንና ሕጋዊውን የባንክ ስርአት ተከትለው ገንዘባቸውን ማንቀሳቀስ እንደሚችሉም ይፋ ሆኗል። የብሪታኒያው ዴይሊ ሜል ይፋ ያደረገውና በታዋቂው ሪትዝ ካርልተን ሆቴል ወለል ላይ ፍራሽና ብርድልብስ ታድሏቸው የታሰሩት ባለስልጣናት፣ባለሃብቶችና ልኡካን በቁጥር 50 ያህል መሆናቸው ተመልክቷል። የሳውዳረቢያ ጠቅላይ አቃቢ ህግ እንደገለጹት ደግሞ ይህ እስራት የመጨረሻው ሳይሆን የመጀመሪያ ምዕራፍ ሲሆን በቀጣይ የሚታሰሩ መኖራቸውንም አስታውቀዋል።

No comments:

Post a Comment